[gtranslate]

ውስብስቡ የአገራችንና የዓለም ሁኔታ፣ እንዲሁም  ግራ የተጋባው  የትግል  ዘዴያችን !

                                                          ፈቃዱ በቀለ(ዶ/ር)

                                                        ጥር፣2015

 

                    „የሰው ልጅ ዕድገት በቆየው ግንባታ ላይ አዲስ የመቀጠል  

                         የትውልድ ሂደት ነው። ይህ በአብዛኛው የሚታየው ታዲያ

                         በሳይንስና በቴክኖሎጂው ዘርፍ ነው። በማህበራዊ ህይወትና

                         በኑሮ ልምድ ላይ የተቀጣጠለ የመረጃ መለዋወጥ ባህላችን

                         እምብዛም የጎላ አይደለም። አብዛኛውን ጊዜ ለአዲሱ ትውልድ

                         እንቅፋት የሚሆነው አሮጌው ትውልድ ላይ ቀድሞ ደርሶበት

                         የነበረ የህይወትና የኑሮ ሳንካ ነው። ለምን ? አላፊው ትውልድ

                         በህይወት ጉዞ ላይ ሳለ እግረ-መንገዱን መጪው ትውልድ

                         መንገዱን እንዲያቃናለት ጥርጊያውን ሊያሳምርለት ይገባል።

                         ጉድባውን ባይደለድል እንኳን አመላካቾችን በማኖር፣ „እዚህ

                         ዕድሜና ኑሮ ላይ እንዲህ ያለ የህይወት ሳንካ አለ“ ማለት

                         ይገባዋል። እኔ በዚች መጽሐፍ ማከናወን የፈለግኩት ይሄንን

                         ተግባር ነው።“ * „ፈተና“ ከሚባለው ከወይዘሮ አስቴር ሰይፈ

                         መጽሀፍ የተወሰደ ጥቅስ!

 

መግቢያ

        አንድ ህዝብ ለነፃነት፣ ለዕኩልነትና ለብልጽግና በሚያደርገው ትግሉ፣ የትግሉ መሰካትና ያለመሳካት ሊወሰን የሚችለው በምሁሩ ንቃተ-ህሊና ስፋትና ጥንካሬ፣ እንዲሁም ድክመት ነው። የአንድን ህዝብ ብሶት በደንብ አዳምጦና ተረድቶ፣ እንዲሁም ደግሞ ተጨባጭ ሁኔታዎችን አንብቦ የህዝቡን የትግል አቅጣጫ ፈር ለማሲያዝ አንድ ምሁር የሚመራበት የትግል ዘዴ መኖር አለበት። ለትግሉ መሳካትም በሳይንስ የተፈተነና ሁኔታውን በደንብ ሊተነትን የሚያስችል የቲዎሪ መሳሪያ መኖር አለበት። እየወደቀ የተነሳውንና እዚህ የደረሰውን በተለይም የአውሮፓውን ስልጣኔና የካፒታሊዝምን ዕድገት ስንመለከት በየታሪኩ ወቅት ብቅ ያሉ፣ በከፍተኛ ዕውቀት የተካኑ ፈላስፋዎችና ሳይንቲስቶች ዕልክ የሚያስጨርስ የጭንቅላት ስራ ባይሰሩ ኖሮ፣ የአውሮፓውም ሆነ ጠቅላላው የዓለም ማህበረሰብ እዚህ ዐይነቱ የዕድገት ደረጃ ላይ መድረስ ባልቻለ ነበር። እንደሚባለው በሳይንስ ላይ ባልተመረኮዘ ቲዎሪ የአንድ ህዝብ የነፃነት ጥምና የስልጣኔ ፍላጎት ተግባራዊ ለመሆን ስለማይችል ነው።

       አንድን ሁኔታ በሳይንስ መነጽር ለማንበብ መሞከርና፣ እንዲሁም ህዝብ እንዲገነዘበው ለማድረግና፣ ከዚያም በመነሳት ትክክለኛውን የትግል አቅጣጫ እንዲይዝ ማድረግ እንደቅንጦት ወይም የአካዴሚሺያን ቅብጠት ሆኖ መታየት የለበትም። እስከዛሬ ድረስ በተለይም የሶስተኛው ዓለም ተብለው በሚጠሩት አገሮች ውስጥ የተካሄደው በመሳሪያ የታገዘ ዕልህ አስጨራሽ ውጣ ውረድ የበዛበት ትግል አመርቂ ውጤት ማምጣት ያልቻለው፣ ለነፃነት እንታገላለን ብለው መሳሪያ አንግበው የሚነሱ ኃይሎችም ሆነ፣ ወይም ደግሞ በሰላም መንገድ እንታገላለን የሚሉ ከመጀመሪያውኑ ሳይንሳዊ መርህን እንደመመሪያ አድርገው መንቀሳቀስ ባለመቻላቸውና ባለመፈለጋቸው ነው። እንደዚህ ዐይነቱ በቲዎሪና በሳይንስ ላይ ያልተመረኮዘና፣ ከውስጥ በግልጽ ክርክር የማይደረግበት የትግል ዘዴ የመጨረሻ መጨረሻ አምባገነናዊ ባህርይ ይይዛል። በብዙ የሶስተኛው ዓለም አገሮችም ዛሬ የሚታየው የኑሮ መመሰቃቀልና የህዝቦች የሰቆቃ ኑሮ የሚያረጋግጠው ከመጀመሪያውኑ የቱን ያህል በቲዎሪና በሃሳብ ዙሪያ ትግል ያልተካሄደ መሆኑን ነው።

       በሳይንስ የተፈተነ የትግል መሳሪያ ቲዎሪ አስፈላጊነቱ እንዲያው አንድን ጨቋኝ አገዛዝ ከመጣል አንጻር ብቻ መታየት የለበትም። በመጀመሪያ ደረጃ፣ ጨቋኝ የሚባለው አገዛዝ ለምን እንደዚህ ዐይነቱን የአገዛዝ ስልት ለመከተል እንደተገደደ ለመረዳት ሲሆን፣ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ፣ አገዛዙ በዘመኑ የአዋቀራቸውን የመንግስት አውታሮች፣ የጣለውን ባህልን አፍራሽና ሃሳብን በታኝ የሆኑ በተለያዩ መልክ የሚገለጹ ክስተቶችን በሙሉ ለመመርመርና እነሱን አሰወግዶ ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ የመንግስት አውታር ለመዘርጋትም ነው። ምክንያቱም፣ እንደዚህ ዐይነቱ አገዛዝ የፖለቲካ ስልጣንን መጨበጥ የህብረተሰብን ችግር መፍቻና ሰላምን የሚያሰፍን አድርጎ ከመረዳት ይልቅ የራሱን ጥቅም ተግባራዊ ማድረጊያ መሳሪያ አድርጎ ስለሚወስድ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ የህዝብን አድማስ የሚያጠቡ፣ በማይረቡ ነገሮች ላይ ጭንቅላቱ እንዲጠመድና ርስ በርሱ እየተጠላለፈና እየተጣላ እንዲኖር የሚያደርጉ አልባሌ ነገሮችን በህብረተሰቡ ውስጥ እንዲነዙ ስለሚያደርግ፣ እንደዚህ ዐይነቱን የስልጣኔ ጠንቅ ጥልፍልፍ ሁኔታ መረዳቱ እጅግ አስፈላጊ ነው። ዛሬ በአገራችንም ሆነ በብዙ የሶስተኛው ዓለም አገሮች ያለው ተጨባጭ ሁኔታ የሚያረጋግጠው እነዚህ አገሮች እንደህብረተሰብ ወደማይታዩበት ደረጃ ዝቅ ብለው ማንም የሚፈነጭባቸው ሆነዋል። ቤተሰብ መመስረት፣ አገርን ገንብቶ ለመጭው ትውልድ የሚሆን በጥሩ እሴት ላይ የተመረኮዘ ህብረተሰብና ማህበረሰብ መመስረት የአንድ ህዝብ የኑሮው ዓላማ ሆነው የማይታዩበት ሁኔታ በአገራችንም ሆነ በብዙ የሶስተኛው ዓለም አገሮች በጉልህ ይታያሉ። የዚህ ሁሉ ችግር አንድም፣ ህብረ-ብሄር፣ ህብረተሰብ፣ አጠቃላይ ባህልና ህብረተሰቡን የሚያስተሳስር በሳይንስና በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት አስፈላጊ መሆናቸውን ካለመገንዘብና በጭንቅላት ውስጥ ካለመቋጠር የተነሳ ሲሆን፣ ሌላም የፖለቲካ ትርጉምን በተጣመመ መልክ መረዳትና ህብረተሰብን ማከረባበቻ መሳሪያ አድርጎ በመውሰድ ዘለዓለማዊ ውዝግብ እንዲፈጠር ከማድረግ የመነጨ የተሳሳተ ግንዛቤ ነው። እንደዚህ ዐይነቱ አመለካከት ስልጣንን በጨበጠው ኃይል ብቻ እንደፈሊጥ ተወስዶ ተግባራዊ የሚሆን ነገር ሳይሆን፣ ራሳቸውም ለዲሞክራሲ እንታገላለን የሚሉ ኃይሎችም ከፍተኛ ችግር እንዳለበቻው እንገነዘባለን።  ከመጀመሪያውኑ በግልጽ የማያስቀምጧቸው መሰረታዊ ነገሮች ስለሚኖሩ እንዳጋጣሚ ስልጣን ላይ በሚወጡበት ጊዜ በድሮው መልክ የሚቀጥሉበት ሁኔታ ይታያል። የገቡትን ቃል-ኪዳን ተግባራዊ እንዳያደርጉ ይሳናቸዋል። ዓለም አቀፋዊ በሆኑ ኢንስቲቱሽኖች እየተጠለፉ በራሳቸው ሌላና ውስብስብ ችግር ፈጣሪዎች ይሆናሉ። የመጨረሻ መጨረሻም ጨቋኝና ጦርነት ፈልፋይ ይሆናሉ። የዚህ ሁሉ ችግር ከምን የመነጨ ነው ?

     የአንድን ህብረተሰብ የችግር ምንጭ በቅጡ የመረዳት ችግር !

              አንድን አገዛዝ በድፍኑ ከመወንጀል ይልቅ ለምን ችግር ፈጣሪ ይሆናል?  የሚያስገድዱትስ ነገሮች ምንድናቸው? ብሎ ራስን መጠየቅና መልስ ለመስጠት መሞከር ሁሉም ሊያቀርበው የሚችለው ጥያቄ ባይሆንም፣ አንድ ምሁር ባይነኝ የሚል ሰው ማቅረብ ያለበት ጥያቄና መልስም ለመስጠት መዘጋጀት ያለበት ጉዳይ ነው። በተለያዩ ጊዜ ስልጣን የሚይዙ ኃይሎች የሚሰሩትም ስህተት ሆነ ጥሩ ስራ ከህብረተሰቦቻቸው ዕድገት ሁኔታ ጋር የተያያዘ ነው። ማንኛውም አገዛዝ ከህብረተሰቡ ውስጥ የሚፈልቅ ስለሆነ አስተሳሰቡና ድርጊቱ በህብረተሰቡ የማቴሪያልና የመንፈስ ዕድገት ሁኔታ ሰፋ ባለ ወይም በጠበበ የምሁር መሰረት  መልክ መገኘት የሚወሰን ነው። ማንኛውም አገዛዝ ከጊዜና ከአካባቢ ወይም ከቦታ ውጭ ስለማይታይ አስተሳሰቡና ድርጊቱ በጊዜና በቦታ የሚወሰኑ ናቸው ማለት ነው። ይህም ማለት በአንድ የተወሰነ ወቅት የሚኖረው የምርት ኃይሎች ዕድገትና፣ በምርት ኃይሎች ዕድገት የተነሳ የህብረተሰቡ መተሳሰርና ያለመተሳሰር ጉዳይ በስልጣን ላይ ያለውን ኃይል እንደየሁኔታው እንዲያስብ ወይም እንዳያስብ፣ ጥሩ ስራ እንዲሰራ ወይም ደግሞ ስራው ሁሉ ተንኮል የተሞላበትና ለህብረተሰቡ ደንታ የሌለው እንዲሆን ያስገድደዋል። በዚህ ላይ ለራሱ ለጥቅሙ ሲል የሚታገል የነቃ የህብረተሰብ ክፍል መኖርና ያለመኖር፣ በአገዛዙ ላይ ጫና ማድረግ መቻልና አለመቻል በአንድ የተወሰነ ወቅት ያለን አገዛዝ አስተሳሰብም ሆነ ድርጊት እንደየሁኔታው ይወስናል። ከዚህም ባሻገር፣ ህብረተሰብአዊ መተሳሰር እንዲኖር በየጊዜው ከሁኔታዎች ጋር የሚጓዙ ኢንስቲቱሽኖች መቋቋምና መሻሻል፣ እንዲሁም ደግሞ ኢንስቲቱሽኖች በየጊዜው የሚከሰቱ የህዝብን ችግሮች መፍታት መቻልና አለመቻል በአንድ አገዛዝ አስተሳሰብ ላይ ተፅዕኖ ይኖራቸዋል። በሌላ አነጋገር፣ የአንድን ህብረተሰብ የማቴርያልና የዕውቀት መሰረት ሳያገናዝቡ ዝም ብሎ በጭፍን የሚሰነዘር ውንጀላ አንድን ህብረተሰብ  የዕውነተኛው ነፃነት ባለቤት ሊያደርገው አይችልም።

       ለምሳሌ በጠባብ አመለካከት የተወጠሩ ግለሰቦችም ሆነ ቡድኖች ከመቶና ከሁለት መቶ ዐመታት በፊት ይገዙ የነበሩ የኢትዮጵያን ነገስታትን በጭፍኑ ሲወነጅሉ በጥያቄ መልክ የማያቀርቧቸውና መልስ ለመስጠት የማይችሏቸው መሰረታዊ ጉዳዮች አሉ። በማንኛውም ምሁር ነኝ ባይ መቅረብ ያለባቸው መሰረተ-ሃሳቦች አሉ። ከሁለትና ከሶስት መቶ ዐመታት በፊት የኢትዮጵያ ህዝብ በምን ሁኔታ ውስጥ ይኖር ነበር?  ራሱን ለማሽነፍ ሲል በምን ተግባሮች ላይ ተሰማርቶ ይኖር ነበር?  ርስ በርሱስ እንዴት ይገናኝ ነበር?  ከገዢው መደብና ሌላ ከፍ ብለው ከሚታዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር የነበረውስ ግኑኝነት ምን ይመስል ነበር?  ከተፈጥሮስ ጋር የነበረው ግኑኝነት እንዴት ነበር?  በተፈጥሮ ውስጥ የሚገኙ ነገሮችንስ አውጥቶ ቅርጻቸውን ለውጦ ለመጠቀም የሚመካባቸው መሳሪያዎችስ ምን ይመስሉ ነበር? ህዝቡን ሊያሰተሳስሩ የሚችሉ ልዩ ልዩ ኢንስቲቱሽኖችስ ነበሩ ወይ? ካሉስ ምን ይመስሉ ነበር?  በህብረተሰቡ ላይ የሚኖራቸው አዎንታዊም ሆነ አሉታዊ ተፅዕኖ ምን ይመስል ነበር? እነዚህንና ሌሎች አያሌ ጉዳዮችን የመመርመሩ ጉዳይ በመሰረቱ ቢያንስ ለፖለቲካ ነፃነት እታገላለሁ በሚለው የህብረተሰብ ኃይል ትከሻ ላይ፣ በተለይም ደግሞ በምሁሩ ላይ የወደቀ ጉዳይ ነው።

        ያለፈውን አርባ ዐመት፣ በተለይም ደግሞ የሃያ ዐመቱን ትግል ካለብዙ ጭንቀት ስመረምር የማገኘው ሁለት አጭር መልሶች  ናቸው። አንደኛው፣ የአገራችን ምሁር፣ እኔንም ጨምሮ ጥያቄ የመጠየቅ ባህል የለንም። ሁለተኛ፣ የተለያዩ ህብረተሰቦችን የማነጻጸር(Comparative Studies) ልምድ የለንም፤ ወይም ደግሞ በዚህ ዐይነቱ የአሰራር ስልት በመጠቀም የህብረተሰባችንን ችግር ለመረዳት በፍጹም አንጥርም። እንደሚታወቀው በህብረተሰብ ሳይንስ ውስጥ ሁለት ወይም ከዚያ በላይ የሆኑ ህብረተሰቦችን የማነጻጸሩ ጉዳይ የተለመደ ሳይንሳዊ አሰራር ዘዴ ነው። የለም በዚህ መልክ መስራት አያስፈልገንም፣ እኛ የራሳችን አንድን ህብረተሰብ የምንመረምርበት መሳሪያ አለን ካልን ደግሞ እሱን ውጭ አውጥተን መወያየትና መከራከር አለበን። ወይም ደግሞ የለንም ካልንና አያስፈልገንም ብለን ግትር ያለ አቋም የምንወስድ ከሆነ ለምን ትምህርት ቤት እንደሄድንም ግልጽ አይደለም ማለት ነው። እንደሚታወቀው ማንኛውም ልጅ ትምህርት ቤት የሚላከው እንዲያውቅ፣ አውቆ እንዲመራመርና ትምህርት ቤት የገነባለትን ህዝብ መልሶ በማስተማር ጤናማ ህብረተሰብ ለመመስረት ነው። በመሰረቱ ትምህርት ቤት የሚላክና ከአንድ ዕውቀት ጋር የሚጋጭ ካልተማረው ጋር ሲወዳደር የተሻለ ኢንፎርሜሽን ያለውና፣ የማመዛዘን እንዲሁም ደግሞ አንድን ነገር በቀላሉ በመረዳት ጥያቄ በማንሳት መልስ ለመስጠት የሚችል ነው ተብሎ ይገመታል። ይሁንና ትምህርት ቤት ተልኮ ትምህርቱን ያገባደደ በሙሉ አንድ የህብረተሰቡን ችግር ለመመርመር የሚያስችለውንና፣ ተጨባጭ ሁኔታዎችን በቅጡ እንዲረዳ የሚያደርጉ የመመርመሪያና የመተንተኛ መሳሪያ ቀስሞ ይወጣል ማለት አይደለም። አንዳንዶች ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ እንደተሰጠና(given)፣ መለወጥም እንደሌለበት ተገንዝበው ኑሮአቸውን በዚያው ሲገፉበት፣ ሌላው ደግሞ ፍትሃዊ አስተዳደር ካልሰፈነና ድህነትም ስር የሰደደ ከሆነ ይህ ሁኔታ ለምን እንደተፈጠረ በመመራመር ለለውጥ የሚዘጋጅ አለ።  ከዚህ ባሻገር ግን አንድ ተማርኩ የሚል ግለሰብም ሆነ በቡድን የተደራጀ ከአርቆ አሳቢነት ይልቅ እልከኛና ችግር ፈጣሪ የሚሆንበት ሁኔታም አለ። ስራው ሁሉ ወደ ተንኮልና ህብረተሰብን ማከረባበት ደስ የሚለውና በዚህ እየተዝናና የሚኖር አለ። ይህ ዐይነቱ ኃይል የጭንቅላት ችግር ስላለበት ምክንያቱን በቅጡ ማጥናትና መልስ ለመስጠት መሞከር በተለይም በጭንቅላት ሳይንስ የሰለጠኑ ሰዎች ተግባር ነው። ያም ሆነ ይህ፣ የመማር ትርጉሙ ስልጣኔን ከማምጣት ውጭ መታየት የሌለበት ጉዳይ ስለሆነ፣ ትምህርት ገበያ ላይ ውለው የኋላ ኋላ ስልጣን ሲጨብጡ ችግር ፈጣሪዎች ከሁኑ ለምን እንደዚህ ዐይነት ሁኔታ እንደሚከሰት መመርመር ያስፈልጋል።

       ከላይኛው አጭር ሀተታ በመነሳት ህብረተሰቦችን የማነጻጸሩን ጉዳይ ትንሽ ቢሆንም ቆም ብለን እንመርምር። የዛሬይቱ ኢትዮጵያ አሁን ባለችበት ቅርጽ ከመዋቀሯ በፊት ከመቶ ወይም ከሁለት መቶ ዐመታት በፊት ብቅ ያሉ ነገስታት እንደየሁኔታው ግዛታቸውን ለማስፋፋትና ሌላውን ህዝብ ገባር ለማድረግ በአብዛኛው ይጠቀሙ የነበረው ኃይልን ነበር። ሃይማኖትንም ለማስፋፋት እንደዚሁ ኃይል ወሳኝ ሚናን ተጫውቷል። በህብረተሰብ ታሪክ ውስጥ በአነሳሱ አንድ ቦታ ላይ ረግቶ የኖረ አገዛዝ በፍጹም አለነበረም። አገዛዞች ውስጣዊ-ኃይል ሊያገኙ፣ ሊስፋፉና ሊያድጉ የሚችሉት ከሌሎች ክልሎች ጋር በኃይልም ሆነ በንግድ ወይም ደግሞ በጋብቻ አማካይነት የተጠቃለሉ እንደሆን ብቻ ነው። እንደዚህ ዐይነቱ አገዛዝን የማስፋፋትና የማጠናከር ጉዳይ በተለይም በሮማውያን አገዛዝ ዘመን የነበረና፣ በኋላ ደግሞ ከአስረኛው ክፍለ-ዘመን ጀምሮ ፊዩዳሊዝም ብቅ ሲልና ሲስፋፋ በአውሮፓ ቀሳውስትና ነገስታት ዘንድ የተለመደ ነበር። በተለይም የአውሮፓ ሞናርኪዎች ሃይማኖትን ለማስፋፋት ሲሉ አልቀበላቸውም ያለውን ሁሉ እስከመስቀልና ቋንጃ እስከመቁረጥ የደረሱበት ጊዜ እንደነበር በታሪክ ማህደር ተመዝግቦ ይገኛል። እንደዚሁም ገበሬውን በጉልበት ማስገበርና፣ ከባላባቱ ፈቃድ ሳያገኝ እንዳያገባና ከቦታ ቦታ እንዳይንቀሳቀስ ማድረግ በአውሮፓ ውስጥ የለመደ የአገዛዝ ዘዴ ነበር። ከሌሎች አህጉሮች ይልቅ ህብርተሰብአዊ ግጭቶችና ጦርነቶች በብዛት የተካሄደው በአውሮፓ ምድር ነው። እንደሚባለውና እንደሰማነው ሳይሆን አውሮፓ በደምና በአጥንት የተገነባ አህጉር ነው። በነጻ ገበያ አማካይነት እንዲያው በስምምነት ላይ የተመሰረተና እዚህ የደረሰ አይደለም። በዚያውም መጠንም እንደ አውሮፓው አህጉር ከፍተኛ ምሁራዊ እንቅስቃሴ የተካሄደበት፣ የሳይንስ ግኝቶች የተፈጠረበትና በኋላም  በንግድ መስፋፋትና በዕደ-ጥበብ ማበብ የከበርቴው መደብ ብቅ ያለበት ሌላ አህጉር በፍጹም የለም። ይሁንና ብዙ ዕውቀት ተስፋፍቶም በጦርነት የዘፈቀና በብዙ ሚሊዮኖች የሚቆጠር ህዝብ የተገደለበትና የተሰቃየበት እንደ አውሮፓ አህጉር የመሰለ፣ ሌላ አህጉር በፍጹም የለም ማለት ይቻላል።

        የኢትዮጵያን የህብረተሰብ ታሪክ በአጭሩ ከላይ ከተዘረዘረው የአውሮፓው የህብረተሰብ አገነባብ ሁኔታ ጋር ስናወዳድረው ውሰጥ-ኃይሉ በጣም ደካማ ሆኖ እናገኘዋለን። ይህም የሆነበት ምክንያት ምናልባትም የኢትዮጵያ ህብረተሰብ በጣም ተሰበጣጥሮ የነበረና እንደ ህብረተሰብ ለመገንባትና አንዱ ከሌላኛው ጋር ተፎካካሪ ለመኖር ብዙ መጓዝ ይኖርበት ስለነበር ይሆናል። በተጨማሪም የፊዩዳሉ ስርዓት እንደ አውሮፓው ውስጠ-ኃይል ለማግኘት ከውጭ የሚመጣ አዲስ አስተሳሰብና የአኗኗር ስልት ዕድል አላጋጠመውም። በመሆኑም እንደ አውሮፓው የፊዩዳል አገዛዝ የትላልቅ ቤተክርስቲያናትና የመኖሪያ ቤቶች የመገንባት ዕድል አላጋጠመውም። የህዝቡን አትኩሮና ተሰባስቦ እንዲኖር የሚያደርጉት የመንደር አቆራቆሮች በኢትዮጵያ የፊዩዳል ስርዓት የተለመደ አልነበረም። በተጨማሪም የኢትዮጵያው የግዛት አመሰራረትና መንግስታትን ወደ ታሪካዊ ስራ እንዲያዘነብሉ ለማድረግ የነበረው ምሁራዊ እንቅስቃሴ ከአውሮፓው ጋር ሲወዳደር ምንም አልነበረም ወይም እጅግ በዝቅተኛ ደረጃ የሚገኝ ነበር ብሎ አፍን ሞልቶ መናገር ይቻላል። ለዚህ ደግሞ የክርስትና ሃይማኖት የበላይነትን ይዞ መቆየትና፣ ይህ ርዕዮተ-ዓለም ከፍልስፍና ጋር ለመጋጨት አለመቻልና አለመታደስ የአገዛዙንም ሆነ የህዝቡን አስተሳሰብ ቆልፎ ሊዝይና፣ ወደ ውስጥ ለውጥ እንዳይመጣ አግዷል ማለት ይቻላል። ስለሆነም በአማዛኙ፣ የኢትዮጵያ አገዛዝ ታሪክ በዕደ-ጥበብ ማበብና መስፋፋት፣ በውስጥ ንግድ መዳበር፣ በገንዘብ ልውውጥ አማካይነት ህዝባዊ መተሳሰር መኖርና፣ በመንደሮችና በከተማዎች ቁርቆራ በፍጹም ሊታማ የሚችል አይደለም። እንደዚሁም ኤስቴቲክስና ህዝቡን ከተፈጥሮ ጋር የሚያገናኙትና ተፈጥሮን እየቃኘ ራሱም ፈጣሪም እንዲሆን የሚያስችሉት ዕውቀቶች ሊዘረጉ አልቻሉም።

       በዚህም ምክንያት በተለያዩ የታሪክ ወቅት ብቅ ያሉ አገዛዞችም ሆነ ህዝቡ ችግርን ለመፍታትና መረጋጋትን ለመፍጠር ኃይልን ቢያስቀድሙ በፍጹም የሚያስደንቅ አይደለም። የአስተሳሰብ አድማሳቸውም ውስን ስለነበር በጉልበት የሚይዙትን ግዛቶች በምን መልክ ማዋቀር እንዳለባቸውና፣ ቤተሰብአዊና ህብረተሰብአዊ አገነባቦች አንድ ላይ ተያይዘው መሄድ እንዳለባቸው በቅደም ተከተል መወሰድ ያለባቸውን እርምጃዎች ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችሏቸው የቲዎሪ መሳሪያዎች አልነበራቸውም። በሌላ አነጋገር፣ በየታሪክ ወቅት የተነሱት ነገስታት በህዝብ ላይ ጉዳቶች ቢያደርሱም ሆን ብለውና አውቀው ያደረጉት ጉዳይ አልነበረም። ማንኛውም አገዛዝም ሆነ ግለሰብ ራሱን እስኪያገኝ ድረስና፣ የሚሰራውን ስራ ሁሉ ለማመዛዘንና ወደፊትም ስህተት እንዳይሰራ ብዙ ውጣ ውረዶችን ማለፍ አለበት። ማህበረሰብአዊና ህብረተሰብአዊ ባህርይ ለማግኘት እያንዳንዱ አገዛዝም ሆነ ግለሰብ ጭንቅላቱ በተሻሉና በአዳዲስ ዕውቀቶች መታደስ አለበት። በዚህ  መልክ  የህብረተሰብን አገነባብ ችግርና ውጣ ውረድ ሳያገናዝቡ የዛሪይቱ ኢትዮጵያ በአመጽ ብቻ ነው ልትያያዝና እዚህ ደረጃ ላይ ለመድረስ የቻለችው ብሎ ድርቅ ማለትና፣ በዚህ ዐይነቱ አመለካከት ብዙ ሁኔታዎችን ያላገናዘበ አጻጻፍም ሆነ አነጋገር መሰንዘር አብሮ ለመስራትም ሆነ ወደፊት አገርን ለመገንባት ከመጀመሪያውኑ እንቅፋት ይሆናል። በኛ አገር ብቻ ሳይሆን፣ በየጊዜው መታደስ ካለበት ዕውቀት አለመኖር የተነሳ ህብረተሰብን የሚያመሰቃቅሉ፣ አንድ ህዝብ ዘላለሙን እየከነፈ እንዲሄድ የሚያደርጉና፣ ህብረተሰብንም ሆነ ተፈጥሮን የሚያናጉ ሁኔታዎች በአገራችንም ሆነ በሌሎች የሶስተኛው ዓለም አገሮችም ተስፋፍተው እንደሚገኘ የታወቀ ጉዳይ ነው። የእንደዚህ ዐይነት ታሪክን በዕውቀት መነፅር ለመመርመር ያለመቻል ሁኔታ `ለነፃነታችን` እንታገላለን በሚሉ እንቅስቃሴዎች ብቻ ሳይሆን፣ ራሳቸውም ለኢትየጵያ አንድነት እንታገላለን በሚሉ ኃይሎች ሲስተጋብ ይሰማል። „በዚያች አገር ላይ ብዙ በደል ተፈጽሟል“ ፣ „ከባንዲራው በስተጀርባ ብዙ ደባ ተካሂዷል“ የሚለው በደንብ ያልተጠናና ግንዛቤ ውስጥ ያልገባ አጉል አነጋገር ራሳችንን እንዳንጠይቅና በአዲስ መንፈስ ተነሳስተን አዲስና የተቀደሰ ተግባር እንዳንሰራ የሚያግደን ነው። የአንድን ህብረተሰብ ታሪክ አስቸጋሪና ውስብስብ ጉዞ በደንብ ሳይመረምሩ የተወሰኑ ኃይሎችን ለመሸንገል ሲባል የሚሰነዘሩ አረፍተ-ነገሮችም ሆኑ ፅንሰ-ሃሳቦች ከማንኛውም ምሁራዊ አስተሳሰብ የራቁና ሃላፊነት የጎደላቸው ናቸው። አንድ ህብረተሰብ ዘለዓለሙን እየተፋጠጠና እየተፋጨ እንዲኖር የሚያደርጉ ናቸው። ማንኛውም የዚህም ሆነ የዚያኛው ብሄረሰብ አካል የሆነ ግለሰብ ቁጭ ብሎ እንዲያስብ የሚያደርጉት አይደሉም። ታሪክን እንዳይሰራና፣ ታሪክ ሊሰራ የሚችለው በግለሰቦችና በአንድ ህብረተሰብ ጥረት መሆኑን እንዲገነዘብ የሚያደርጉት አይደሉም። በአጭሩ ይህንንም ሆነ ያንን ብሄረሰብ መሸንገል ለማንም አይጠቅምም።

        ወደ ንዑስ አርዕስቱ ልምጣና፣ እስከዛሬ ድረስ ጠምዶ የያዘንን አባዜ ለመረዳት የእኛንም ሆነ የህብረተሰብአችንን አእምሮ ለስለስ የሚያደርግ፣ በሰፊውና በጥልቀት እንድናስብ፣ እንዲሁም ደግሞ ሎጂክንና ዲያሌክቲክን  የምርምር መሳሪያ ለማድረግ ከመጀመሪያውኑ በህብረተሰብአችን ውስጥ ስላልተስፋፉ እየመላለስን ስህተት እንድንሰራ እንገደዳለን። የህብረተሰብአችንን ችግር ዲሞክራሲ በመኖሩና ባለመኖሩ ብቻ ልንረዳው በፍጹም አንችልም። ምክንያቱም አንድ ሰው ዲሞክራት ከመሆኑ በፊት አእምሮውን ከማንኛውም ዕቡይ ፀባይ፣ ወይንም ኋላ-ቀር  ከሆኑ አስተሳሰቦች  ማጽዳት ስላለበትና፣ ህብረተሰብንም ለመገንባት ቆራጥ እርምጃ መውሰድ ያለበት ጉዳይ ስላለ ነው። ከላይ በተዘዋዋሪም ለማሳየት እንደሞከርኩት፣ ከሪናሳንስና ከዚህ ጋር የተያያዙ ተጨባጭም ሆኑ የሚሰሙ ግን ደግሞ ሊዳሰሱ የማይችሉ ነገሮች በአውሮፓው ምድር ቀስ በቀስ እያሉ ባይስፋፉ ኖሮ ስለ ኤንላይተንሜንት ማውራት በፍጹም አይቻልም ነበር። የኤንላይተንሜንት እንቅስቃሴ ከመኖሩ በፊትና የሰውን ልጅ አስተሳሰብ በአዲስ መልክ ከማዋቀር በፊት ስለሊበራሊዝም ማውራት በፍጹም ባልተቻለ ነበር። ከዚያ በኋላ ልዩ ልዩ የህብረተሰብ ኃይሎች ሲያብቡና እንደ መደብ `ሲደራጁ` ኢንስቲቱሽናዊ የጥገና-ለውጥ እንዲኖር በፍጹም የሞናርኪ አገዛዝ ላይ ግፊት ሲያደርጉ ይህንን መቋቋም ያልቻለው የነገስታት አገዛዝ ሳይወድ በግድ ለአዳዲስ የህብረተሰብ ኃይሎች ቦታውን እንዲለቅ ተገደደ። በዚህ ብቻ አላበቃም። የምዕራብ አውሮፓ አገሮች በህብረ-ብሄር ከተዋቀሩና የኢንዱስትሪ አብዮት ማካሄድ ሲጀምሩ ይህ በራሱ አዳዲስ ተቃዋሚ ኃይሎችን ማፍራት ጀመረ። በኢንዱስትሪ አብዮት የተነሳ ከተማዎች በህዝብ ብዛት ጥቅጥቅ ማለት ሲጀምሩ፣ ይህ ሁኔታ የሶሻል ጥያቄዎችን አስነሳ። በአንድ በኩል የድሮውን ስርዓት የሚናፍቁ፣ ዕድገት ሲባል ተፈጥሮን የሚቀናቀን መሆን እንደሌለበት የሚያመለክቱ፣ በሌላ ወገን ደግሞ ከመሬት ተፈናቅሎ ወደ ኢንዱስትሪ ሰራተኛነት የተለወጠውና ከማሽን ጋር መታገል የጀመረው ጥያቄዎችን ማንሳት ጀመሩ። አዲሱ የከበርቴ መደብ በቀላሉ ዝም ብሎ በፋብሪካው ውስጥ ተቀጥሮ የሚሰራውን ወዝአደር መበዝበዝ እንደማይችል ትግል ጀመሩ።በዚህ መልክ እየተስፋፋና ስር እየሰደደ የመጣው ትግል ይበልጥ የምሁራዊነት ባህርይ በመያዝ ህብረተሰብ በሌላ መልክም መደራጀት እንዳለበት አመለከቱ። በአጭሩ በዚህ መልክ ነው በአውሮፓው ማህብረሰብ ውስጥ ችግሮች ብቅ ሲሉ እነሱን ሳይሸሹ በመመርመርና አማራጭ በማቅረብ አገርን መገንባት የተያያዘው። ይህ ዐይነቱ ህብረተሰብአዊ እንቅስቃሴ ከሁለት መቶ ዐመታት በኋላም በሌላ መልኩ ተከስቷል። ከሰላሳ ዐመታት በላይ ጀምሮ በብዙ አንዳንድ የአውሮፓ አገሮች በሌላ መልክ እየተደገመ ነው። የግሪን/አረንጓዴው/ ፓርቲ እንቅስቃሴ ከሰላሳ ዐመት በፊት የማይታሰበውን ያህል ዛሬ ራሱን የቻለ ኃይል ሆኖ ተደላድሎ ይገኛል። በህብረተሰብ ውስጥም ስር የሰደደ ነው። ዛሬ ደግሞ የፒራተሪ ፓርቲ በየቦታው ብቅ በማለትና በመደራጀት ወደፊት ሊታለፍ የማይችል ኃይል እየሆነ በመምጣት ላይ ነው። ይህ ሁሉ በትግል የሚገኝ ነው። ምንግዜም የጭንቅላትን ስራ በማስቀደም ነው። ምንጊዜም ቢሆን ከአመፅ ይልቅ ህብረተሰብአዊ ችግሮችን ለመፍታት ዕውቀትን ማስቀደምና እንደህብረተሰብአዊ ኃይል ሆኖ ለመውጣት በብቃት በመደራጀት ነው። በራስ ላይ ከፍተኛ ዕምነትን በማሳደር ነው። ዲሞክራሲ ከላይ ወደታች በአንድ የገዢ ኃይል የተወረወረበት የታሪክ ወቅት አልነበረም። ሀቀኛ ዲሞክራሲ በአመጽ የሚገኝ ሳይሆን በከፍተኛ ምሁራዊ እንቅስቃሴ በመታገዝና ግፊት በማድረግ ብቻ ነው። እዚህ ላይ የተለያዩ የዲሞክራሲ ዐይነቶችን ሳናገናዝብ ማለት ነው።

        ያም ሆነ ይህ አፄ ኃይለስላሴ ስልጣን እስከያዙ ድረስ የነበረውን የአገራችንን  ሁኔታ ስንመረምር -የአፄ ምኒልክን የዘመናዊነት ፖሊሲ ወደ ጎን በመተተው- እስከዚያን ጊዜ ዘመን ድረስ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ በአማዛኙ አስተሳሰቡን ወጥረው በያዙ በግብርና ኢኮኖሚና፣ በርዕዮተ-ዓለም ደረጃ ደግሞ በክርስትናና በእስላም ሃይማኖት ይተዳደር ነበር። በፊዩዳሉ ኢኮኖሚ በአንድ በኩል፣ በሌላ ወገን ደግሞ እዚህና እዚያ ተሰበጣጥረው በሚገኙ ሌሎች ምርታዊ ክንውኖችና በከብት እርባታ መሀከል የተቆላለፈ ግኑኝነት የተነሳ የምርት ሃይሎች ሊያድጉ አልቻሉም። በዚህ ላይ የክርስትና ሃይማኖት ከሌሎች ሃይማኖት ነክ ካልሆኑ አምልኮቶች ጋር በመቆላለፍ የህዝባችንን የማሰብ ኃይል ይወስን ነበር። ይህም ማለት በእንደዚህ ዐይነት የኑሮ ሁኔታ ውስጥ የሚገኝ ህብረተሰብ ከውስጥ የአእምሮ ተሀድሶ ካላደረገና፣ የአሰራርና የአኗኗር ዘዴውን እንዲለውጥ የሚያስችሉትን የቴክኖሎጂ መሻሻል እስካላደረገ ድረስ ኑሮው ተደጋጋሚና አሰልቺ ከመሆን አልፎ በቀላሉ ለማንኛውም አደጋ የሚጋለጥ ይሆናል። በተለያየ ጊዜያት ባወጣሁት ጽሁፍ እንዳመለከትኩት በተፈጥሮ ሳይንስ፣ በተለይም በአስትሮኖሚ ግኝት አማካይነት ነው በአውሮፓ ምድር የካቶሊክ ሃይማኖት የበላይነቱን ሊነጠቅ የቻለው። በአገራችን ግን ይህ ዐይነቱ ምርምርና መጋፈጥ ባለመኖሩ ነው ነገሮች ሁሉ በሃይማኖትና በፊዩዳላዊ መነጽር አመለካከት መታየት የቻሉት። ትላንትም ዛሬ አስተሳሰባችን፣ አጻጻፋችንና ነገሮችን መገምገም፣ እንዲሁም አንድ ሰው ለየት ያለ አስተሳሰብ ይዞ ሲወጣ ሽምቅቅ ማለት የሚያረጋግጠው የቱን ያህል ነገሮችን በድሮው ዐይነት እንደምንመለከት፣ እንደምናስብና እንደምንረዳ ነው። በተጨማሪም ይህ የሚያረጋግጠው የቱን ያህል የባህል ተሃድሶ እንዳላደረግንና ለማድረግም ዝግጁ እንዳልሆን ነው።

ዘመናዊነት (Modernization) ያመጣው ጠንቅ !

      በመጀመሪያ ደረጃ በአንዳንድ ኢትዮጵያውያን ጸሀፊዎች ዘመናዊነት የሚለው ጽንሰ-ሃሳብ በተሳሳተ መልክ ይቀርባል። በህብረተሰብ ታሪክ ውስጥ ለውጥና(Transformation) ዘመናዊነት የነበሩ ነበሩ። ለመጀመሪያ ጊዜ ተራማጅ ወይም የህብረተሰብን ለውጥ አርማ ይዘው የተነሱ የግሪኩ ሶፊስቶች(Sophists) ናቸው። በሁለተኛ ጊዜ፣ ከፍተኛ ህብረተሰብአዊ ለውጥና ዘመናዊነት በሬናሳንስ አማካይነት ነው ሊገኝ የቻለው። ከዚህ ስንነሳ ዘመናዊነትና ህብረተሰብአዊ ለውጦች፣ -ህብረተሰቦች በዚያው ረግተው ይቁሙ ካልተባሉ በስተቀር- የታሪክ ግዴታና አስፈላጊም ናቸው። አስፈላጊነታቸውም፣ አንድም፣ የሰው ልጅ የማሰብ ኃይል ስላለውና ለውጥን ሰለሚፈልግ፣ ሌላም በለውጥ አማካይነት ብቻ በቁጥር እያደገና እየጨመረ  የሚመጣውን ህዝብና ፍላጎቱን ማሰተናገድና ማሟላት ስላለበት ነው። በጥንታዊ ባህላዊ ኖርሞች የተጠመደ ህብረተሰብ አዳዲስ ችግሮች ሲፈጠሩ ጥያቄ ለማንሳትና መልስ ለመስጠት ይቸግረዋል። ስለዚህም አንዳንድ የነቁ ግለሰቦች ለችግሩ መፍትሄ ለመስጠት ደጋግሞ በመጠየቅ ችግሩ የሚፈታበትን መንገድ ይጠቁማሉ። ከተለያዩ ምሁሮች የተለያዩ አስተሰሳቦች በመፍለቅ ምሁራዊ ትግል ይደረጋል። ቀስ በቀስም እንደ ኃይሎች አሰላለፍ አንደኛው አስተሳሰብ በማሸነፍ የለውጡ መንገድ ይዘጋጃል ማለት ነው። በዚህም ምክንያት በአውሮፓ ምድር ውስጥ ከአስተሮኖሚና ከሌሎች ሳይንሳዊ ግኝቶች፣ የፍልስፋና ምርምር መስፋፋት፣ የግጥምና የሊትሬቸር ማበብ፣ እንዲሁም የክላሲካል ሙዚቃና በተወሰነ የጂኦሜትሪ ቅርጽ የቤት አሰራርንና ልዩ ልዩ የመናፈሻ ቦታዎችን መስራትና ህዝብን በአንድ የተወሰነና ስርዓት ባለው መልክ እንዲሰበሰብ ማድረግ ልዩ ዐይነት ዘመናዊነት ነው። አንድ ህብረተሰብ ካለሳይንስና ካለቴክኖሎጂ አብዮትና እንዲሁም ጭንቅላትን በሚያድስ ዕውቀት ለውጥ ካላመጣ ወደ መተረማመስና ወደ መከረባበት ያመራል። ስራው ሁሉ ጦርነት ይሆናል። ስርዓት ያለው ኑሮ ለመገንባት በፍጹም አይችልም። በውጭ ኃይሎች በቀላሉ ይጠቃል። ስለዚህም ስለዘመናዊነትና ስለህብረተሰብአዊ ለውጥ በምናውራበት ጊዜ ነገሩን ሰፋ አድርገን መመልከት ይኖርብናል።

       ከ1940ዎቹ መጨረሻ ጀምሮ በተለይም በአሜሪካን ሶስዮሎጂስቶችና ኢኮኖሚስቶች ለሶስተኛው ዓለም አገሮች ተብሎ የተዋቀረውን የሞደርናይዜሽን ፕሮግራም ጠጋ ብለን ስንመለከት ግን የየአገሮችን ልዩ ልዩ ልምዶችና የአኗኗር ስልቶች በማጥናትና ከዚያ በመነሳት የተነደፈ ፕሮግራም ሳይሆን፣ በተለይም የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝምን ተፅዕኖ ከማስፋፋት ጋር የተያያዘ፣ ሁለ-ገብ ሳይሆን የተወሰነ ህብረተሰብን ክፍል ለመጥቀምና፣ በዚያ አማካይነት ስር-ነቀል ዕድገት እንዳይኖር የታቀደ ልዩ ሴራ ነው ማለት ይቻላል። ይህ በተወሰኑ የአሜሪካን ሶስዮሎጂስቶች የዳበረው አስተሳሰብ በመሰረቱ ኤምፔሪሲዝም በሚባለው በቀጥታ በሚታዩ ነገሮች ላይ የተመሰረተ አስተሳሰብ ሲሆን፣ ከዚያ ተሻግሮ በመሄድ በአንድ ህብረተሰብ ውስጥ የሰፈነውን የኃይል አሰላለፍ፣ የፖለቲካና የመንግስት አወቃቀር፣ የምርት ኃይሎች ዕድገትንና የምርት ግኑኝነትን ሁኔታና፣ እነዚህ ነገሮች አንድ ላይ በመያያዝና በመጣመር በአጠቃላይ ህብረተሰብአዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ላይ ስለሚኖራቸው አሉታዊ ተፅዕኖ ወደ ውስጥ በመግባት አይመረምርም። የአንድን ህብረተሰብ አወቃቀር በዘመናዊነትና በኋላቀርነት በመክፈልና፣ ከዚህ በመነሳት ያለውን የኢኮኖሚ ዕድገት ችግር በልዩ የምዕራቡ የፍጆታ አጠቃቀምና የተወሰነ አሰራር ስልት ለመቅረፍ እንደሚቻል ያመለክታል።

        እነዚህ ሶስይሎጂስቶች ይህንን አመለካከት በብዙ የሶስተኛው ዓለም አገሮች ሲያስፋፉና ተቀባይነት እንዲኖረው ሲያደርጉ፣ በቲዎሪያቸው ውስጥ ያላከተቷቸው ለዕውነተኛ ነጻነት ጠቃሚና ለኢኮኖሚ ዕድገት የሚሆኑ ሌሎች ብዙ መሰረተ-ሃሳቦችና ልምዶችን ከቁጥር ውስጥ አላስገቡም። በመጀመሪያ ደረጃ፣ በእነ ሶክራተስና ፕላቶ የዳበረውን፣ ዕውቀት ሊፈልቅ የሚችለው ከሚታዩ ነገሮች ሳይሆን በማሰብ ኃይልና ከተጨባጭ ሁኔታዎች ርቆ በመሄድ ነው የሚለውን ከቁጥር ውስጥ አላስገቡም። ከዚህ ጋር ተያይዞ፣ የተሳሳተ አመለካከትና በተሳሳተ አመለካከት ላይ የተገነባ አስተዳደር ሊያስከትል የሚችለውን ዕኩልነትን የሚጻረርና የየግለሰቦችን ዕውነተኛ ነፃነት የሚገፍና ለገዢዎች የሚያመችን ትምህርትና ርዕዮተ-ዓለም አልመረመሩም። በሁለተኛ ደረጃ፣ ብዙ የምዕራብ አውሮፓ አገሮች እንደ ህብረ-ብሄር መንግስታት ባለተዋቀሩበትና፣ አገሮች በክልል ባልተወሰኑበት በጨለማው ዘመን ይገኙ የነበሩበትን ሁኔታና፣ ከዚያ ለመውጣት ሲሉ የግዴታ በሬናሳንስ አማካይነት መውሰድ የተገደዱትን ሁለ-ገብ የግንባታ ስትራቴጂ በፍጹም አላጤኑም። በሶስተኛ ደረጃ፣ አንዳንድ የአውሮፓ መንግስታት እንደ ህብረ-ብሄር ከተቋቋሙ ከ16ኛው ክፍለ-ዘመን ጀምሮ ተግባራዊ ያደረጉትን የመርካንትሊስት ሁለ-ገብ የማኑፋክቱር፣ የከተማዎችና የካናል ሲይስተም ግንባታዎችን በፍጹም አላገናዘቡም። በአራተኛ ደረጃ፣ ሌሎችን ነገሮች ሁሉ ትተን፣ ብዙ የምዕራብ አውሮፓ መንግስታት በሁለተኛው ዓለም ጦርነት የተነሳ ኢኮኖሚያቸው ከተከሰከሰ በኋላ እንደገና መልሰው ለመገንባት የወሰዱትን በመንግስት የተቀነባበረና የተደገፈ ሁለ-ገብ የኢኮኖሚ ፖሊሲና ልምድ ዘመናዊ ብለው ከሚጠሩት ለሶስተኛው ዓለም በተዘጋጀው ቲዎሪያቸው ውስጥ በፍጹም አላካተቱም። የነዚህ የዘመናዊ ቲዎሪ አራማጆች ዋና ዓላማ ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት በኋላ የተቋቋመውን የኃይል አሰላለፍና ይሰበክ የነበረውን የነፃ ንግድና ገበያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ ሲሆን፣ በዚያውም በተለይም የአሜሪካንን የበላይነት በየቦታው ለማረጋገጥና በየአገሮቹ ውስጥ ዕውነተኛ የሆነ  ሁለገብ የኢንዱስትሪ አብዮት እንዳይመጣ ከመጀመሪያውኑ መሰናክል ማዘጋጀት ነበር። ስለሆነም በአሜሪካንና በተቀረው የምዕራብ አውሮፓ ካፒታሊዝም ግፊትና የበላይነት የተነሳ በብዙ የሶስተኛው ዓለም አገሮች ሸቀጦችን እያመጡ በየአገሩ ገበያ ላይ የሚያራግፍ  የነጋዴ የህብረተሰብ ክፍል እንዲፈጠር ሁኔታውን አመቻቹ። ዕድገቱና አስተሳሰቡ በዚያው ብቻ እንዲቀር ሆኖ ተዘጋጀ። ሰፋ ያለ ምሁራዊ እንቅስቃሴና በባህል የተገነባ የከበርቴ መደብ እንዳይፈጠር መሰናክል ደቀኑ። በህብረተሰብ ግንባታ ታሪክ ውስጥ እንደተረጋገጠው ሰፋ ባለ የኢንዱስትሪ አብዮት አማካይነት ብቻ ነው በሁሉም አቅጣጫ የሚያስብ ምሁራዊ እንቅስቃሴ ሊዳብርና፣ ፈጣሪና ተወዳዳሪ የሆነ የከበርቴ መደብ ደግሞ መፈጠር የሚችለው።

         ከዚህም ሌላ ይህ ዐይነቱ በውስን የካፒታሊዝም ሎጂክ ላይ የተመሰረተውና ለሶስተኛው ዓለም ተብሎ የተዘጋጀው የሸቀጣ ሸቀጥ ኢኮኖሚ ተግባራዊ እንዲሆንና ሁለ-ገብ ህብረተሰብአዊ ዕድገት እንዳይካሄድ የመንግስት መኪናም ዘመናዊ በሚል ሽፋን ስር መዋቀር ነበረበት። ስለሆነም ቢሮክራሲያዊ መዋቅሩና ሌሎች የመንግስት መኪናዎች በአንድ በኩል አዲሱን ኤሊት እንዲጠብቁና እንዲከላከሉ ሆነው ሲዋቀሩ፣ በሌላ ወገን ደግሞ በተለይም ለአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ሰርጎ ለመግባት እንዲያመቹ ሆነው ተዘጋጁ። ምክንያቱም ቀላል ነው፤ ማንኛውንም ህብረተሰብዊ እንቅስቃሴና ለለውጥ የሚደረግ ትግልን በእንደዚሁ ዐይነቱ የመንግስት መኪና ነው ማኮላሸት የሚቻለው። ስለዚህም አገርን ለመጠበቅ ተብሎ የተዋቀረው የሲቪልና የሚሊተሪ እንዲሁም የደህንነት ቢሮክራሲ በመሰረቱ የአገዛዙንና የውጭ ኃይሎችን ጥቅም የሚያስጠብቅ እንጂ ለህብረተሰቡ አጠቃላይ ዕድገት እንዲያመች ሆኖ የህብረተሰቡን ፍላጎት በማካተት ከታች ወደ ላይ የተደራጀ አይደለም። ከታች ወደ ላይ ሰፋ ካለ ምሁራዊ እንቅስቃሴ ጋር እየተነፃፀረ ያልተዋቀረ በመሆኑ በንቃተ-ህሊናው ደካማነት አንድ ዐይነት ህዝባዊ እንቅስቃሴ በሚነሳበት ወቅት ወደ ጨፍጫፊነት ይቀየራል። በተለይም አንድ ወጥ አገዛዝ በሰፈነበትና የተደራጀ የሲቪክ ማህበር በሌለበት ህብረተሰብ ውስጥ በአሜሪካን ሎጂክ የተዋቀረ የሲቪሊና የሚሊታሪ ቢሮክራሲ ወደ ፋሺሽትነት ይለወጣል ማለት ነው። ይህ ዐይነቱ ሁኔታ በብዙ የላቲናን የአፍርካ አገሮች ታይቷል። ከዚህም ባሻገር ይህ ዐይነቱ የመንግስት ቢሮክራሲ ከኢኮኖሚው መሰረትና ስፋት ጋር እየተነፃፀረ የተዋቀረ ባለመሆኑ ህብረተሰብአዊ ሀብትን መጣጭ ነው። እንደሚታወቀው አንድ አገር የራሷ የመሳሪያ ኢንዱስትሪ ከሌላትና፣ መሳሪያ ከውጭ የምታስመጣ ከሆነ የአገር ውስጥ ሀብት ወደ ውጭ ይፈሳል። ከዚህም ባሻገር ለመሳሪያ ግዢ የሚወጣ ወጪ ምርታማ ስላልሆነና የምጣኔ ሀብትን ስለሚጋራ በኢኮኖሚው ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ይኖረዋል ። በዚህ መልክ የአሜሪካንን ጥቅም ለማስፋፋት ሲባል የተኮተኮተውና የተጠናከረው የመንግስት የመጨቆኛ መሳሪያና ቢሮክራሲ አገርን ለመግንባት ማገልገያ ከመሆን ይልቅ ከረዥም ጊዜ አንፃር ጦርነትን ፈልፋይ እንዲሆን ተደርጓል። የመንግስት ሚና ወደ መጨቆኛ መሳሪያነት ተቀንሶ እንዲታይ በመደረጉ፣ ከውጭ ትዕዛዝ ተቀባይና ጦርነትን የሚያካሂድ እንዲሆን ተደርጓል። በዚህም የተነሳ መንግስታዊ ፖሊሲዎች አጠቃላይ ህብረተሰብአዊ ዕድገትን ከማምጣት ይልቅ ሀብት አባካኝ በመሆን ህብረተሰቡ ስርዓትና ዓላማ ይዞ ኑሮውን እንዳይመራ አግደውታል።

      በመሆኑም የተወሰነው ተማረ የሚባለው የህብረተሰብ ክፍልና መንግስታት የተወሳሰበውን የካፒታሊዝምን ዕድገትና የልዩ ልዩ ኢንስቲቱሽኖችን የሻጥር አሰራር ጠጋ ብለው ለመመርመር ባለመቻል በየታሪክ ወቅት ብቅ ያሉትን አወናባጅ የኢኮኖሚ ፖሊሲዎች በማስተጋባትና ተግባራዊ በማድረግ ለብዙ ሚሊዮን ህዝቦች መሞትና መሰቃየት እንዲሁም መሰደድ ምክንያት ሊሆኑ በቅተዋል። በተጨማሪም የመንግስት መኪናውና ቢሮክራሲው ለውጭ ሰላዮች ክፍት በመሆን አንድ አገዛዝ ማድረግ ያለበትን ህብረተሰብአዊና የአገር ግንባታ ተግባር እንዳያካሂዱ ታግደዋል። በዚህም ምክንያት በተለይም አብዛኛዎቹ የአፍሪካ መንግስታት የዚኽኛው ወይም የዚያኛው የውጭ ኃይል ተቀጥያ በመሆንና፣ በሚያስፈልግበትም ጊዜ የመንግስት ግልበጣ የሚካሄድባቸው መድረኮች  በመሆን የታሪክ ግዴታቸውን እንዳይወጡ ተደርገዋል። መረጋጋት የማይታይባቸውና፣ እንዲያውም ለታዳጊ ትውልድ መጥፎ ምሳሌ በመሆን የአገርንና የህብረተሰብን ትርጉም በማበላሸት የሰው ልጅ ማድረግ ያለበትን ታሪካዊ ስራ እንዳይሰራ በቀጥታ እንቅፋት ሆነዋል። በሳይንስና በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ ሰፊ ገበያና ሰፋ ያለ ህብረተሰብአዊና ባህላዊ እንቅስቃሴ እንዳይካሄድና እንዳይዳብር መሰናክል ሆነዋል። ይህ ዐይነቱ አሰራር እንደተፈጥሮ ህግ ተደርጎ በመወሰዱ የአገዛዝ ለውጥ በሚደረግበት ጊዜ ሁኔታው በድሮው መልክ ይቀጥላል። በተጨማሪም ስለመንግስት ምንነትና ሚና በቲዎሪ ደረጃ እንደ አውሮፓው ምሁራን በሰፊው ውይይትና ክርክር ስለማይካሄድ ስለመንግስት የሚኖር ግንዛቤ ተዳፍኖ እንዲቀር ይደረጋል። በተለይም ከውጭ በሚናፈስ የተሳሳተና ከሳይንስ ጋር የማይጣጣም ጥራዝ ነጠቅ አባባል በመወናበድና መንግስትን እንደ አምላክ በመቁጠር፣ አባዛኛዎች ምሁራን ስለመንግስት ምንነት እንዳይጠይቁ ታግደዋል። የአውሮፓን ምሁራንን ከኛ ጋር ሲነፃፀሩ የሚለያቸው፣ ስለመንግስትም ሆነ ስለግለሰብ ሚና፣ እንዲሁም ስለህብረተሰብ ዕድገት ያላቸው ግንዛቤ  በጣም ይለያል። ይህንን ለመረዳት አሁንም በአናሎጊ እንመልከት።

        በአውሮፓ ምድር ውስጥ የመንግስት ሚና በብዙ መልክ ተገልጿል። ከእነሶክራተስ/ፕላቶንና እስከሬናሳንስ ድረስ የነበረው የመንግስት ግንዛቤ፣ መንግስት የአንድን የህብረተሰብ ኃይል ጥቅም ብቻ አስጣባቂ ሳይሆን የሁሉንም ህብረተሰብ ክፍል ጥቅም አስጠባቂ መሆን አለበት የሚል ነበር። በፕላቶን ዕምነት ፖለቲካና ስነ-ምግባር በአንድነት በመጣመር ለአንድ አገዛዝ የህዝብን ርዕይ ተግባራዊ እንዲያደርግ በር ይከፍቱለታል። ስለሆነም በዚህ የአስተሳሰብ ክልል ውስጥ ያልተደራጀ የመንግስት መኪናና አገዛዝ አድልዎን የሚያስፋፋና ቀስ በቀስም ወደ ዘራፊነት የሚያመራ ይሆናል። ይህ ከሆነ ደግሞ የህብረተሰብ ኖርም በመናጋት አንድ ህዝብ ስርዓትና ጥበብ ያለው ኑሮ ሊገነባና፣ በሰላምና በመከባበር ሊኖር አይችልም። የጀርመንን ክላሲኮችም ይህንን መሰረት በማድረግ ጥበባዊ መንግስት በምን መልክ መዋቀር እንዳለበትና ተግባሩስ ምን መሆን እንዳለበት በሰፊው ጽፈዋል። ካፒታሊዝም በአሸናፊነት ከወጣ ከ18ኛው ክፍለ-ዘመን ጀምሮ ግን የመንግስት ሚናና ትርጉም እነ ፕላቶን በፈለጉትና ትክክል ነው ባሉት መስመር ሊዋቀር አልቻለም። በተለይም የሊበራሊዝም አስተሳሰብ ሲስፋፋ የእነ ፕላቶንና የሌሎች ክላሲኮች የመንግስት ቲዎሪ እየተገፈተረ በአዲሱ የኃይል አሰላለፍ ፍላጎት ሊዋቀር ቻለ። ይሁንና ግን በሊበራሎች ዕምነት መንግስት የአንድን ህብረተሰብ ክፍል ብቻ ጥቅም አስጠባቂ ሳይሆን እንደሪፌሪ ነው። መንግስት የህግ የበላይነት እንዲከብር የሚያደርግ እንጂ አድልዎ የሚያደርግ አይደለም ይሉናል። በሊበራሎች ዕምነት እያንዳንዱ አገር እንደ ህብረተሰብ የሚታይ አይደለም። አንድ አገር ግለሰቦች የየራሳቸውን ጥቅም፣ ካፒታሊስቱ ትርፍን፣ ሰራተኛው ደግሞ ገቢውን ከፍ ለማድረግ የሚታገሉበት መድረክ ነው። የእያንዳንዱ ግለሰብ አርቆ አስተዋይነት በራሱ የጥቅም ዙሪያ ብቻ የሚሽከረከር እንጂ ከጠቅላላው የህብረተሰብ ጥቅም ጋር የሚያያዝ አይደለም። በመሆኑም የሰው ልጅ ማህበራዊና ህብረተሰብአዊ አይደለም የሚል አደገኛ አመለካከት ያስፋፋሉ። ይህ አመለካከታቸው ተጨባጩን የህብረተሰብ ዕድገት ታሪክ፣ በተለይም ደግሞ የካፒታሊስትን ህብረተሰብ ተጨባጭ ሁኔታ ይጻረራል። መንግስትም ሪፌሪ ሳይሆን የካፒታሊዝምን ዕድገትና መስፋፋት እንዲሁም የቴክኖሎጂ ምጥቀትን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚደግፍና የሚያግዝ ነው። ስለሆነም እንደየሁኔታው በተለያየ መልክ የሚገለጸውን የከበርቴ መደብ በመደገፍና በመደጎም በአሸናፊነት እንዲወጣና በዓለም ገበያ ላይም ተወዳዳሪ እንዲሆን የሚያደርግ ነው። በተጨማሪም የውስጥ ገበያ እንዲስፋፋ የከተማዎችን ዕድገት በማፋጠንና በልዩ ልዩ የመገናኛ ዘዴዎች እንዲተሳሰሩ በማድረግ የካፒታልንና የሌሎች ሀብቶችን ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ በፍጥነት እንዲሽከረከሩ ያግዛል። በሌላ አነጋገር የመንግስት ፖሊሲዎች በሙሉ ከቴክኖሎጂው ፍጥነት ጋር የሚጓዙ ብቻ ሳይሆኑ፣ መንግስት ራሱ በሁሉም አቅጣጫዎች ንቁ ፖሊሲዎችን ተግባራዊ በማድረግ ለአጠቃላይ ህብረተሰብአዊ ሀብት መፈጠር ዐይነተኛ መሳሪያ ሊሆን ችሏል። በሌላ ወገን ግን በየጊዜው ብቅ በሚሉ አዳዲስ የነቁና ህብረተሰብአዊ ኃላፊነት በሚሰማቸው ኃይሎች የተነሳ  የካፒታሊስት መንግስት የአንድን ህብረተሰብ ክፍል ጥቅም ብቻ አስጠባቂ እንዳይሆን የሚታገድበትም ጊዜ አለ። ስለዚህም የተቀረውም የህብረተሰብ ክፍል ተጠቃሚ እንዲሆንና ህብረተሰብአዊ ሚዛን እንዳይናጋ በማሰብ በልዩ ልዩ የኢኮኖሚ መሳሪያዎች የሶሻል መስክንና የባህልን እንቅሳቃሴ ይደጉማል። በዚህ መልክ ገንዘብ በኢኮኖሚው ውስጥ እንዲገባ በማድረግ የዕቃዎችንና የአገልግሎትን በፍጥነት መሽከርከር በተዘዋዋሪ ያግዛል ማለት ነው። ይህ ዐይነቱ ድጎማና በሶሻል መስክ ውስጥ መሳተፍ እንደ ኃይል አሰላለፉ ተለዋዋጭ ነው። በአጠቃላይ ሲታይ ግን የመንግስት በልዩ ልዩ የኢኮኖሚ ዘርፎችና በባህል እንቅስቃሴ ውስጥ ተሳትፎ ማድረግ የባህል ዕድገት ነፅብራቅ እንደሆነ መገንዘብ እንችላለን። ከጭንቅላት ተሃድሶ ጋር የተያያዘ ነው። የህብረተሰብንና የአገርን ትርጉም በሚገባ ከመረዳት ጋር የተያያዘና፣ በዚህም አማካይነት ብቻ አንድ ህብረ-ብሄር በቋሚ መሰረት ላይ ጸንቶ ሊቆይ ይችላል ብሎ በማመንም የሚደረግ ንቁ ተሳትፎ ነው። ይህ አመለካከት ከአሜሪካን ይልቅ  በምዕራብ አውሮፓ ውስጥ ከፍተኛ ተቀባይነት ያለውና እንደ ባህል የሚታይ ነው። ይሁንና ግን በጥልቅ ሲመረመር፣ በተለይም ባለፉት ሰላሳ ዐመታት የካፒታሊስት መንግስታት በአጠቃላይ ሲወሰዱ በተለያዩ የፊናንስና የቀረጥ ፖሊሲዎች አማካይነት ሀብትን ከዝቅተኛው የህብረተሰብ ክፍል ወደ ከፍተኛው በማስተላለፍ ሀብታሙን የበለጠ ሀብታም አድርገውታል። በሁሉም አገሮች ህብረተሰብአዊ መዛባቶች በመከሰታቸው፣ በተለይም ለቀኝ ኃይሎች አመቺ ሁኔታዎች በመፈጠር ጥላቻ እየተስፋፋ ነው።

         ስለሆነም በአገራችንም ሆነ በብዙ የሶስተኛው ዓለም አገሮች በተፈጠረው ያለተስተካከለ ዕውቀትና ህብረተሰብአዊ ተሃድሶ አለመኖር የተነሳ፣ በአንድ በኩል የመንግስት ሚና ሊጣመም ችሏል፤ ድርጊቱ ሁሉ ወደ ጦርነት ተቀንሷል፤ በሌላ ወገን ደግሞ በተሳሳተ ፖሊሲ በመጠመዘዝና በመመራት ህብረተሰብአዊና የአካባቢ መዛባት ሊፈጠር ችሏል። በአገራችንም ሆነ በሌሎች የሶስተኛው ዓለም አገሮች በየጊዜው ስልጣንን የሚጨብጡትን የዕውቀት ደረጃ ስንመለከት ይህንን ሁሉ ችግር ለማየት የማይችሉ ብቻ ሳይሆኑ፣ ከውጭ ኃይሎች ጋር በመመሰጣጠር የባሰ ችግርን በመፍጠር ችግሮች እንዲደራረቡ የሚያደርጉ ሆነዋል። ከዚህ ሁኔታ ብቻ በመነሳት ነው ከ1950 ዓ.ም መጀመሪያ ጀምሮ በአገራችን ምድር የተፈጠረውን ሁኔታና እዚህና እዚያ ብቅ ያሉትን የህብረተሰብ ኃይሎች አስተሳሰብና ድርጊታቸውን መረዳት የምንችለው።

        አብዛኛውን ጊዜ በዘልማድ አነጋገር አፄ ኃይለስላሴ ዘመናዊነትን ያስገቡና ኢትዮጵያን ከዘመናዊ ቴክኖሎጂ ጋር ያስተዋወቁ መሪ ናቸው እየተባለ ይነገራል። ይህ ዐይነቱ አነጋገር የናፍቆት ይሁን የሌላ አመለካከት እየተመላለሰ ሲስተጋባ ይሰማል። የዚህ ሁሉ ችግር አሁንም ቢሆን የኢትዮጵያን ዕድገት በየኢፖኩ እየወሰዱ ከህብረተሰብ ሳይንስና(Sociology) ከፍልስፍና፣ እንዲሁም ከሳይኮሎጂ አንጻር የሚመረምሩ ምሁራን ፍላጎት አለመኖር ነው። የብዙዎቻችን አጠቃላይ ዕውቀት(Generalist) የነገሮችን ዕድገት በተናጠል እየወሰድን እንዳንመረምርና እንዳንመዘግብ አግዶናል። በተጨማሪም ያለን ህብረተሰብአዊ ኃላፊነትና ንቃተ-ህሊና ደካማ በመሆኑ የአገዛዙን ድክመትና የህብረተሰብአችንን ችግር በጽሁፍም ሆነ በሌሎች ነገሮች በሰፊው ማሳየት አልቻልንም። ስለሆነም አፄ ኃይለስላሴ ለህብረተሰብአችን ዕድገት ያደረጉትን አስተዋጽዖ በጥሞና የሳይንስ መነጽር፣ በተለይም ለንጉስ ናፋቂዎችና የሳቸውን ስራ ለሚያጋንኑት ማስረዳት የማይቻልበት ሁኔታ ተፈጥሯል። የሰው ልጅ ሚናና ዕኩልነት በማይታወቅበት በእንደኛው ባለው ህብረተሰብ ውስጥ ተውልደው ያደጉ ውጭ አገርም ሰላሳና አርባ ዐመት ያህል ከኖሩ በኋላ አንኳ ከ1940ዎቹ መጨረሻ አንስቶ እስከ 1974 ዓ.ም ድረስ ያለውን የህብረተሰብአችንን ያልተስተካከለ ዕድገት ሲያስረዷቸው ነገሩን እንደስድብና አገዛዙን እንደመናቅ አድርገው ነው የሚቆጥሩት።

       ያም ሆነ ይህ የአፄው ዘመናዊነት ፖሊሲ አጠቃላይና(Holistic) የተስተካከለ ዕድገትን ያመጣ አይደለም። በህብረተሰቡ ውስጥ ግልፅ ያሰራር ስልትና ክፍፍል(Division of Labour) እንዲፈጠር ያደረገ አይደለም። የሳይንስና የቴክኖሎጂ ዕምርታ እንዲኖር መንገድ ለመክፈት የሚያስችል ፖሊሲ አለነበረም። የኢኮኖሚ ፖሊሲው እጅግ የተሰበጣጠሩና ውስጠ-ኃይላቸው ደካማ የሆኑ አጠቃላይ ሀብትን ለመፍጠር የማያስችሉ የኢኮኖሚ ሁኔታዎችንና ግኑኝነቶችን የፈጠረ ነው። ይህ ዐይነቱ የተሰበጣጠረና ውስጠ-ኃይሉ ደካማ የሆነ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ከሶስዮሎጂ አንፃር መንፈሱ ያልረጋና ህብረተሰብአዊ ኃላፊነትን ሊቀበል የማይችል የህብረተሰብ ክፍል ብቅ እንዲል አድርጓል። የሚሙለጨለጭ፣ አታላይ፣ሌላውን በእግዚአብሄር አምሳል የተፈጠረውን አምሳያውን የሚንቅ፣ በቀላሉ ለውጭ ኃይል የሚያጎበድድና፣ አገሩንም ለመሸጥ የተዘጋጀ፣ ፈጣሪ ያልሆነና በቀላሉ የሚታለልን የህብረተሰብ ክፍል በአገራችን ውስጥ ብቅ ሊል ችሏል። ይህ አንደኛው ሲሆን፣ የአፄው ያልተጠና የኢኮኖሚ ፖሊሲ ፊዩዳሊዘምን በአዲስ መልክ ሲያጠናክር፣ እዚያው በዚያው ደግሞ ከዚህም ከዚያም ብቅ ያለ፣ ይህንን ሆነ ያንን እወክላለሁ የሚል ንዑስ ከበርቴ የብሄረሰብ እንቅስቃሴ ሊፈጠርና፣ በአሜሪካንና በእንግሊዝ ኢምፔሪያሊዝም አገሮችን በማዳካም ስትራቴጂ ውስጥ በመጠቃለል፣ ምክርና ርዳታ በማግኘት ለህብረተሰብአዊ ትርምስ ምክንያት ሆኗል። በአናሎጊ ስንመለከት፣ የአውሮፓው ካፒታሊዝም የብሄረሰብን አመለካከት በመደምሰስ፣ ህብረተሰቡን  በመበወዝና፣ ስራ ለመፈለግ ሲል ከክልሉ ወጥቶ ወደሌላ ቦታ የሚሄድ ከሌላው ጋር በመጋባት ብሄረሰቡ የጣለበትን መጋረጃ በመበጣጠስ፣ ከብሄረሰብ ይልቅ ብሄራዊ ባህርይ እንዲወሰድና ብሄራዊ ባህልን ባህሉ እንዲያደርግ ተገዷል። የካፒታሊዝም ውስጣዊ-ኃይል(Dynamism) በቡድንና በዘመድ አዝማድ መደራጀትንና መሰበሳብን በመበጣጠስ በዕምነትና በዕውቀት ላይ እንዲሆን አድርጓል። ስለሆነም በካፒታሊዝም ዕድገት ውስጥ ህብረተሰቦችና የፖለቲካ ፍልስፍና አረማመድ ልዩ ዐይነት ባህርይ ነው ያላቸው ማለት ይቻላል።

       አሁንም ወደኛ አገር ስንመጣ፣ በአገር ደረጃ ከመደራጀትና ብሄራዊ አጀንዳ ይዞ ከመንቀሳቀስ ይልቅ ነገሮችን በጠባቡ በመረዳትና በጠባብ አስተሳሰብ በመወጠር ነገሮችን ሁሉ በሎጂክና በዲያሌክቲክ መነጽር ማየት የማይቻልበት ሁኔታ ሊፈጠር ቻለ። እኔ ብቻ ነኝ የተጨቆንኩ፣ የተበደልኩ በማለትና በማጋነን የአንድን ህብረተሰብ ዕድገት በሳይንስ መነጽር ለመመርመር የማይቻልበት ሁኔታ ተፈጠረ። በዚህ መልክ ደግሞ ነገሮች ሁሉ በዝቅተኛ ወይም በበላይነት ስሜትነት እየተገለጹ ለውይይትና ለክርክር አመቺ እንዳይሆኑ ተደረጉ። ይህ የተወሳሰበ ሁኔታና የኛ ደካማ ዕውቀትና ማንኛውንም ነገር በጠባቡ መመልከት በተለያየ መልክ የሚገለጹ፣ ጭቁን ህዝቦችን እናግዛለን የሚሉ፣ በመሰረቱ ግን ሰላዮችና የአገራችንን ዕድገትና ሰላማዊ ኑሮና በጋራ ግንባታ መንቀሳቀስ የሚቀናቀኑና ለዝንተ-ዓለም ተመጽዋች ሆነን እንድንኖር የሚያደርጉ ኢምፔሪያሊስታዊ ኃይሎች መሳሪያ በመሆን ርስ በርስ እንድንበጣበጥ ሆነ። ይህ አስቸጋሪ የህብረተሰብአችን ዕድገት በብሄረሰብ ተወካዮች ብቻ የሚወሰን ሳይሆን፣ ራሳቸውም ለብሄራዊ ነፃነትና ለአንድነት እንታገላለን የሚሉትን አስተሳሰባቸውን ያቀፈና በዕውቀትና በዕምነት ደረጃ እንዳይደራጁ ያደረገ ነው። ስለዚህም ነው የየካቲቱ አብዮት በወንድማማችና በእህትማማች፣ ነገር ግን ደግሞ ለአንድ ዓላማ እንታገላለን በሚሉ ቡድኖች መሀከል የርስበርስ መተላለቅ እንዲኖር ያደረገው። „አብዮት ካለደም መፈሰስ አይሰምርም“ እየተባለ በብዙ መቶ ሺህ ህዝብ እንዲገደልና እንዲሰቃይ ዛሬም እንዲሸማቀቅና ለነጻነቱ እንዳይታገል የተደረገው ግለሰብአዊነትንና ቀና ዕምነትን ከራስ ጋር ለማዋሃድ ባለመቻሉ ነው። የየካቲቱ ሁኔታ ዛሬም ይታያል። ዕውቀትንና ዕምነት ሳይሆን ግለሰቦችን ማወደስና በጭፍን መመራት፣ ቡድናዊ ስሜትን ማጎልበስና ለጋራ ዓላማ ለመታገል ያለመቻል፣ ከዕውነተኛና ስልጣኔ ይልቅ በማይታወቀው ሊበራሊዝምና የገበያ ኢኮኖሚ አስተሳሰብ ክልል መሽከርከርና፣ የሌላውን አስተሳሰብ ማፈንና ሌላውን ለማጥፋት መታገል የቱን ያህል ከፊዩዳል ባህርይ እንዳልተላቀቅን ነው የሚያረጋግጠው። በኮምፒዩተርና  በኤንተርኔት ዓለም እያለን አሁንም ቢሆን እዚያው በዚያው የድሮውን ቡድናዊና ግልጽ ያልሆነ አሰራር እያራመድን እንገኛለን። ይህ በራሱ ለዕድገት ፀር መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል። በኢትዮጵያዊነት ስሜት ሊጋረድ የሚችል አይደለም።

        ከዚህ በመነሳት ነው የአብዮቱን ምስቅልቅል ሁኔታ መረዳት የሚቻለው። ሁላችንም የሶሻሊዝምና የኮሙኒዝም ውጤቶች አልነበርንም። ሁላችንም የኢትዮጵያ ፊዩዳል ስርዓትና የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ውጤቶችና፣ የአሜሪካንን እሴት(Value) ናፋቂዎች ነበርን። አሁንም ያለን አለን። የለም እንደዚህ ዐይነቱ  በተወሰነ ወቅት ብቅ ያለ ርዕዮተ-ዓለምና የኢኮኖሚ ግኑኝነት እኛን የሚመለከት አይደለም የምንል ከሆነ ልዩ ፍጡሮች ነን ማለት ነው። በሶስዮሎጂና በሳይኮሎጂ ልንገለጽ የማንችል፣ መጥፎም ሆነ ጥሩ ነገር ሲስፋፋ ልንቀበልና ልንለወጥ የማንችል፣ እንደተፈጠርን የቀረን ነን ማለት ነው። ለነገሩ ስዎች ስለሆን የአስተሳሰብ ለውጥ እናመጣልን፣ ወይንም ደግሞ ጥያቄ ውስጥ ሳናገባ እንቀበላለን። በሌላ ወገን ደግሞ የአንድ ሰው አስተሳሰብ ለውጥና አንድን ነገር መቀበል ከሰውነት ጋር ማዋሃድ ሁለት ሶስት ትውልድን ይጠይቃል። አንድ ሰው በአንድ ርዕዮተ-ዓለም ለመመራትና ዕምነት እንዲኖረው የጭንቅላት ለውጥ ያስፈልገዋል። ለዚህ ነው የየካቲቱን አብዮት አራማጆች፣ በተለይም የደርግን መሪዎች በሶሻሊዝምና በኮሙኒዝም ስም ማማትና መወንጀል የማይቻለውና ስህተትም የሚሆነው። ሶሻሊስቶች ወይም ኮሙኒስቶች ስለሆኑ አይደለም በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ወጣትንና ሌላውንም የጨረሱት። ስለሶሻሊዝም የተጻፉ መጽሐፎችም ውስጥ ሰውን በመግደልና በመጨፍጨፍ ብቻ ነው አዲስ ህብረተሰብ መመስረት የሚቻለው የተባለበት ቦታ የለም። በርዕዮተ-ዓለም የሚምሉትንና የሚገዘቱትን ድርጊታቸውንም የምንረዳው የፈለቁበትንና የአደጉበትን የህብረተሰብ አወቃቀርና፣ ከዚያ ጋር ተያይዞ በትምህርት ዓለም የቀሰሙትንና በአገራችን የተስፋፋውን ውስን የካፒታሊዝም ስልተምርት ስንረዳ ብቻ ነው። ከዚህ ውጭ የሚደረግ ትንተናና አነጋገር ሳይንሳዊ አይደለም። አንድን ህብረተሰብ ደግሞ ከሳይንስ አንፃር መመርመር ካልቻልንና ችግሩን ካልተረዳን መፍትሄ መስጠት አንችልም። በመወንጀልና በተራ ቃላት ድርደራ፣ ወይም ደግሞ በጥላቻ ላይ ተመርኩዘን የምናራግበው ወሬ ሌላ ህብረተሰብአዊ ቀውስን ጋባዥ ይሆናል። ስለሆነም  የደርግንና የተቀሩትን ተራማጅ ነን የሚሉትን ቡድኖችም ሆነ ግለሰቦች ባህርዮችና ድርጊቶች፣ እልከኝነትና አልበገርም ባይነት፣ ከውይይት ይልቅ በጠበንጃ ትግል ማመንና ችግርን በኃይል ለመፍታት መሞከር፣  መፎከር፣ የሚያረጋግጠው የቱን ያህል ከበርቴያዊ ውይይት ወይም ደግሞ የፕላቶን ዲያሌክቲካዊ የውይይት ዘዴ፣ ጥያቄን የማቅረብና ለመመለስ የመሞከር ባህል ከሰውነታችን ጋር ያልተዋሃደ መሆኑን ነው። ኩሙኒካቲቭ ከሆነ የአነጋገር ስልትና በውይይት የማሳመን ልምድ አለመኖር፣ በጋርዮሽና ተደራጅቶ ለመስራት ዝግጁ ከመሆን ወደ አፍራሽነት ማምራት፣ በራስ ላይ ዕምነት ከማሳደርና ርስበርስ በግልጽ ከመወያየት ይልቅ የብሄራዊ አጀንዳችንን የውጭ ኃይሎች እንዲፈቱልን እነሱን መማፀን የሚያረጋግጠው አንድ የተከበረች አገር ለመገንባት ገና ያለተዘጋጀን መሆናችንን ነው። ስለዚህም የየካቲቱ አብዮት መክሽፍ፣ ደም መፋሰስና ህብረተሰብአዊ እሴቶች መበጣጠስና የህዝባችን ህሊና መረበሽና አቅጣጫውን ማጣት በቀላል ነገሮች በጥቁር/ ነጭ በመሳል የሚገለጹ አይደለም። የብዙ ዐመታትን የጭንቅላት ስራ የሚጠይቁ ናቸው።

        ያም ሆነ ይህ ከ1940ዎቹ መጨረሻ ጀምሮ እስከ 1974 ዓ.ም ድረስ በዘመናዊነት ስም የተካሄደውን ህብረተሰብአዊ መመሰቃቀል መረዳት የሚቻለው፣ በአንድ በኩል በጊዜው የነበረውን ዕውቀትና የምሁር ብስለትም ሆነ ድክመት ከቁጥር ውሰጥ ያስገባን እንደሆን ነው። በተጨማሪም በንጉሳዊ አገዛዝ የተወቃረው የሲቪልና የሚሊተሪ ቢሮክራሲ አገርን ለመገንባት መቻልና ወይም አለመቻል፣ እንዲሁም ደግሞ ከማንኛውም የአገርን አንድነት ከሚያናጋ ሴራ ለመጠበቅ ብቃትነት ያለው ወይም የሌለው መሆኑን  ስንገነዘብ ብቻ ነው። ከዚህም ስንነሳ የምንጠይቃቸው ጥያቄዎች፣ የምሁሩ ኃይልም ሆነ ቢሮክራሲው የቱን ያህል የተወሳሰበውን የዓለም ሁኔታና፣ በተለይም የአሜሪካኖችን አሻጥር የተረዱና፣ ስትራቴጂያዊ ጥናቶች በማካሄድ በጥንቃቄ መወሰድ ያለበትን እርምጃ መውሰድ የሚችሉ ነበሩ ? በጊዜው የዓለምን ፖለቲካና በአካባቢው የሚካሄደውን የጂኦ ፓለቲካ እሽቅድምድም የሚያጠና ኢንስቲቱሽን ነበር ወይ? ስለሆነም ህብረ-ብሄርንና(Nation-State) ህብረተሰቡን በጠንካራ መሰረት እንዳይገነባ የሚደረገውን የውጭ ኃይሎችን ግፊትና አሻጥር የሚከታተልና የሚያውቅ የምሁር እንቅስቃሴ ነበር ወይ? ወይስ አገዛዙና ቢሮክራሲው ግብታዊ የፊዩዳል ፖለቲካ በመከተል አገራችንን ያሰጠቁ ነበር ወይ? ብለን በማንሳት በጊዜው የነበረውን አጠቃላይ አስተሳሰብና የፖለቲካ ሂደት መገምገሙ የአገራችንን አስቸጋሪ ጉዞ እንድንረዳ ያስችለናል። በመሆኑም፣ የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም የበላይነትን ከተቀዳጀ ጀምሮ ደካማ አገሮች በጠንካራ መሰረት ላይ እንዳይገነቡና፣ ህዝቦቻቸውም የሰላም ኑሮ እንዳይኖሩ የሚሸርበው ተንኮል በጊዜው ለብዙዎች ግልጽ እንዳልነበር መረዳት ይቻላል። ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ማለቂያ በኋላ ባለፉት ስድሳ ዐመታት ዓለም እፎይ ያለችበት፣ በተለይም እንደኛ ያሉ ደካማ አገሮች እፎይ ብለው ኃይላቸውንና ሀብታቸውን በማጣመር አገር ለመገንባት የተነሱበትን ወቅት ያገናዘበ በጣም ጥቂት ነው ብል አልሳሳትም። ጦርነት ማካሄድና፣ አንዱ ሌላውን በማጥፋት ብቻ ለመኖር የሚቻል ተደርጎ እንደተፈጥሮ ህግ ሆኖ በተወሰደበት ዓለም ውስጥ፣ ከትላንት በስቲያ በኮሙኒዝም ስም አገሮችን ማሰስ፣ በዛሬው ወቅት ደግሞ በአሸባሪነት ስም በየቦታው ጦርነት በመቀስቀስ አገሮችን ማመስና ህዝቦች በጋራ በመነሳት በሳይንስና በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ ጤናማና ጥበባዊ አገር እንዳይመሰርቱ የተደረገበትን ሁኔታ፣ በተለይም ለፖለቲካ ስልጣን እንታገላለን በሚሉት ጭንቅላት ውስጥ ሰርጎ የገባ ጉዳይ አይደለም። በዚህ መልክ የተቀነባበርውን የእንግሊዝና የአሜሪካን ፕሮጀክት፣ ጠቅላላው ሰለጠንኩ የሚለው የምዕራቡ ዓለምም በተለያዩ መሳሪያዎችና የረቀቁ ዘዴዎች እንደሚያግዝና ዕድገታችንና በሰላም መኖራችንን የሚቀናቀኑ ኃይሎች ብዙ እንደሆኑ ለብዙዎቻችን ግልጽ የሆኑ አይመስለኝም። በሌላ አነጋገር አሜሪካና እንግሊዝ ብቻቸውን አይደለም ጦርነት የሚያካሂዱት። የነጩ ዓለም ሲጮህ በአንድ ጊዜ ነው።  የሚዶቅሰንም ክንዱንም በማጣመር በአንድ ላይ ነው። እኛ ደካሞች ደግሞ የተለያዩ ተንኮሎችን እየፈጠርንና ርስባራሳችን እየተጠላለፍን ሁኔታውን እናመቻችላቸዋለን። አልፎም ተርፎም በስለላ ተግባር እንተባበራቸዋለን። ለሳይንስና ለቴክኖሎጂ እንዲሁም ለብሄራዊ ነፃነት እታገላለሁ የሚለውን ግለሰብም ሆነ ድርጅት አሳልፈን በመስጠት ለማስመታት እንሞክራለን። የሃሳብ መጋጨት ተናውጦን፣ ራስን ለማግኘት ባለመቻልና የቀና ስራ ላለመስራት በጠባብ የሃሳብ ክልል ውስጥ በመሽከርከር ችግር ስንፈጥር እንታያለን። በዘመናዊነት ስም የገባውን ጥቅላላውን የተበላሸ የአሰራር ስልትና የዛሬውንም የኢህአዴግ/የወያኔ የትርምስ ፖለቲካ መገንዘብ የምንችለው ከአጠቃላዩ የኢምፔሪያሊስት ፕሮጀክት ነው። ከዚያ በፊት ግን አንዳንድ መሰረተ-ሃሳቦችን እንመልከት።

የኒዎ-ሊበራሊዝም ዓለም አቀፋዊ ፕሮጀክትና ውጤቱ!

       አብዛኛዎች የምዕራብ አውሮፓ አገሮች ኢኮኖሚያቸውን መልሰው ከገነቡ ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት በኋላ የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም በተለይም በኢኮኖሚ መስክ ተወዳዳሪ ያጋጥመዋል። በጊዜው ምዕራብ ጀርመንና ጃፓን በተለይም በውጭ ንግዳቸው አሜሪካንን ይቀድማሉ። ይህ ሁኔታና አሜሪካን በቬትናም የሚያካሂደው ጦርነት በአንድ በኩል የዶላርን በዓለም አቀፍ ደረጃ  በብዛት መስፋፋት ሲያስከትል፣ በዚያው መጠንም የአሜሪካን የወርቅ ክምችት መጠኑ በከፍተኛ ደረጃ እየተሟጠጠ ይመጣል። በብሬተንስ ውድስ ስምምነት አሜሪካን ዶላርን በወርቅ ለመለወጥ የገባውን ስምምነት ወደ ስድሳዎች ዐመታት መጨረሻ ላይ ተግባራዊ ለማድረግ የማይችልበት ሁኔታ ይፈጠራል። በዚህም የተነሳ ከ1944 ዓ.ም ጀምሮ ይሰራበት የነበረው ዶላርን በወርቅ የመቀየሩ ግዴታ በፕሬዚደንት ኒክሰን አስተዳደር በ1971 ዓ.ም እንዲቀር ይደረጋል። በ1973 ዓ.ም ተለዋዋጭ የከረንሲ ገበያ በመፍጠር ካፒታል ካለምንም ገደብ ሊንቀሳቀሰ የሚችልበት ሁኔታ ይፈጠራል። በዚህ ላይ በ1973/1974 የተከሰተው የዘይት ዋጋ መናር የምዕራብ አውሮፓን ኢኮኖሚዎች ቀውስ ውስጥ ከቶት ነበር። ስለሆነም ብዙ መንግስታት እንደቀድሞው በኬኒያኒዝም ላይ የተመሰረተ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ለማካሄድ የማይችሉበት ሁኔታ ይፈጠራል። በኒዎ-ሊበራሊዝምና በነፃ ንግድ አራማጅነት የሚመራው የእነ ፕሮፌሰር ሚልተን ፍሪድማን ፍልስፍና ከአሜሪካና ከምዕራብ አውሮፓ አልፎ ዓለም አቀፋዊ የሚሆንበት ሁኔታ ይዘጋጃል። በ1980ዓ.ም መጀመሪያ ላይ ለሶስተኛው ዓለም የኢኮኖሚ ዕድገት ያመቻል የሚባል የመዋቅር መስተካከያ(Strucctural Adjustment Program) ተዘጋጅቶ ይቀርባል። ፕሮግራሙን የዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅትና የዓለም ባንክ ተግባራዊ እንዲያደርጉት ይደረጋል። በተለይም ፕሮግራሙን እንዲቀበሉ በብዙ የአፍሪካ አገሮች ላይ ግፊት ይደረጋል። ይህ የኒዎ-ሊበራሊዝም የኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊ ከሆነ ከጥቂት ዐመታት በኋላ በየአገሮች ውስጥ አዲስ የሀብት ክፍፍልና የኃይል አሰላለፍ ይፈጠራል። በማኑፋክቱር ላይ ከተመሰረተ የኢኮኖሚ ዕድገት ይልቅ የንግድ እንቅስቃሴና የኤክስፖርት መስኩ እየተጠናከረ ይመጣል። በዚያውም መጠን አገሮች የባሰውኑ በዕዳ እየተበተቡና፣ ዕዳቸውን ለመክፍል ሲሉ አዳዲስ አንጀት አጥብቅ ፓሊሲ(Austerity Program) እንዲከተሉ ይገደዳሉ። በዚህም ምክንያት የተነሳ የውስጥ ገበያን በጠንካራ መሰረት ገንብቶ የተስተካከለ ኢኮኖሚ በአገር ደረጃ ከመገንባት ይልቅ የተዛባ ሁኔታ ይፈጠራል። በዚህ ዐይነቱ የኒዎ-ሊበራል ፕሮጀክት በተለይም ከሰሀራ በታች ያሉ የአፍሪካ አገሮች በአንድ በኩል ገበያቸውን ለውጭ የፍጆታ ዕቃ ክፍት ሲያደርጉ፣ በሌላ ወገን ደግሞ ኢንዱስትሪዎቻቸው እየተመቱባቸው መጡ። በዚህ መልክ  በዓለም አቀፍ የታወቁት ግብጻዊው የኢኮኖሚ ምሁር ፕሮፌሰር ሳሚር አሚን እንዳሉት አፍሪካ ብቻ ሳትሆን ዓለም በጠቅላላው ወደ ኒዎ-ሊበራል የመገበያያ መድርክነት ተለወጠች።

       ይህ በእንደዚህ እንዳለ፣ በምስራቅ አውሮፓና በቀድሞው የሶቭየት ህብረት ውስጥ አዲስ ሁኔታ ይፈጠራል። በፕሬዚደንት ጎርባጆብ የተቀደደው ፕርስትሮይካ ሶቭየት ህብረትን እንድትሰነጣጠቅ በሩን ይከፍታል።  የኮሙኒስት አገሮች መበታተንና አዲስ ዓለም አቀፍ የፖለቲካና የኃይል አሰላለፍ መከሰት የአሜሪካን ካፒታሊዝም በአሸናፊነት እንደወጣ ተደርጎ ይተረጎማል። የዓለምም ህዝብ ከእንግዲህ ወዲያ በሊበራሊዝምና በነፃ ገበያ አማካይነት  ብቻ ህልሙና ምኞቱ ተግባራዊ እንደሚሆንለትና እንደሚጠናቀቅለት ይበሰራል። የታሪክ ወይም የርዕዮተ-ዓለም መጨራሻዋ ደረሰ ተብሎ በነፉኩያማ ይተረጎማል። ልክ ሄገል የፕረሽያ መንግስት በጀርመን ምድር በአሸናፊነት ሲወጣ የምፈልገውን አገኘሁ ብሎና የታሪክን ድምዳሜ በዚያው ገድቦ እንደተነተነው ሁሉ፣ ፉኩያማም የኮሙኒዝምን መከስከስና የአሜሪካንን ካፒታሊዝም በአሸናፊነት መውጣት የዓለም ህዝብ ደስታ መግለጫ አድርጎ ተረጎመው። ከዚህ የአሜሪካን ፕሮጀክት ውጭ የዓለም ህዝብ የሚንቀሳቀስበት ሌላ የነጻነት ፕሮጀክት የለም ተብሎ ተነገረን። ስለሆነም፣ ራሷን እንድታገል በተገደደችው ራሽያና በተቀረው የምስራቅ አውሮፓ አገሮች የኒዎ-ሊበራሊዝም ፕሮጀክት መሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዲሆን ተደረገ። ይህ ሾክ ቴራፒ(Shock Therapy) በመባል የሚታወቀው ፖሊሲ ተግባራዊ ሲሆን፣ ጥቂቱን የሚያደልብበትና አብዛኛውን ህዝብ ደግሞ ወደድህነት የሚገፈትርበት ሁኔታ ተፈጠረ። በዚህ የኒዎ-ሊበራል ፕሮጀክት በመመካትና አዲስ የተፈጠረውን ደካማ የፖለቲካ ሁኔታ ተገን በማድረግ በተለይም የራሽያ ህልውና ጥያቄ ውስጥ መግባት ጀመረ።  የአሜሪካንና የእንግሊዞች ፕሮጀክት አዳዲስ ኃይሎችን በመጥቀም እንዴት አድርገው የራሺያን የጥሬ ሀብት ለመዝረፍና ጠቅላላው ኢንዱስትሪዋን ለመምታትና የሶስተኛው ዓለም ሁኔታ መፍጠር እንደሚችሉ ስትራቲጂ ይቀይሳሉ። በእርግጥም እነፕሬዚደንት ዬልሲንና ወጣት ኢኮኖሚስቶች የተከተሉት የኢኮኖሚ ፖሊሲ ራሽያን ሙሉ በሙሉ ጥገኛ የሚያደርጋትና ወደድህነት በመገፍተር ህልውናዋን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ ነበር። በዚህ ላይ አንዳንድ የድሮው በሶቭየት ህብረት ክልል ውስጥ የነበሩ ፌዴራል መንግስታት ነፃ ከወጡ በኋላ በሰሜን አትላንቲክ የጦር ካምፕ ውስጥ መጠቃለልና ራሽያን ለመክበብ የተወሰደው እርምጃ የራሽያን የጂኦ ፓለቲካ ሁኔታና የውስጡን የፖለቲካ ኃይል አሰላለፍ የሚያናጋ ነበር። ይህ የአሜሪካንና የእንግሊዝ ኢምፔሪያሊዝም ሻጥርና ድርጊት ግን ቀስ በቀስ በፕሬዚደንት ፑቲን ሊከሽፍና ስትራቴጂክ ቦታዋን መልሳ እንድታገኝ ሆናለች ። ይሁንና ግን አሁንም ቢሆን አሜሪካን ራሽያን ከውጭ በመክበብና፣ ከውስጥ ደግሞ አንዳንድ የሲቪክ ማህበራትንና በቅራኔዎች አያያዝ የሚሰራውን ስህተት በመጠቀም ፖለቲካዊ ትርምስ እንዲፈጠርና ለሱ የሚስማማ ለስለስ ያለ አገዛዝ እንዲመጣ የውስጥ ለውስጥ እንደሚሰራ ግልጽ ነው። የሰሞኑ የዱማ ምርጫና የምዕራቡ ዓለም፣ በተለይም የኦባማ አስተዳደር ጣልቃ-ገብነት የሚያረጋግጠው አሜሪካ የቱን ያህል ራሽያ ውስጥ የአገዛዝ ለውጥ እንዲመጣ እንደሚፈልግ ነው። በተለይም እንደራሽያ ያሉ ታላላቅ አገሮች ውስጥ ባለው ገና ባልሰከነ የኃይል አሰላለፍና፣ ንቃተ-ህሊናው የዳበረ የከበርቴ መደብ በሌለበት አገር፣ በተለይም ደግሞ የሲቭክ ማህበሩና የፖለቲካ ፓርቲዎች ገና ብዙም የምዕራቡን ዓለም የሻጥር ፖለቲካ በደንብ ማገናዘብ በማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ ተራ የፓርሊሜንተሪ ምርጫ ማካሄድና ስልጣን መልቀቅ ራሽያ ያላትን ኃይል ሊያዳክመው ይችላል። ይህ ማለት ግን ህልውናዋን የማይጎዳና ለሁሉም የሚያመች ዲሞክራሲያዊ ሂደት ተግባራዊ አይሁን ማለቴ አይደለም። ብሄራዊ ስሜት የሚዳብርበትና፣ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች እንደ ጠላት የማይተያዩበት አዲስ የፖለቲካ ባህል ቢፈጠር ህብረተሰብአዊ ሚዛን ጠብቆ የውጭ ኃይሎችን ጣልቃ ገብነት መቋቋም ወይም በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ ይቻላል።

       በሌላ ወገን ግን ባሸናፊነት ወጣ የተባለለት ጎሎባል ካፒታሊዝምና የአሜሪካን እሴት በተለይም ከ1997 ዓ.ም ጀምሮ ቀስ በቀስ ግን ደግሞ በእርግጠኝነት ቀውስን እየተከናነበ ይመጣል። የዶት ኮም ቀውስና በብዙ የኤሺያ አገሮች የደረሰው የኢኮኖሚ መናጋት የሚያረጋግጠው የቱን ያህል የግሎባል ካፒታሊዝምን ውስንነት ነው የሚያሳየው። ግሎባላይዜሽን በከፍተኛ ደረጃ መሰበክ ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ እንደታመነበት የዓለም ህዝብ ወደ ብልጽግናና እኩልነት አላመራም። የጥሬ-ሀብትን መዝረፍና የገንዘብንም ሆነ ሌላ ተንቀሳቃሽ ካፒታልን በፍጥነት ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ በማንቀሳቀቀስ ብዙ የሶስተኛውን ዓለም አገሮች መቀመቅ ውስጥ ነው የከተታቸው። በአንድ አገር ውስጥና አካባቢ የተተከሉ ኢንዱስትሪዎች ማምረት ጀምረው ለጥቂት ዐመታት ከተንቀሳቀሱ በኋላ የሰራተኛ ዋጋ ውድ ነው በሚል እየተነቀሉ ሌላ ቦታዎች በመውሰድ ተስፋ አግኝቶ ቤተሰቡን ማስተዳደር የጀመረውን ሰራተኛ እንደገና ወደድህነት ዓለም እንዲወረወር ይደረጋል። ከዚህ ጋር ተያይዘው ተግባራዊ የተደረጉት የሞነቴሪ የኢኮኖሚ ፓሊሲዎች በሙሉ በየአገሮች ውስጥ የተዛባን ሁኔታንና በሀብት መባለግን ነው ያስከተሉት። በሌላ አነጋገር፣ እነ ፉኩያማ እንደሰበኩት የዓለም ማህበረሰብ በሊበራሊዝምና በካፒታሊዝም አማካይነት ነጻነቱንና ህልሙን ዕውን ሊያደርግ አልቻለም። በተለይም የፋይናንስ ካፒታሊዝም ማደግና ከቁጥጥር ውጭ መውጣት በተጨባጭ የኢኮኖሚው ዘርፍና የትርፍ ትርፍን ለማካበት ገንዘብን በተለያዩ የፊናንስ ፕሮዳክቶች አማካይነት እዚያው በዚያው በማሽከርከር በሚካሄደው ክንዋኔ ልዩነት እንዲፈጠር ሆነ። የፋይናንስ ካፒታሊዝምን የበላይነት ለመግታት በየጊዜው የሚወሰዱት ያልተሟሉ እርምጃዎች የበለጠ ጥንካሬ እየሰጡትና መንግስታትንም በዕዳ በመተብተብ ወደ ማናጋት ደረጃ የደረሰበት ሁኔታ በግልጽ ይታያል እንጂ የተዳከመበት ሁኔታ በፍጹም አይታይም። ምክንያቱም በየአውሮፓ ከተማዎች፣ በተለይም በብርሰልስና በዋሽንግተን የተቀመጡት ሎቢስቶች ህጉን አርቅቀው ስለሚሰጧቸው ይበልጥ ለመጠናከር ችሏል። በተለይም አሁን በግሪክ፣ በጣሊያን፣ በስፔይና በፖርቱጋል እየታየ ያለው በዕዳ መተብተብና የፋይናንስ ካፒታል እነዚህ አገሮች ጥብቅ የሆነ የባጀት ፖሊሲ እንዲያካሂዱ መገፋፋት የሚያመለክተው በዚህ መልክ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለፋይናንስ ካፒታል የሚያመች ዓለም አቀፋዊ አገዛዝ(Global Governance) ለመመስረት ነው። የየአገሮች ብሄራዊ ነፃነት በመናድና በራሳቸው በመንግስታት መወሰድ ያለበት የህብረተሰብ ፖለቲካ ቀርቶ፣ ምን ዐይነት የኢኮኖሚ ፖሊሲ ማካሄድ እንዳለባቸው ዋሽንግተንና ለንደን ወይም ብርሰልስ ይወሰናል ማለት ነው።

      የፋይናንስ ካፒታሊዝም በማበጥና፣ ፓርቲዎችንና መንግስታትን በተዘዋዋሪ ፖሊሲያቸውን ለሱ እንዲስማማ እንዲያወጡ በማድረግ በአጠቃላይ ሲታይ ካፒታሊዝምን በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንደከተተው በግልጽ ይታያል። ባለፉት ወራት ዎል ስትሪትን መያዝ(Occupy Wallstreet)   በማለት ከአሜሪካን ተነስቶ ወደ ምዕራብ አውሮፓ ከተማዎች የተስፋፋው ሰላማዊ ሰልፍና ግብግብ የሚያመለክተው በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ህዝቦች በፋይናንስ ካፒታል የደረሰባቸውን ብሶት ለማሰማትና ቁጥጥር እንዲደረግም ነው። ፕሬዚደንት ኦባማም ከሶስት ዐመት በፊት ለምርጫ ውድድር ሲቀርብ „አዎን ይቻላል“  ብሎ ለአሜሪካን ህዝብ ብቻ ሳይሆን „ለዓለም ህዝብም ተስፋ የሰጠውን“ ተግባር ላይ ማዋል ያልቻለው፣ በአንድ በኩል በፋይናንስ ካፒታል ማበጥና በፓርቲዎች ላይ የበላይነት እንዳለው የሚያረጋግጥ ሲሆን፣ በሌላ ወገን ደግሞ የሚሊታሪና የኢንዱስትሪው ኮምፕሌክስ የኦባማን መንግስት በዓለም አቀፍ ደረጃ ጦርነት ብቻ እንዲያካሄድለት ግፊት ስለሚያደርግበትም ነው። ከዚህም በመነሳትና በዎል-ስትሪት ሰዎች የተሰገሰገው የገንዘብ ምኒስተሩና የኢኮኖሚ አማካሪዎቹ፣ እንዲሁም የፊዴራል ሪዘርቡ ሃላፊ ቤርናንኪ አሁንም በኒዎ-ሊበራል አጀንዳቸው በመግፋት ኦባማ ፍቱን የሆነ የስራአጡን ቁጠር በከፍተኛ ደረጃ ሊቀንስ የሚያስችል የኢኮኖሚ ፖሊሲ እንዳይከተል አድርጎታል። ከዚህም በላይ አሜሪካ ራሱ በሚሰብከው የነፃ ገበያና የነፃ ንግድ ፍልስፍናው ገበያውን ልቅ በማድረጉ ወደ ውስጥ ስትራቴጂክ የኢንዱስትሪ ዘርፎቹም ሆነ የፍጆታ አምራች ኢንዱስትሪዎቹ በጣም እየተዳከሙበት ነው። የአሜሪካን ገበያ በቻይናና በሌሎች የሩቅ ምስራቅ ኤሺያ የኢንዱስትሪ ውጤቶች በመወረር ኤኮኖሚው እየተዳከመና የስራአጡም ቁጥር እየጨመረ እንዲመጣ ተገድዷል። በዚህም ምክንያት በቀላሉ ሊወጣው የማይችለው የማህበራዊና የባህል ቀውስ ውስጥ ወድቋል። ሰሞኑን ታትም በወጣ የዓለም አቀፍ ሄራልድ ትሪቡን ላይ በሰፊው እንደተነተነው፣ አሜሪካ ልክ እንደሌሎች የላቲን አሜሪካን አገሮች ዕጣ ሊደርሳት እንደሚችል ነው። ይህም ማለት የድረግን ትራፊክ የሚቆጣጠሩ ቡድኖች፣ በተለይም ትላልቅ ከተማዎችን በቁጥጥራቸው ስር ማድረግ እንደሚችሉና ከፍተኛ የሆነ ህብረተሰብአዊ ቀውስ እንደሚመጣ ነው። በዚህ ላይ ለተወሳሰበ የጦር መሳሪያ የሚወጣው ወጪና ለጠቅላላው የመከላከያ ኃይል የሚፈሰው በጀት በኢኮኖሚው ላይ ከፍተኛ መዛባት በማስከተል ወደፊት ሊወጣው የማይችለው ሁኔታ ውስጥ እየከተተው ነው።

        ይህ በዚህ እንዳለ፣ በኢኮኖሚ ድጎማው ሳይሆን በሚሊታሪውና በፖለቲካው ጥንካሬ በመነሳት በተለይም እንደኛ ያሉ ደካማ አገሮችን በሱ የጦርነት ስሌት ውስጥ ማካተት ቀላሉ መንገድ ሆኖ አግኝቶታል። በኢኮኖሚ መስክ ደግሞ የዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅትና የዓለም ባንክ የስራ ድርሻን በመውሰድ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ አገሮችን በግሎባል ካፒታሊዝም የአስተሳሰብና ድህነትን የመፈልፈል መዳፍ ውስጥ እንዲወድቁ በማድረግ ልዩ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ሁኔታ ተፈጥሯል። በተለይም በአገራችን የሰፈነው በጣም ደካማ የምሁር እንቅስቃሴ የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም በአገራችን ውስጥ ገብቶ የፈለገውን እንዲፈተፍት ሁኔታውን አመቻችቶለታል። የነቃ የሲቪክ ማህበረሰብ በሌለበት አገር ውስጥ የውጭ ኃያላን መንግስታት እንደልባቸው ሰርገው በመግባት የጭቆና ሁኔታዎችን ያዘጋጃሉ ማለት ነው። ሀብት እንዲዘረፍ ሁኔታውን ያመቻቻሉ። ዕድገት እንዳይመጣ ያግዳሉ። ሰፊው ህዝብ አቅመቢስ እንዲሆን ያደርጋሉ። ዲሞክራሲያዊ መብቶች ሙሉ በሙሉ እንዲገፈፉ፣ በተለይም በስልጣን ላይ ላሉት ልዩ ልዩ የጭቆና መሳሪያዎችን ያቀብላሉ፤ ምክርም ይሰጣሉ። ለነሱ የሚያመች ልዩ ዐይነት የኃይል አሰላለፍ በመፍጠር ትግሉን አስቸጋሪ በማድረግ የጭቆና ዘመኑንም ያራዝማሉ። የወያኔን ፓለቲካና ጥንካሬ እንዲሁም የሀብት ዘረፋና ድህነትን መፈልፈል ከዚሁ፣ በተለይም የእንግሊዝና የአሜሪካን ግሎባል ካፒታሊዝም ፕሮጀክት ነጥሎ ማየት ስህተት ብቻ ሳይሆን እጅግ አደገኛ የፖለቲካ አካሄድም ነው።

   ግሎባል ካፒታሊዝምና የወያኔ አጀንዳና የፖለቲካ ትርምስ  !

          ወያኔን በአብዮታዊ ዲሞክራሲና በሶሻሊዝም ስም የሚወነጅሉትን ስሰማና ሳነብ፣ ፈረንጆች እንደሚሉት በአንድ ዐይኔ አለቅሳለሁ፣ በሌላው ደግሞ እስቃለሁ። ሁላችንም ቢሆን ወያኔ እንዴት እንደተፈጠረ በትክክል አናውቅም። መልስ ሊሰጡን የሚችሉት በአጠናነሱ ላይ የነበሩና ለተወሰነም ጊዜ አብረው የታገሉና ራሳቸውን አግለው ከወጡት ነው። ይሁንና እነዚህም ቢሆኑ በእነመለስ ጭንቅላት ውስጥ ገብተውና ድርጊታቸውን ተከታትለው የወደፊት ፕሮጀክታቸው እንደዚህ ነው ብለው የተሟላ ስዕል ሊሰጡን አይችሉም። እኔም በቦታው ብሆን ኑሮ ቀደም ብዬ መተንበይ አልችልም ነበር። በተለይም ደግሞ የእነሌኒንን መጽሀፍ የሚደግምና ኢምፔሪያሊዝምን እዋጋለህ የሚል ሰውና ድርጅት፣ በኋላ 180 ዲግሪ ተገልብጦ የኢምፔሪያሊስትን ፕሮጀክት ተግባራዊ ያደርጋል ብሎ ከመጀመሪያውኑ መናገር ያዳግታል። አንድን ግለሰብና ድርጅት በድርጊቱ ብቻ ነው መመዘንና ትንተና መስጠት የሚቻለው። ከዚህም በመነሳት ነው ለዲሞክራሲና ለነፃነት እታገላለሁ የሚልን ግለሰብንም ሆነ ድርጅት የፖለቲካ ትንተና ትክክል መሆኑንና አለመሆነኑ መመርመርና የራስን ፍርድ መስጠት የሚቻለው።

       ብዙዎችን የተቃዋሚ ኃይሎች ትክክለኛ የፓለቲካ ትንተና ለመስጠት ያገዳቸው በእኔ እምነት ከሶስት ምክንያቶች በመነሳት ነው። አንደኛ፣ የኢህአዴግ አወቃቀር አንድ ወጥ ስለሆነና፣ ከውስጥ ፓርቲውን የሚቆጣጠረው ደግሞ በማርክሲስት-ሌኒንስት ርዕዮተ-ዓለም የሚመራ ነው ተብሎ ስለታመነና፣ ከላይ ወደታች የተዘረጋ የስልጣን እርከን ስላለ፣ በዚህም ምክንያት አገዛዙ የሚያራምደው የአብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ፖሊሲ ነው የሚል ነው። ሁለተኛው ምክንያት፣ በደርግ ዘመን የሰፈነውና በሶሻሊዝም ስም የተካሄደው ጭፍጨፋና ህብረተሰብን ማከረባበት ብዙዎችን የሰከነና በጥናት ላይ የተመረኮዘ ትንተና እንዲሰጡ አላስቻላቸውም። በሶስተኛ ደረጃ፣ አብዛኛዎቹ ተቃዋሚ ኃይሎች በአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም አማካይነት በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚካሄደውን የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊሲ ትክክል ነው ብለው ስለሚያምኑና፣ ከነፃ ገበያ ባሻገር ሌላ አማራጭ የሌለ ስለሚመስላቸው አሜሪካንን እንደቅዱስ ኃይል ነው የሚመለከቱት። ስለሆነም በአቶ መለስ ዜናዊ የሚመራው መንግስት በሚያካሄደው የኢኮኖሚ ፖሊሲና በአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም በተጠነሰሰውንና በሚሰበከው የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊሲ መሀከል ግኑኝነት የለም። ከዚህ የተሳሳተ ግምትና አመለካከት በመነሳት ብዙዎቹ የተቃዋሚ ኃይሎች ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ የተከተላቸውንና ተግባራዊ የሚያደርጋቸውን የኢኮኖሚ ፓሊሲዎች የሚመለከቱት ከዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅትና ከዓለም ባንክ አገሮችን ከማድኸየት ፕሮጀክት ውጭ ነው።በብዙዎቹ ዕምነት የዓለም የገንዘብ ድርጅትና የዓለም ባንክ አደረጃጀት በቀጥታ ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት መፈጸሚያ በኋላ የተፈጠረውን የኃይል አሰላለፍና የሶስተኛውን ዓለም አገሮች በአዲሱ የዓለም የስራ-ክፍፍል በማካተት ቀጭጨው እንዲቀሩ ከማድረግ ጋር የሚታይና የሚያያዝ አይደለም።

       እስከማውቀው ድረስ ከተቃዋሚ ድርጅቶች ወይም ከኢትዮጵያ ኢኮኖሚስቶች የኢህአዴግን የኢኮኖሚ ፖሊሲ ውስጣዊ ይዘት በሚመለከት ከኒዎ-ሊበራሊዝም ሁኔታ በመነሳትና በመተንተን የተሰጠ መግለጫ ወይም ትንተና የለም። የኢህአዴግ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ስምና ውስጣዊ ባህርይ ምን እንደሚመስል ካልታወቀ ደግሞ ምን ዐይነት ትግል ማካሄድና ምንስ አማራጭ ለመስጠት እንደሚቻል በጣም አስቸጋሪ ይሆናል። አንድን አገዛዝ በአምባገነንነት ስምና ዲሞክራሲ ባለመኖሩ፣ ወይሞ ምርጫ በሚካሄድበት ወቅት ግልፅ የሆነ አሰራር የለም ብሎ መፈረጁ ብቻ አይበቃም። በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ያለ የረዥም ጊዜ ታሪክ ያለውንና በስልጣኔ ጥማትና በዲሞክራሲ እጦት የሚሰቃይን ህዝብ በሶስት መፈክሮች ብቻ መሸንገልና የስልጣኔውንም ጎዳና ማሳየት አይበቃውም። የአገራችንን የተወሳሰበ ችግርና፣ በአገዛዙና በውጭ ኃይሎች መሀከል ያለውን የእከክልኝ ልከክልህ የጥቅም መተሳሰር ለመተንተን ከአምባገነን ባህርይው፣ ከመደብለ ፓርቲና ዲሞክራሲ እጦት ባሻገር ሄዶ መተንተን ተገቢ ነው።

       ያም ሆነ ለማንኛችንም ግልጽ እንዲሆን፣ ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ከሁለት ዐመት በኋላ መከተል የጀመረው በዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት(IMF) ተዘጋጅቶ የቀረበለትን የኢኮኖሚ ፖሊሲ ነው። ፓሊሲውን ያላያችሁ ካላችሁ ማሳየት ይቻላል። በስምምነቱና በፖሊሲው መሰረት፣ 1ኛ)የኢትዮጵያ የውጭ ገንዘብ ከዶላር ጋር ሲወዳደር በደርግ ዘመን 2.05 ብር በአንድ ዶላር ይመነዘር የነበረው፣ ከኢህአዴግ ጋር በተደረሰው ስምምነት 5 የኢትዮጵያን ብር በአንድ ዶላር እንዲመነዘር ይደረጋል። ይህ ኢኮኖሚስቶች ዲቫልዌሽን የሚሉት ገንዘብን ዝቅ የማድረግ ፖሊሲ በኒዎ-ሊበራሎች ዕምነት ወደ ውጭ የሚላክ ምርትን በብዛት እንዲሸጥ ያደርጋል ተብሎ ይታመንበታል። እንደዚህ ዐይነቱ ፖሊሲ ደግሞ በተለይም የኢንዱስትሪ ምርትን በጥራት አምርተው ለማይልኩ አገሮች እንደፍቱን መሳሪያ ሊሆን እንደማይችል ከብዙ አገሮች ታሪክ የምንማረው ሀቅ ነው። ወደ ኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ሲመነዘር በገንዘብ ቅነሳው የተነሳ የአገሪቱ የንግድ ሚዛን መሻሻል ሳይሆን በከፍተኛ ደረጃ እየተዛባ ነው የመጣው። በዚያው መጠንም ዕዳዋ ሊጨምር ችሏል። በጊዜው ከውጭ በሚመጡ ዕቃዎች ላይና በመለዋወጫ ዕቃ ጥገኛ በሆኑ ኢንዱስትሪዎች ላይ የማምረቻ ዋጋ ከፍ በማለቱ ለግሽበት ምክንያት ሆኗል። 2ኛ) በስምምነቱ መሰረት ኢትዮጵያ የአገሯን የውጭ ንግድ መገበያያ ለውጭ ካፒታልና ዕቃዎች ክፍት ማድረግ አለባት። ይህም ሌላው የኒዎ-ሊበራሎች ዕምነት ሲሆን፣ አንድ አገር ገበያዋን ክፍት ካደረገች ለኢኮኖሚ ዕድገት አመቺ ሁኔታን ትፈጥራለች። ኢንቬስተሮች በመምጣትና መዋለ-ነዋይ በማፍሰስ የስራ መስክ ሊከፍቱ ይችላሉ። የስራ መስክ ሲከፈት፣ ገቢ የሚያገኘው የመግዛት ኃይሉ ከፍ ይላል ይሉናል። የዚህንም ውጤት የተከታተልንና የምናውቅ ያለን ይመስለኛል። ይህ ሁለተኛው ፖሊሲ በተግባር ሲመነዘር በርካሽ ዋጋ የሚያመርቱ እንደቻይናና ህንድ የመሰሉ አገሮች የአገራችንን ገበያ በቀላሉ መውረርና፣ ወደ ውስጥ ደግሞ ብዙ ተመሳሳይ ምርት የሚያመርቱ ኢንዱስትሪዎችን መምታት ችለዋል። 3ኛ)በመንግስት ቁጥጥር ስር የነበሩ ኢንዱስትሪዎች፣ ባንኮች፣ የመድህን ኩባንያዎችና ሌሎች መደብሮች ወደ ግል መዘዋወር አለባቸው። ይህን ፕራይቬታይዜሽን ይሉታል። አሁንም በኒዎ-ሊበራሎች ዕምነት የመንግስት ጣልቃ ገብነት  ለኢኮኖሚ ዕድገት ጠንቅ ስለሚሆን፣ ቁልፍ የሚባሉ የኢኮኖሚው ዘርፎች ከመንግስት ቁጥጥር ውስጥ መላቀቅ አለባቸው። የኒዎ-ሊበራሎች ዋናው ችግር የየአገሮችን የኢኮኖሚ ሁኔታና አወቃቀር ከታሪክ አንጻርና ከግሎባል ካፒታሊዝም ሁኔታ በመነሳት ትንተና ለመስጠት አለመቻል ነው። የህብርተሰብን የዕድገት ታሪክና የባህል ሁኔታ በፍጹም ከግምት ውስጥ አያስገቡም። በእነሱ ዕምነት አሜሪካንና የተቀረው የካፒታሊስት አገሮች የሚሰራበት የአሰራር ዘዴ ካለምንም ችግር በሁሉም አገሮች ተግባራዊ መሆን ይችላል። ስለሆነም፣ በተወሳሰበ የማቲማቲክስ ሞዴሎችና ከመንግስት በተሰጣቸው ስታትስቲክስ ብቻ በመደገፍና በመነሳት የአንድን አገር ሁኔታ ከዳር እስከዳር እየተዘዋወሩ ሳያጠኑ በሚያቀርቡት `ትንተና` ብዙ ፖለቲከኞችንና ምሁራን ነን ባዮችን ያሳስታሉ።

        በዚህ የተሳሳተ ምክርና ፖሊሲ ምክንያት የተነሳ በቀላሉ በመንግስት ቁጥጥር ስር የነበሩ ሀብቶች በኢህአዴግ ካድሪዎችና በአቶ መለስ ቁጥጥር ስር እንዲውሉ ተደርገዋል። ካድሬዎች በመንግስት ድጋፍ የተነሳ ከባንክ ብድር በማግኘት በአጭር ጊዜ ውስጥ ሀብታም ሊሆኑና ለመዝረፍም በቅተዋል። እንደዚህ ዐይነቱ ፖሊሲ ራሽያና ሌሎች የምስራቅ አውሮፓ አገሮችም ተግባራዊ በመሆኑ ጥቂቱን ሲያደልብ፣ አብዛኛውን ህዝብ ደግሞ ወደ ድህነት ገፍትሮታል። በቀድሞው የፕሬዚደንት ክሊንተን የውጭ ጉዳይ ምኒስተር ሚስ ኦልብራይት የሚመራ የጥናት ቡድን በምስራቅ አውሮፓ ውስጥ የተካሄደውን  የገበያ ኢኮኖሚ ለውጥ ያስገኘውን ውጤት ለማወቅ በብዙ መቶ ሺህ የሚቆጠር ህዝብ ጠይቆ ያገኘው መልስ ከ70 በመቶ በላይ የሚሆነው ህዝብ በገበያ ኢኮኖሚው ተጠቃሚ እንዳልሆነና፣ በሶሻሊዝም ዘመን በኑሮው እርገጠኛ እንደነበር ነው የደረሰበት። በእርግጥም የኒዎ-ሊበራል የገበያ ኢኮኖሚ በብዙ የምስራቅ አውሮፓ አገሮች ህበረተሰብአዊ መመሰቃቀልን አስከትሏል። ወጣት ሴት ልጆች ሰውነታቸውን እንዲሸጡ የተገደዱበት ሁኔታ ተፈጥሯል። በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ወጣት ሴቶች በነፍሰ-ገዳዮች ህይወታቸውን እንዲያጡ ተደርገዋል። በራሽያና በሌሎች የምስራቅ አውሮፓ አገሮች ልጃገረዶች ላይ የደረሰውም ግፍ በኛ ልጆችም ላይ ደርሷል። 4ኛ) የውስጡን ገበያ ሊበራላይዝ ማድረግ የገበያን ኢኮኖሚ በማያሻማ መልኩ ተግባራዊ ያደርገዋል። የአቅራቢና የጠያቂ ሁኔታ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ በመሆን ለውድድር ያመቻል የሚል ቀላል መልስ ነው። 5ኛ) መንግስት ለሶሻል መስክ የሚመድበውን ባጀት አይ ሙሉ በሙሉ መሰረዝ አለበት፣ ካሊያም በብዙ እጅ መቀነስ አለበት። በዚህ መልክ ገንዘብ ምርታማ ካልሆነው ወደ ምርታማ መስክ በመሸጋገር ከረዥም ጊዜ አንፃር ሲታይ የስራ መስክ ይፈጥራል ይላል። በአጭሩ በዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅትና በዓለም ባንክ የሚደገፈው የኒዎ-ሊበራል የኢኮኖሚ ፖሊሲ አጀንዳ ይህንን ነው የሚመስለው። ፓሊሲው ይበልጥ ርዕዮተ-ዓለማዊ ባህርይ ስላለው የአንድን አገር የኢኮኖሚና የማህበራዊ ኑሮ ችግር ከመፍታት ይልቅ ከፍተኛ ህብረተሰብአዊ መዛባትን ያስከትላል። ሰፊው ህዝብና አቅም የሌለው በቀላሉ ይጠቃሉ ማለት ነው። በመሰረቱ ፖሊሲው ፀረ-ሰውና የፋሺዝም ባህርይ ያለው ነው። ይሁንና ግን ብዙ ሰዎች ውስጣዊ ይዘቱን በደንብ ስለማይረዱና ተፈጥሮአዊ ዕውቀት ስለሚመስላቸው ለአገራቸው ውድመት የበኩላቸውን አስተዋፅዖ ያደርጋሉ። በደንብ የፖሊስውን ተግባራዊነት የተከታተለ፣ ፖሊሲው ከወጣ ከ1980 ዓ.ም ጀምሮ ብዙ አገሮች የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊና የባህል ትርምስ ውስጥ በመውደቅ ለአገዛዝ እንዳያመቹ ተደርገዋል። የዓለም ማህበረሰብ ሁሉ የተፈጥሮ ህግ ይመስል ተመሳሳይ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊ እንዲያደርግ በመገደዱ ሁሉም በአንድ ዐይነት የቫይረስ በሽታ የተለከፈ ይመስል ትርምስ ውስጥ ይገኛሉ። በዚህ መልክ ዓለምን በአንድ ወጥና ተመሳሳይ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ማዋቀሩ የተፈጥሮን ህግ ይፃረራል። ምክንያቱም ተፈጥሮ በተለያዩ አፅዋት፣ እንስሳትና በውስጧ ባሉ ልዩ ልዩ ነገሮች እንደምትገለጽና ይህም የተፈጥሮ ህግ እንደመሆኑ መጠን፣ ይህንን የተፈጥሮን ህግ ደምስሶ ተመሳሳይ እንዲሆን ማድረግ በተፈጥሮ ላይ ብቻ ሳይሆን በሰውም ላይ ከፍተኛ አደጋ ያደርሳል። እንደዚሁም ልዩ ልዩ የህብረተሰብ ታሪክ፣ ባህልና ልምድ ያላቸውን አገሮች በአንድ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ማዋቀሩ ልክ በተፈጥሮ ላይ ዘመቻ እንደማድረግ ነው የሚቆጠረው። በብዙ የላቲንና በሴንትራል አሜሪካና እንዲሁም በሰሜን አሜሪካ እንደሚታየው፣ ይህንን ዐይነቱን ታሪክን፣ ባህልን፣ የተለያዩ ህዝቦችን የህሊና አወቃቀርና የማቴሪያል ሁኔታ ያለገናዘበ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊ ማድረግ ዘለዓለማዊ ህብረተሰብአዊ ቀውስ ነው የሚያመጣው።

       ከዚህ የኒዎ-ሊበራል ፖሊስ የምናየውና የምንማረው፣ 1ኛ)ፖሊሲው በምንም ዐይነት ስለ ህዝብ መሰረታዊ ፍላጎቶች(Basic Needs) አያወራም። የአንድ ህብረተሰብ መሰረታዊ ፍላጎት በነፃ ገበያ ኢኮኖሚ አማካይነት ብቻ ነው ሊፈታ የሚችለው ብሎ ከመጀመሪያውኑ ያስቀምጣል። የገበያ ኢኮኖሚ ተግባራዊ ሆኖ በሚሊዮን ለሚቆጠር ህዝብ የዳቦ ጥያቄ እስኪመልስ ድረስ ህዝቡ አፉን ከፍቶና እጁን አጣጥፎ መቀመጥ አለበት። ይህ ዐይነቱ ስሌት በብዙ አገሮች እንደታየው ህብረተሰብአዊ ችግርና የህሊና መጎሳቆልን ያስከትላል። 2ኛ) በዚህ መሰረት በቀላል ስራ ላይ ሊውል የሚችል በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ህዝብ ጉልበቱንና ዕውቀቱን ተግባራዊ እንዳያደርግ ይገደዳል። ይህ በራሱ ደግሞ ሀብትን በስነ-ስርዓት ማዋል የሚለውን የራሱን የገበያ ኢኮኖሚ ህግ ይፃረራል። 3ኛ)በፖሊሲው ተግባራዊነት የተነሳ ለህብረተሰቡ የማይጠቅሙ(Socially Unncessary)  የመዋዕለ-ነዋይ ክንውኖች ይካሄዳሉ። እነዚህ በመሰረቱ ህብረተሰብአዊ ሀብት(Social Wealth) ፈጣሪዎች አይደሉም። 4ኛ)የመዋዕለ-ነዋይ ክንዋኔዎች የሳይንስና የቴክኖሎጂ መሰረት የላቸውም። ሳይንስና ቴክኖሎጂን መሰረት ያላደረገ መዋዕለ-ነዋይ ክንዋኔ የማደግና የመስፋፋት ባህርይ የለውም ማለት ነው።5ኛ)ይህ ሁኔታ ርስ በርሱ የተያያዘ የአገር ውስጥ ገበያ(Home Market) እንዳይዳብር ያግዳል። ይህም ማለት የገበያን ኢኮኖሚ መሰረተ-ሃሳብ ይፃረራል ማለት ነው። 6ኛ)ፖሊሲው ልዩ ዐይነት ዕውነተኛ የሆነን የኢኮኖሚ ዕድገት የሚቀናቀን ህብረተሰብአዊ ግኑኝነትን(Social Relationship) ይፈጥራል። ሀብቱን በሆነው ባልሆነው የሚያባክንና ህብረተሰብአዊ ኃላፊነት የማይሰማው የህብረተሰብ ክፍል ብቅ ይላል ማለት ነው። 7ኛ)የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊሲ በመሰረቱ እርስ በርሱ የተያያዘና ከታች ወደ ላይና፣ በሁሉም አቅጣጫ ሊያድግና ሊስፋፋ የሚችልን(Organic Growth) የኢኮኖሚ ዕድገት ይፃረራል። በሌላ አነጋገር፣ ኢኮኖሚ ዕድገትም እንደማንኛውም ተፈጥሮአዊ ዕድገት ባዮሎጂካል፣ ፊዚካልና ኬሚካላዊ ክንውን ነው። የሰው ልጅ ከተፈጥሮ ጋር በሚያደርገው ልዩ ልዩ ግኑኝነቶችና ልውውጦች በተፈጥሮ ውስጥ የሚገኙ ነገሮችን አውጥቶ ቅርፃቸውን በመለወጥ የፍጆታና ሌሎች ለምርት መሳሪያዎች የሚያገለግሉ ቴክኖሎጂዎችን ይፈጥራል፤ ያመርታልም። በሰውና በተፈጥሮ መሀከል የሚደረገው ግኑኝነት ሜታቦሊካል ክንዋኔ ነው። የኒዎ-ሊበራል ፖሊሲ እነዚህን ሳይንሳዊ መሰረተ-ሃሳቦች በመፃረር የሰውን ልጅ የፈጠራ ችሎታ ያደበዝዛል፤ አትኩሮው ወዳልባሌ ነገሮች ላይ እንዲያዘነብል ያስገድዳል። የሰው ልጅ ዕውነተኛ ታሪክን እንዳይሰራ ያደርጋል። ስለሆነም በብዙ የአፍሪካ አገሮችና በኢትዮጵያችንም ተግባራዊ የተደረገው ይህ ፖሊሲ በከፍተኛ ደረጃ ለሀብት ውድመትና ለአካባቢ መበላሸት ምክንያት በመሆን የብዙ ሚሊዮን ህዝቦችን ኑሮ በከፍተኛ ደረጃ አናግቷል፤ አጨልሟልም። 8ኛ)ከዚህ በሻገር ኢኮኖሚ ፖሊሲው ግልፅ የማያደርገው ነገር አለ። ይኸውም በገበያ ኢኮኖሚና በካፒታሊስት ስልተ-ምርት መሀከል ያለውን ልዩነት በሚገባ አብራርቶ አያስቀመጥም። ፖሊሲው በኒዎ-ሊበራል ላይ የተመሰረተ ነፃ የገበያ ኢኮኖሚን ተግባራዊ ለማድረግ ነው የሚለን ከሆነ በመሰረቱ እንደዚህ ዐይነቱ ፖሊሲ የካፒታሊዝምን መሰረተ-ሃሳብ ሙሉ በሙሉ ይፃረራል። ይህም ማለት በፖሊሲው አማካይነት ቀስ በቀስ እያለ የሚመጣ ህብረተሰብአዊ ለውጥና ግኑኝነት፣ እንዲሁም በሁሉም አቅጣጭ ሊገለፅ የሚችል የስራ-ክፍፍልና ኢኮኖሚያዊ ክንዋኔ በፍጹም ተግባራዊ ሊሆን አይችልም ማለት ነው። እንደሚታወቀው በአውሮፓ የህብረተሰብ ታሪክ ውስጥ ካፒታሊዝም በተወሰኑ የፖሊሲ መሳሪያዎች ተግባራዊ የሆነ ሳይሆን የረዥም ጊዜ የትግል ውጤት ነው። የተወሰነው የህብረተሰብ ክፍል ባሸናፊነት በመውጣት ጠቅላላውን ህብረተሰብ በሱ ርዕዮተ-ዓለማዊ የአስተሳሰብ ክልል ውስጥ በማድረግ የምርት ክንዋኔን ከተራ የሸቀጣ ሸቀጥ ምርት ወደ ተወሳሰበ የምርት ክንዋኔ በመለወጥ ጠቅላላውን ህብረተሰብ በራሱ ቁጥጥር ስር ያደረገበት ሁኔታ በጉልህ ይታያል። ስለሆነም ካፒታሊዝም በላፉት አራት መቶ ዐመታት ልዩ ልዩ ደረጃዎችን በማለፍና ርስ በርሱ በመቆላለፍ ከአገር ደረጃ አልፎ የዓለምን ህዝብ እየገዛ ነው። ይህም ማለት ካፒታሊዝም ከፍተኛ ውስጣዊ-ኃይል ያለውና በሳይንስና በቴክኖሎጂ በመደገፍና በፋይናንስ ካፒታል በመታገዝ ምርትን በብዛትና በጥራት የሚያመርት ኢኮኖሚያዊ ክንዋኔ ነው። ከዚህ ስንነሳ የእነ ዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅትና የዓለም ባንክ ኢኮኖሚ ፖሊስ በምንም ዐይነት ከካፒታሊስት የገበያ ኢኮኖሚ ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም ማለት ነው። ፖሊሲው ተግባራዊ በሚሆንበት ጊዜ የካፒታሊዝምን ዕድገት ይገታል። ጤናማ ውድድር እንዳይኖር ያግዳል።

      ከዚህ ሀተታና ማነፃፀር ስንነሳ ባለፉት ሃያ ዐመታት በአገራችን ምድር ተግባራዊ የሆነው በኒዎ-ሊበራሊዝም ላይ የተመረኮዘው የነፃ ገበያ ድህነት ፈልፋይ በመሆኑ የሚያስደንቀን አየደለም። ኢኮኖሚው 11% አድጓል ቢባልም የኢኮኖሚው እንቅስቃሴ በአገልግሎት መስክና በህንፃ ስራ ላይ ያተኮረ በመሆኑ ውስጠ-ኃይል ያለውና በሁሉም አቅጣጫ ሊስፋፋ የሚችል ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ሊካሄድ አልቻለም። በመሆኑም ስራ ለሚፈልገው በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ሰው የስራ መስክ ሊከፍትና የገቢ ምንጭ ሊሆን አልቻለም። በቂ የስራ መስክና በቂ ገቢ ካልተፈጠረ ደግሞ ስለኢኮኖሚ ዕድገት ማውራት አይቻልም ማለት ነው። በአንፃሩ ግን እንደዚሁ ዐይነቱ የኢኮኖሚ ዕድገት በሁሉም አቅጣጫ መዛባትን አስከትሏል። ምንም ሳይሰራ ሀብታም በሆነውና በሰፊው ህዝብ መሀከል ከፍተኛ የገቢ ልዩነት ሊታይ ችሏል። አዲስ ብቅ ባሉ ባለሀብቶች ሰፊው ህዝብ ከመሬቱ የሚፈናቀልበት ሁኔታ ተፈጥሯል። ይህ ዐይነቱ ሁኔታ በተለይም በአዲስ አበባ ውስጥ ተስፋፍቷል። የግል የከተማ ቦታዎችን ለልማት እንፈልገዋለን እየተባለ ብዙ ሰው ከትውልድ ወደ ትውልድ ከተላለፈ ንብረቱ ላይ ተፈናቅሏል። ሌላውን ደግሞ አስር ፎቅ ስራ እየተባለ የማይችል በመሆኑ የግዴታ ንብረቱን በአዲሱ ጉልበተኛ ባለሀብታሞች እየተነጠቀ ነው። በዚህም ዐይነቱ ህገ-ወጥ ተግባር የተበሳጨው ብስጭቱን መቋቋም ስላልቻለ ራሱን የሚገድል ብዙ ሰው እንደሆነ በጋዜጣዎች ላይ ሰፍሯል። እንደዚህ ዐይነቱን የተዛባና ህገ-ወጥ ድርጊት ራሱ መንግስት ደጋፊና የውስጥ ለውስጥ አዘጋጅ ለመሆኑ የአገሪቱ ሁኔታዎች በሚገባ ያረጋግጣሉ። ባጭሩ የዛሬው አገዛዝ ለህዝቡ አጠቃላይ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ያመጣ ሳይሆን፣ ወደ ዘራፊነት የተሸጋገረና በሁሉም አቅጣጫ በከፍተኛ ደረጃ ሚዛናዊነት እንዳይኖር ያደረገ ነው።

       በኢህአዴግ/ወያኔ የሚለፈፈውን በአሃዝ የሚሰጥ የኢኮኖሚ ዕድገት አስመልክቶ ከብዙ አቅጣጫዎች መወናበድ ይታያል። አገዛዙ ኢኮኖሚው 11% በመቶ ያድጋል ሲል፣ የለም ይህ ሊሆን አይችልም፣ ኢኮኖሚው ከ6% በመቶ በላይ ሊያድግ አይችልም እያለ የዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት ይናገራል፤ ስለዚህ በሁለቱ መሀከል ለምን ይህን የመሰለ የዕድገት ልዩነት ይታያል? ብለው ጥያቄ የሚያቀርቡ ብዙ የዋሆች እንዳሉ ከደርሱኝም ሆነ በድህረ-ገጽ ላይ ከወጡ ጽሁፎች መመልከት ይቻላል። በመጀመሪያ ይህን የመሰለ ጥያቄ የሚያቀርቡ የህዝባችንን የኑሮ ሁኔታና ድህነቱ ሳይሆን ያሳሰባቸው በሁለቱ መሀከል ስለሚታየው ቲያትር ነው። በሁለተኛ ደረጃ፣ እንደዚህ ዐይነቱ ጥያቄ ሲቀርብ ለብዙዎች ኢኮኖሚ የሚለው ጽንሰ-ሃሳብና የኢኮኖሚ ዕድገት መሰረታዊ ይዘት ግልጽ አይደለም ማለት ነው። በሶስተኛ ደረጃ፣ የአገራችን ኢኮኖሚ ፖሊሲ በምን የርዕዮተ-ዓለም መሰረት ላይ እንደተመረኮዘ ግልጽ አይደለም ማለት ነው። ስለዚህም እንደዚህ ዐይነቱ የኢኮኖሚ ፖሊሲና ዕድገት ከተወሰነ የህብረተሰብ ጥቅምና ከዓለም አቀፍ ሁኔታ በመነሳት የተነደፈ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ለመሆኑ ለብዙዎች ግልጽ አይደለም ማለት ነው።

       በመሰርቱ፣ የዓለም አቀፍ ድርጅት የወያኔን የዕድገት ዕቅድ ሲያስተባብልና የራሱን ግምት ሲሰጥ የሁለቱም ዕቅድ ሊሆን ይችላል ተብሎ የሚገመት እንጂ በእርግጥም ኢኮኖሚው በተሰጠው የአሃዝ መጠን ያድጋል ማለት አይደለም። ምክንያቱም በመሀከሉ ከመጀመሪያውኑ የማይታሰቡ ነገሮች ስለሚከሰቱ እነዚያን ቫርያብሎች ሁሉ በኢኮኖሚ ስሌት ውስጥ ማካተት አይቻልም። በተጨማሪም ራሱ የኢኮኖሜትሪክስ ስሌት በአንድ ህብረተሰብ ውስጥ ያሉ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሁኔታዎችን አዋቅሮ በሂሳብ መልክ ማቅረብና ኢኮኖሚው በዚህ መጠን ያድጋል ብሎ መናገር አይቻልም። በተረፈ የዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት ትመናውን ሲሰጥ የሚመረኮዝበት ቁጥር ከየአገሮች መንግስት የሚሰጠውን የስታትስቲክስ ዳታዎች ተመርኩዞ ነው። በየአገሩ የራሱ ተወካይ ኢንስቲቱሽኖች የሉትም። ይሁናን የየአገሩ መንግስት ራሱን ከፍ ለማድረግ ሲል አጋኖ ሲሰጥ ብዙ የማያካትታቸው ትሪንዶች አሉ። የዓለም የገንዘብ ድርጅት የዓለምን የኢኮኖሚ ሁኔታ `በተሻለ መልክ መገመት` ስለሚችል፣ የአገሪቱን የማምርት ኃይልና ከውጭ ጋር ያላትን የኢኮኖሚ ግኑኝነት በማጤንና ይህም በአገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ የሚያመጣውን ተፅዕኖ በማስላት መንግስት ካሰላው ዕድገት በታች አድርጎ ቢያስቀምጥ የሚገርምና የሚያስደነግጥም አይደለም።

      ያም ሆነ ከተራ የኮመን ሴንስ አንፃርና ከፊዚካል ኢኮኖሚ መሰረተ-ሃሳብ ስንነሳ በአንድ አገር ውስጥ የኢኮኖሚ ዕድገት መለካት ያለበት ከተጨባጭ/Physical/ ሁኔታዎች አንፃር በመነሳት ነው። ይህም ማለት በአንድ አገር ውስጥ የተሰሩ ትምህርት ቤቶች፣ ሆስፒታሎች፣ መንገዶች፣ የኃይል ማመንጫዎች፣ የንጹህ ውሃ ጉዳይ፣ የቲያትር ቤቶችና ሙዚየሞች…ወዘተ. በነፍስ ወከፍ ለእያንዳንዱ ይህን ያህል ነው የሚደርሰው ተብሎ የሚሰላ ከሆነ ይህ እንደ መሰረታዊ የኢኮኖሚ ዕድገት ሆኖ መታየት ያለበትና ትክክለኛው የአሰላል ዘዴም ነው። ይህ ብቻ ሳይሆን፣ የከተማዎች አገነባብና አደረጃጀት፣ በተለያዩ የአንድ አገር ከተማዎችና መንደሮች መሀከል የካፒታልና የተለያዩ ዕቃዎች በተለያየ መንገድ መሽከርከርና ሰፊውን ህዝብ ማዳረስ፣ እነዚህ ሁሉ በመሰረቱ እንደ ኢኮኖሚ ዕድገት መተመን ያለባቸው ናቸው። ከዚህም ሌላ በኢኮኖሚ ዕድገት ውስጥ መግባት ያለባቸው፣ ለምሳሌ አንድ አገር የመሬት መንቀጥቀጥም ሆነ ሌላ አደጋ ቢደርሳባት በአጭር ጊዜ ውስጥ አደጋ የደረሰበትን የህብረተሰብ ክፍል ለመርዳት የሚያስችላት ልዩ ልዩ የቴክኒካል ነገሮችና ቴክኖሎጂዎች ማቅረብ ትችላለች ወይ? የሚለውም በተለይም ከረዥም ጊዜ የኢኮኖሚ ዕድገት አንፃር መሰላት ያለበት ጉዳይ ነው። በተለይም በብዙ የሶስተኛው ዓለም አገሮች ይህንንና ሌሎች አንድን ህዝብ ከልዩ ልዩ አደጋዎች የሚከላከሉና፣ አደጋ በሚደርስበትም ጊዜ ለመቋቋም የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎች በኢኮኖሚ ዕድገት ውስጥና በጠቅላላው የአገር ግንባታ ክንውን ውስጥ እንደመሰረታዊና ስትራቴጂያዊ ነገሮች አይታዩም። ከዚህ በተረፈ የማይጨበጡ ግን ደግሞ ለአንድ ህዝብ ደስታን የሚሰጡ፣ ልዩ ልዩ መዝናኛዎች፣ የሊትሬቸር ዕድገት መስፋፋትና የአንባቢው ቁጥር፣ የሰው የዕውቀት ደረጃ፣ የፈጠራ ችሎታና በኮሙኒቲ ደረጃ መሰባሰብ…ወዘተ. እነዚህ ሁሉ በኒዎ-ክላሲካል ወይም በኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚስቶች የኢኮኖሚ ዕድገት ስሌት ውስጥ በፍጹም አይገቡም። በሌላ ወገን ግን የኢህአዴግን/ ወያኔንና የዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅትን ስሌት ትክክል ነው ብሎ ቢወሰድ እንኳ፣ በኢኮኖሚው ዕድገት ሳቢያ የተከሰቱ ብዙ አሉታዊ ውጤቶች/Externalities/፣ ማለትም የአካባቢ መቆሸሽ፣ የቆሻሻ መኖሪያ ቦታዎች/Slums/ መስፋፋት፣ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ህዝቦች ከቆሻሻ እየለቀሙ መብላት፣ ለጋ ሴቶች በህይወታቸው ውስጥ ደስታን ሳያዩ ሰውነታቸውን እንዲሸጡ መገደድ፣ የማጅራች መቺዎችና ሌባዎች መብዛት… ወዘተ. አደገ ከተባለው ኢኮኖሚ መቀነስ ያለባቸው ቢሆንም እነዚህ ከስሌት ውስጥ አይገቡም። ይህ ብቻ ሳይሆን፣ የኢኮኖሚ ዕድገቱን ስንመለከት በአገር ውስጥ ያልተመረቱ ብዙ ምርቶችና የህንፃ ዕቃዎች በምርት ክንውን ውስጥ በሚገቡበት ጊዜ አገር ወስጥ እንደተመረቱ ተደርገው ነው የሚሰሉት። እንደሚታወቀው በአገር ውስጥ በየመስኩ የሚመረት ተጨማሪ ምርት(Value-added) ብቻ ነው አንድ ላይ በመደመርና ካለፈው ዐመት ጋር ሲወዳደር ኢኮኖሚው በዚህ መጠን አድጓል ተብሎ ተስልቶ የሚቀርበው።

         ያም ሆነ ይህ፣ ይህ ዐይነቱ የኢኮኖሚ ዕድገት አሰላልና የኢኮኖሚ ፖሊሲ ቀደም ብለው የወጡና በተቀራራቢም መልክ ተጨባጭ ሁኔታዎችን የሚገልጹና፣ በተለይም የካፒታሊዝምን የተወሳሰበ ዕድገትና የሀብት ክምችት የሚያሳዩ አያሌ ምርምሮችና መጽሀፎችን እንዳልነበሩ በማድረግ ነው እስከዛሬ ድረስ የዓለም ማህበረሰብን ሊያወናብድ የበቃው። በመጀመሪያ ደረጃ የመርካንታሊስቶች የኢኮኖሚ ቲዎሪና ፖሊሲ አለ። በሁለተኛ ደረጃ ከእነ አዳም ስሚዝ ጀምሮ እስከማርክስ ድረስ ክላሲካል ኢኮኖሚ እየተባለ የሚጠራውና ስለካፒታሊዝም ዕድገት በሰፊው የሚያትተው ምርምር አለ። በሶስተኛ ደረጃ የታወቀው የአውስትርያውና የአሜሪካኑ ኢኮኖሚስት ሹምፔተር ስለ ኢኮኖሚ ዕድገትና ስለካፒታሊዝም የሀብት ክምችት በሰፊው የሚያትተው አለ። በአራተኛ ደረጃ፣ በቶርስታይን ቬብለን የሚወከለው የኢንስቲቱሽን ኢኮኖሚክስ አለ። በፕሮፌሰር ቬብለን ዕምነት ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ከረዥም ጊዜ የኢንስቲቱሽን ለውጥና ዕድገት ጋር የተያያዘ ነው። በሌላ አነጋገር ሰፋ ያለና የተቀላጠፈ ኢንስቲቱሽን በሌለበት አገር ውስጥ ስለኢኮኖሚ ዕድገት ማውራት አይቻልም ማለት ነው። አምስተኛ፣ በፕሮፌሰር ኤሪክ ራይነርት የተደረሰበት እጅግ ግሩም የሆነ ስለ ስልጣኔና አጠቃላይ የኢኮኖሚ ዕድገት የሚያትት ጥናት አለ። ከዚህ ስነነሳ የኒዎ-ሊበራል የኢኮኖሚ ፖሊሲ የዕድገት አሰላል ዘዴ እነዚህ ታላላቅ የፍልስፍናና የኢኮኖሚክስ ምሁራን ከሚያስተምሩን በብዙ እጅ ይለያል። ከነዚህ ምሁራን መጽሀፎች ጋር ይበልጥ መተዋወቅ ለአገራችን የኢኮኖሚና የህብረተሰብ ግንባታ ይጠቅመናል። በአንፃሩ የኒዎ-ክላሲካልንና የኒዎ-ሊበራልን የኢኮኖሚ ፖሊሲና የንግድ ቲዎሪ እየደጋገምን ተግባራዊ የምናደርግ ከሆነ አገራችን በምንም ዐይነት የስልጣኔ ብርሃንን ለማየት አትችልም። ያም ሆነ ይህ፣ ይህ ዐይነቱ በእነ ዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅትና የዓለም ባንክ የሚደገፈው የኒዎ-ሊበራል የኢኮኖሚ ፖሊሲ በአገራችን ምድር ተግባራዊ ከሆነ ወዲህ በህብረተሰቡ ላይ ያሳደረውን ተጽዕኖ ደግሞ ጠጋ ብለን እንመልከት።

  1. ፓለቲካዊ ውጤቱ!

 

             በመጀመሪያ ደረጃ የመንግስቱ መኪና በከፍተኛ ደረጃ ተጠናክሯል፤ ጨቋኝ ሆኗል። በዚህ መልክ ብቻ ነው ራሱን ሊያደልብና የሶሻል መሰረት ይሆኑልኛል ብሎ የሚገምታቸውን የህብረተሰብ ክፍሎች ሊጠቅም የሚችለው። በዚህም የተነሳ የመንግስቱ መኪና የህብረተሰቡን ሀብት በመምጠጥ ምርታማ ወዳልሆኑ ነገሮች ላይ እንዲያውል ተገዷል። ይህ ዐይነቱ አገዛዝ ወደዚህ ደረጃ የደረሰው ከላይ እንደተነተነው በውጭ አማካሪዎች ምክርና ግፊት ነው። በዚህ ዐይነት መንገድ ብቻ ነው የህብረተሰቡን ሀብት ሊመጥና የተዛባ ሁኔታ ሊፈጥር የቻለው። ስለሆነም የተወሰኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን መደጎምና ምክር ሰጥቶ ህብረተሰብአዊ መዛባት እንዲኖር ማድረግ የዓለም አቀፍ ኢንስቲቱሽኖች ዋና ተግባር እንደሆነ በብዙ አገሮች የተረጋገጠና በጥናትም የተደረሰበት ነው። በሴንተርና በፌሪፌሪ(Center/Peripherie)  መሀከል ያለው የማዘዝና የመታዘዝ ግኑኝነት በእንደዚህ ዐይነት የአሰራር ዘዴ ነው የሚካሄድውና ተግባራዊ የሚሆነው። ስለዚህም ነው በላፈው ክረምት 2010 ዓ.ም ላይ፣ ሙኒክ ከተማ ጀርመን አገር ላይ በተደረገው የሴኪዩሪቲ ስበሰባ ላይ የአሜሪካኗ የውጭ ጉዳይ ሚኒስተር ወይዘሮ ሄለሪ ክሊንተን መለስ ዜናዊ በዚያ አካባቢ ያለ የምንተማመንበትና፣ መረጋጋትን ሊያሰፍን የሚችለው የቀረን መሪ እሱ ብቻ ነው ብለው የተናገሩት። እዚህ ላይ ወይዘሮይቷ ስለሴኪዩሪቲ ሲናገሩ፣ እኛ በፈለግን ጊዜ ጦርነት የሚያካሂድልን ነው ማለታቸው እንጂ በእርግጥም ሰላም ያሰፍናል፤ ዕድገትም ያመጣል ማለታቸው አይደለም፤ አልነበረምም። ለኛ ምስኪን ህዝቦች በማሰባቸው አይደለም እንደዚህ ብለው የተናገሩት።

        ይህ ብቻ አይበቃም፤ በአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም የሚመራው ግሎባል ካፒታሊዝም የሱን እሴት ተግባራዊ የሚያደርጉለትንና ከውስጥ ደግሞ የተዛባ ሁኔታን የሚፈጥሩለትን በየዘርፉ በማሰልጠን ያሰማራል። ባለፉት ሃያ ዐመታት ይህ ዐይነቱን የህብረተሰብ ክፍል እየመለመሉ ማስገባትና ቁልፍ ቁልፍ የኢኮኖሚ ቦታዎችን ማሲያዝና የህብረተሰቡን አመለካከት ማዛባት የተለመደ ጉዳይ ነው። ለዚህ እንደዋና የሚጠቀሰው የኮሞዲቲ ገበያ የሚባለውን የአሜሪካንን የተበላሽ እሴትና የባርያ ስራ ማስፋፋቱ ሊጠቀስ ይችላል። በዚህ መልክ ልክ እንደ አሜሪካን ትላልቅ ኩባንያዎች ሴኤኦ(CEO) እየተባሉ በልዩ ልዩ የኢኮኖሚ መስክ የተሰገስጉት፣ ሀብት ፈጣሪዎችና ቴክኖሎጂ አፍላቂዎች ሳይሆኑ ድህነትን ለመፈልፈል የሚያግዙ ናቸው። አዲስ ዕውቀትን በማፍለቅ ህዝባችንን ያስተማሩ አይደሉም። በዚህም ምክንያት ቺፍ ኤኒሚ ኦፊሰር(Chief Enemy Officer) ተብለው ሊጠሩ ይችላሉ። እነዚህ አዲሱ የአሜሪካንን እሴት የሚያስፋፉ፣ በተለይም ለወጣቱ ትውልድ መጥፎ ምሳሌ በመሆን ለፈጠራ ስራ ያለውን ውስጣዊ ስሜት እንዲሟሽሽ ሊያደርጉ ችለዋል። ደላላ በመሆን፣ የአየር ባየር ንግድ ላይ በመሰማራት ዕውነተኛ ስራ ሳይሰራ እያጭበረበረ ሀብታም የሚሆንበት ሁኔታ ፈጥረውለታል። ለባህልና ሞራል መበላሽት እንዲሁም ህዝባችን እየተናቀና እየተረገጠ እንዲኖር ዋና ምክንያት ሆነዋል ማለት ይቻላል።

      በእንደዚህ ዐይነት ኢኮኖሚያዊ ኃይል አሰላለፍ ሰፊው ህዝባችን መሉ በሙሉ ነፃነቱን ተነጥቋል። መብቱን ሊያስከብርባቸው የሚችልባቸውን የተለያዩ የሲቪክ ማህበራትን እንዳያደራጅ ታግዷል። የውስጥ ለውስጥ ምን እንደሚሰራና አገሩም እንዴት እንደሚፈራርስ በሳይንስ የተጠና ጥናት ሊቀርብ የማይቻልበት ሁኔታ ተፈጥሯል። ሰፋ ያለና በራሱ የሚተማመን ምሁራዊ እንቅስቃሴ እንዳይዳብር ታፍኖበታል። በዚህ መልክ ሰፊው ህዝብ ባለስልጣን ነን በሚሉ የሚደርስበትን በደል ሊያሰማ የሚችል ኃይል የለውም ማለት ነው። ይህ ዐይነቱ ፓለቲካዊ ክፍተት የግዴታ የውጭ ኃይሎች እንደፈለጉ የአገሪቱን የዕድገት አቅጣጫ እንዲያዛንፉ በር ይከፍትላቸዋል። ታዛዥ መንግስትና የአሜሪካንን እሴት የሚያራምዱ የህብረተሰብ ክፍሎች ባህላዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ህብረተሰብአዊና ልዩ ልዩ እሴቶች እንዳያድጉና ሰፊው ህዝብ ርስበርሱ በመተሳሰር አንድ የጋራ አገር እንዳይገነባ ያግዳሉ ማለት ነው። እንደዚህ ዐይነቱ ህብረ-ብሄር በጠንካራ መሰረት እንዳይገነባ የማድረጉ ተግባር በተለይም የአሜሪካንና የእንግሊዝ መንግስታት ዋና የተንኮል ተግባር ነው። ሌሎችም የምዕራብ አውሮፓ መንግስታት በልዩ ልዩ „ዕርዳታ ሰጪ“ ድርጅቶቻቸው አማካይነት ሰርጎ በመግባትና ለብሄራዊ ኢኮኖሚ ግንባታ በማይጠቅም እዚህና እዚያ ተሰበጣጥሮ በሚገኝ ፕሮጀክት ላይ በመሰማራት፣ በአንድ በኩል ብዙ ሰዎችን ያሳስታሉ፣ በሌላ ወገን ደግሞ ህዝቡ ርስበርሱ እንዳይተማመን የብሄረሰብና የሃይማኖት ግጭቶች እንዲነሱ የውስጥ ለውስጥ ደባ ይፈጽማሉ። በተለይም በእንደዚህ ዐይነቱ ተንኮል የተካኑ የሃይማኖት „ዕርዳታ ሰጪ“ ድርጅቶች ናቸው። ከዚህ ባሻገር እነዚህ መንግስት ነክ ያልሆኑና መንግስት ነክ ድርጅቶች ስትራቴጅክ ኢንፎርሜሽን በመሰብሰብ ለየመንግስቶቻቸው ያስተላልፋሉ። ኢንፎርሜሽኑ ተጠንቶ እንደገና ለሌላ ተንኮል መጥንሰሻ ያገለግላል።

        ወያኔ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ ሆን ብሎ የተያያዘው አገሪቱን በብሄረሰብ ክልል በማካላል ህዝቡ ርስበርሱ እንዲናቆርና ብሄራዊ ስሜት እንዳይኖረው ማድረግ ነው። በተለይም የራሱን የጎሳ ሰዎች ቁልፍ ቁልፍ ቦታዎችን በማስያዝ ህብረተሰብአዊ ግጭት እንዲፈጠር በይፋና በድብቅ ተንኮሎችን ይሸርባል። የአቶ መለስና የግብረአበሮቹ አገዛዝ አገርን በክልል ከልሎ የከፋፍለህ ግዛ ፖሊሲ ማካሄድ በመሰረቱ የእንግሊዞች ስትራቴጂ ነው። አንድ አገር በአንድ ቋንቋ፣ በባህልና እንዲሁም በልዩ ልዩ ነገሮች መተሳሰር የለባትም። መብትህ ይጠበቅልሃል እየተባለ እያንዳንዱ ብሄረሰብ የራሱን ፊደል በመፍጠር በራሱ ቋንቋ እንዲማር ይገደዳል። በአንድ አገር ውስጥ የሚኖር ህዝብ ተጨማሪ የብሄረሰብ ግድግዳ ተበጅቶለት እንዳይግባባ ይደረጋል። አንድ ዐይነት አመለካከት ያለውና ልብ ለልብ የሚገናኝ ህዝብ በቀላሉ አንድ ላይ በመነሳት ጠንካራ አገር ሊገነባ ስለሚችል በዚህ ዐይነቱ የቋንቋ ብዛትና መብትህን ታስጠብቃለህ እየተባለና እየታለለ ታሪክ እንዳይሰራ ይታገዳል። እንግሊዝ ይህንን የከፋፍለህ ግዛ ፖሊሲዋን በአውሮፓ ምድር ውስጥ በ17ኛው ክፍለ-ዘመን በማካሄድ ለሃይማኖት ግጭት ዋና ምክንያት ሆናለች። በቅኝ ግዛት ዘመንም ይህንን ፓለቲካዋን በመቀጠል፣ አንዱን ብሄረሰብ አሳንሶ በመመልከትና ሌላውን ደግሞ የበላይነት ስሜት እንዲኖረው በማድረግ የረዥም ጊዜ እሳት አቀጣጥላ ሄዳለች። በመቀጠልም ጎሳ የጥናት መስክ(Subject of Study) ሆኖ ተቀባይነት እንዲኖረው በማድረግ ኤትኖሎጂ የሚባል እያንዳንዱን ጎሳ ምንነት በጥልቀት የሚያጠና የትምህርት መስክ አስፋፋች። ይህ ዐይነቱ የኮሎኒያል ፕሮጀክት ዛሬም የሚሰራበት ሲሆን፣ አፍሪካውያን እንደ አገርና እንደ ህብረ-ብሄር መታየት የለባቸውም። ማንኛውም ወደ አንድ የተጠቃለለና ወደ ህብረ-ብሄር የሚያመራ አጠቃላይ ፕሮጀክት በእንጭጩ መቀጨት አለበት። ስለዚህም ብሄራዊ ስሜት የሌላቸውን እየፈለጉና እየመከሩ በአገሬው ሰው ዘለዓለማዊ ብጥብጥ እንዲኖር ማድረግ ነው። ከዚህ ስንነሳ እነ አቶ መለስ ቢያንስ ስልጣን ከያዙ ጀምሮ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ከእንግሊዝና ከአሜሪካን እንዲሁም ከአንዳንድ የምዕራብ አውሮፓ መንግስታት ጋር በመስራት ኢትዮጵያ እንደ አንድ ህብረ-ብሄር እንዳትገነባ ልዩ ልዩ መሰናክሎችን ዘርግተዋል። ከክልል ፓለቲካው ሌላ የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊሲ ዐይነተኛ ህዝብን በታኝ ፖሊሲ ነው።

        ከዚህ ስንነሳ እያንዳንዱ ከተለያዩ ብሄረሰብ የወጣ ምሁር የእነ እንግሊዝን ርኩስ ተግባር ጠጋ ብሎ መመርመር አለበት። በታሪክ ውስጥ በአንድ አገር ክልል ውስጥ የሚኖር ልዩ ልዩ ብሄረሰብ ብቻውን በመሆን ዕውነተኛ ነፃነትን የተቀዳጀበት ቦታና ጊዜ የለም። ዕውነተኛ ታሪክና ግለሰብአዊ ነፃነት በተናጠል፣ በመጠራጠርና በመፈራራት ላይ በተመሰረተ ትግል የሚገኝ አይደለም። የሰው ልጅ በመሰረቱ ህብረተሰብአዊና ማህበራዊ ነው። ግለሰቦችም ከይትኛውም ብሄረሰብ ይውጡ ህልማቸውን ዕውን ሊያደርጉ የሚችሉት በአንድ ህብረተሰብ ውስጥና በልዩ ልዩ መስክ በማህበር ሲደራጁ ብቻ ነው። በብሄረሰቡ የሚደራጅ አንድ ግለሰብ ዕውነተኛ ነፃነቱን ሊቀዳጅ  በፍጹም አይችልም። ምክንያቱም በልዩ ልዩ መልክ የሚገለጹ ፍላጎቶቹን፣ ለምሳሌ በቲያትር መልክ፣ በሊትሬቸር፣ በሙዚቃና በሌሎች ነገሮች ደስታንም ሆነ ችግርን ወይም ሀዘንን የሚገልጹ ነገሮች ሊዳብሩና ሊያብቡ የሚችሉት ብሄራዊና ህብረተሰብአዊ ባህርይ ሲኖራቸው ብቻ ነው። ዕውነተኛ ግለሰብአዊ ነፃነት ሊገኝ የሚችለው ከብሄረሰብ ውጭ ሲታሰብ ብቻና፣ ማንኛውንም ሰው እንደ ወንድም ወይም እህት ሲታይ ብቻ ነው። ስለዚህም ነው የጀርመን ክላሲኮች እነሺለር፣ ጎተና ሌሎችም እዚህና እዚያ የራሳቸውን „ክልል“  አጥረው አንድ ህብረ-ብሄር ለማዋቀር የማይፈልጉትን የፊዩዳል አገዛዞች አጥብቀው በመቃወም ለብሄራዊ ወይም ለአገር አቀፍ ቲያትርና ሊትሬቸር አጥብቀው የታገሉት። እነሺለር እንደሚሉት ይህ ዐይነቱ ትናንሽነት (Small States= kleinstaaterei) ጀርመንን ከማዕከለኛው ክፍለ-ዘመን ጀምሮ እስከ 19ኛው ክፍለ-ዘመን መግቢያ ድረስ በዴንማርክ፣ በስዊድን፣ በፈረንሳይና እንዲሁም በአውስትሪያ፣ እንድትጠቃና እንድታደከም በማድረግ ዕድገቷን ያደናቀፈ ስለነበር የግዴታ በአዲስ አስተሳሰብና መንፈስ ላይ በመመርኮዝ ነው ለሪፑብሊክ መመስረት ያልተቆጠበ አስተዋፅዖ ያደረጉት። ይህ ብቻ ሳይሆን ዕውቀታቸውን በተግባር በማሳየትና በመመንዘር ከአንድ ትንሽ ከተማ በመነሳት ካለውጭ ድጋፍ ትላልቅ ነገሮችን መስራት እንደሚቻል አረጋግጠዋል። ልዩ ዐይነት አርክቴክቸር፣ ሙዜየምና ጋርደኖች፣ እንዲሁም የዕውቀት መስፋፊያ ቤተመጻህፍት በመስራትና በማስፋፋት በዚህ አማካይነት ስልጣኔውም ወደ ሌሎች የጀርመን ከተማዎች እንዲተላለፍ አድርገዋል። በመሆኑም እኛም ይህንን በመረዳትና ስሜታችንን በዚህ መልክ ልናረካበት የምንችልባቸውን መድረኮች ከዋና ከተማ አልፈው በአገሪቱ ምድር እንዲስፋፉና ስር እንዲሰዱ በማድረግ ህዛባችን ታሪክ የሚሰራበትንና ዕውነተኛ ነፃነቱን የሚቀዳጅበትን መንገድ መቀየስ አለብን። ህዝባችን እንዲተሳሰር መሰረቱን መጣል አለብን። የኢምፔሪያሊስቶችን አሻጥር በእንጭጩ ለመቅጨት ሳንታክት መስራት አለብን።

  1. ማህበራዊና ባህላዊ ውጤቱ!

       በተለይም ያለፉትን 60 ዐመታት የካፒታሊዝምን በዓለም አቀፍ ደራጃ መስፋፋት ስንመለከት ተልዕኮው ስልጣኔን ማምጣትና በየአገሩ የሚኖሩ ህዝቦች የኑሮ ሁኔታቸው እንዲሻሻልና እንደሰው ልጅ ክብራቸው ተጠብቆ በሰላም እንዲኖሩ ያደረገበት ሁኔታና  ቦታ በፍጹም የለም። የካፒታሊዝምም ዋና ተልዕኮ ዕውነተኛ ዕድገትን በዓለም አቀፍ ደረጃ ማስፋፋት ሳይሆን፣ ርካሽ የሰው ጉልበትና የጥሬ ሀብት ለመፈለግና፣ በዚያውም የሸቀጣ ሸቀጥ ማራገፉያ ገበያ ለመፈለግ ብቻ ነው። ስለሆነም እንደምናየው በብዙ የሶስተኛው ዓለም ተብለው በሚጠሩ አገሮች አብዛኛው ህዝብ ከእንስሳ በታች እንዲኖር የተገደደበት ሁኔታ ተፈጥሯል።

      ግሎባላይዜሽን በዓለም አቀፍ ደረጃ እየተስፋፋ ነው፣ ከዚህ ሌላ አማራጭ መንገድ የለም ከተባለልን ከ1990ዎቹ መጀመሪያ ጀምሮ ደግሞ የሶስተኛው ዓለም ህዝብ ብቻም ሳይሆን ራሱ የእንዱስትሪ አገሮች ህዝብም በኑሮ አስተማማኝ ያልሆነበት ሁኔታ ውስጥ ወድቆ ይገኛል። ሰሞኑን በኦኤሴዲ በወጣው ስታትስቲክስ መሰረት፣ የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊ ከሆነ ከሰለሳ ዐመት ጀምሮ በብዙ አገሮች በዝቅተኛውና በከፍተኛው የኢንከም ተቀባይ የህብረተሰብ ክፍል መሀከል ከፍተኛ የገቢ ልዩነት እንዳለ ነው። በገቢ ልዩነት በአንደኛ ደረጃ የተቀመጠችው ታላቋ አሜሪካ ስትሆን፣ የገቢው ልዩነት በሀብታሙና በደሀው መሀከል 27% በመቶ አድጓል። ቀጥሎ ደግሞ ቺሌና ሚክሲኮ ሲሆኑ፣ እነሱም እንደዚሁ የኒዎ-ሊበራልን ኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊ ማድረግ ከጀመሩ ወዲህ በሀብታምና በደሀው መሀከል የገቢ ልዩነት በከፍተኛ ደረጃ ይታያል። ወደ አውሮፓ ስንመጣ ደግሞ፣ ከምዕራብ አውሮፓ ውስጥ በተለይም በጀርመን ባለፈው 15 ዓመታት በታችኛውና በላይኛው የገቢ ተቀባይ የህብረተሰብ ክፍል ልዩነቱ 8% አድጓል። በሌላ አነጋገር ሀብታሙ የበለጠ ሀብታም ሲሆን፣ የሰራተኛው ገቢ ደግሞ አይ ባለበት ረግቷል፤ ወይም ደግሞ ዕድገቱ ይህን ያህልም አልጨመረም ማለት ነው። እንግዲህ እዚህ ላይ የጀርመን ኢኮኖሚ በአሁኑ ጊዜ ውስጠ-ኃይሉ ከፍተኛ ነው በሚባልበትና፣ በዓለም አቀፍ ደረጃም በብዙ ዘርፎች ተወዳዳሪ በሆነበት ወቅት ነው እንደዚህ ዐይነቱን ዜና ከኦኤሴዲ የሚነገረን።

       ወደ አገራችን ስንመጣ ደግሞ የአገራችን ህዝብ የማህበራዊ ሁኔታ በብዙ እጅ አስተማማኝ ያልሆነበት ሁኔታ ውስጥ ይገኛል። በመጀመሪያ ደረጃ የአገራችን ኢኮኖሚ በተለየ መሰረትና ህግ የሚንቀሳቀስ ነው። ውስጠ-ኃይሉ ደካማ ስለሆነና መስፋፋት ስለማይችል ሾል ለሚፈልገው የስራ መስክ ሊከፍት አይችልም። ከዚህ ስንነሳ በሁለተኛ ደረጃ፣ አብዛኛው ህዝብ ተከታታይና አስተማማኝ ገቢ የለውም። ከአንድ ፐርሰንት የማይበልጥ ቤተሰብ ከውጭ በሚላክለት ድጎማ ነው የሚኖረው። ይህም ማለት አብዛኛው ህዝብ የሚቀምሰውና የሚልሰው የለውም ማለት ነው። ጠንካራና ሰፋ ያለ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች በሌሉበት አገር ውስጥ ሌሎች ለህብረተሰቡ የሚጠቅሙ የማህበራዊ ነገሮችና ሶሽል ኔትወርክስ ለማቋቋምና ሰፊውን ህዝብ ለመደጎም በፍጹም አይቻልም። መንግስት ልሹ በገቢው በጣም ደካማና ተመጽዋች በመሆኑ በተለይም በእድሜ የገፋውን ህዝብ ሊረዳ በፍጹም አይችልም ማለት ነው። በተለይም የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊ መሆን ከጀመረ ወዲህ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ሁሉ በተወሰኑ ነገሮችና አካባቢዎች ላይ ብቻ ያተኮረ በመሆኑ በተለይም የገጠሩ ህዝብ በጣም እንዲጎዳ ተደርጓል። ከዚህ በተረፈ የሚሰሩት ስራዎች፣ ማለትም ትምህርት ቤቶችና ክሊኒኮች ደግሞ በኢኮኖሚ ድክመት የተነሳ አንደኛ፣ ጥራት የላቸውም፣ ሁለተኛ፣ ተከታታይነት የላቸውም። ስለዚህም በአስተማማኝ ሁኔታ ሰፊውን ህዝብ ሊያዳርሱ በፍጹም አይችሉም። ሌሎች የንጹህ ውሃ ማግኘት፣ የመጸዳጃ ጉዳይ፣ በጥራትና በብዛት ለሰፊው ህዝብ መኖሪያ ቤት መስራት አለመቻል፣ አሁን በተያያዘው ልዩ ዐይነት የሀብት ሽግሽግ ስፊው ህዝብ ከቦታው መፈናቀልና የተቀረው ደግሞ በእርግጠኝነት ለመኖር አለመቻል … ወዘተ.  የአገራችን ህዝብ በምን ዐይነት የማህበራዊ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኝ ነው የሚያረጋግጠው።

        የተስተካከለ የኢኮኖሚ ዕድገት በሌለበት አገር ውስጥ አስተማማኝ ማህበራዊ ኑሮ መመስረት እንደማይቻል ሁሉ፣ ቤተሰብና ማህበራዊ ሁኔታ ከተናጋ ደግሞ የአገሪቱ እሴቶች የሆኑት  መከባበርና መረዳዳት የመሳሰሉት የባሰውኑ ደብዛቸው ይጠፋል። ውሸት፣ ሌብነት፣ በግልጽ ዘረፋና ጉቦኝነት፣ ራስንና ቤተሰብን ለማዳን ሲባል የራስን ሰውነት መሸጥ፣ ወደ መጠጥና ወደ ሌሎች ለጤንነት አደገኛ የሆኑ የሚጨሱ ነገሮች ላይ መሰማራትና ራስም መነገድ፣ ቀስ በቀስም ማፍያዊ የሆኑ ተግባሮች መስፋፋት፣ በተለይም ደግሞ ለመኖሪያ የሚሆኑ የቆሻሻ ቦታዎች መስፋፋትና እነዚህ ቦታዎች ለማፍያና ለስርቆት አመቺ መሆን… ወዘተ. የአገሪቱን ጠቅላላ እሴት ሊያናጋው ይችላል ማለት ነው። በተጨማሪም፣ ከሃያ ዐመት በፊት በአገራችን ተሰምቶም ታይቶም የማይታወቅ ልዩ ዐይነት የወሲብ ግኑኝነትና አገሪቱ ይህንን አስቀያሚ ነገሮች ሊያስፋፉ ለሚችሉ ልቅ በመሆኗ የአገራችን እሴት ወድሟል። የሃያ ዐመቱ የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊሲና ግሎባል ካፒታሊዝም እንደዚህ ዐይነቱን ቆሻሻ ነገር ነው ያሰተማሩን። ስልጣኔን ሳይሆን ውርደትን እንድንከናነብ ነው ያደረጉን። ከእንስሳ በታች እንድንቆጠርና ዘለዓለም ፍርፋሪ እየተጣለልን እንድንኖር ነው የተደረግነው። ይህ ደግሞ በመሰረቱ በእግዚአብሄር አምሳል የተፈጠረውን ዐይነተኛ ባህርያችንን፣ ማለትም ቆንጆ ቆንጆ ነገሮችን መስራትና ከተፈጥሮ ጋር ተፋቅረን በሰላም መኖር ያለብንን ውስጣዊ ፍላጎታችንን ይፃረራል። ከዚህ ስንነሳ የአገዛዙን አስተሳሰብ በመጠኑም ቢሆን እንቃኝ።

     ለምን ወያኔ ይህንን የጥፋት ፖለቲካ እንዲከተል ተገደደ ?

             እንደዚህ ዐይነቱን የፖለቲካ ስልት ለመተንተን የሚያስችል የሶሶይሎጂ ወይም የፖለቲካል ቲዎሪ ፍልስፍና ያለ አይመስለኝም። በመሰረቱ እንደዚህ ዐይነቱን የተወናበደና አገር አጥፊ ፖሊሲ ለመመርመር የሳይኮሎጂስቶችና የኖይሮ ባዮሎጂስቶች ተግባር ነበር። በዚህ ረገድ አልቦ ዕውቀት ስላለኝ አጥጋቢ መልስ ለመስጠት ያዳግተኛል። ይሁንና ከባህልና ከህብረተሰብአዊ የባህል ዕውቀት በመነሳት አንዳንድ ነገሮች ማለት የሚቻል ይመስለኛል። ይህንን በሚመለከት፣ ወደ ሌላ ነገር አይተርጎምብኝና፣ የዛሬው አገዛዝ በአማዛኙ ከትግሬ ሳይሆን፣ ከኦሮሞ ወይም ከአማራ፣ ወይም ከሌላ ብሄረሰብ የተውጣጣ ቢሆን ኖሮ እንደዚህ ዐይነቱን የፖለቲካ ስልት ይከተል ነበር ወይ?  ጥያቄው ሂፖቴቲካል ስለሆነ ለመመለስ አስቸጋሪ ነው። ይሁንና ግን የኢትዮጵያ ስልጣኔ ዋናው ምንጭ ከሆነና፣ የክርስቲያንን ሃይማኖት ከተቀበለ ህዝብ አብራክ ውስጥ የወጣ ነፃ አውጭ ድርጅት ነኝ ከሚል እንደዚህ ዐይነቱን አገርን አጥፊ ፖለቲካ እንዲከተል ምን አስገደደው ?

              ከብዙ የፖለቲካ ተንታኞች የሚቀርብ አንድ የተለመደ አጻጻፍና አባባል አለ። ይኸውም አገዛዙ አምባገነን ስለሆነ ነው እንደዚህ ዐይነቱን ፖለቲካ የሚያካሂደው የሚል ነው። የወያኔን የፖለቲካ ስልትና ሂደት በአንድ ቃል መግለጽ የማይቻል ብቻ ሳይሆን፣ በጣም አደገኛ ነው። ምክንያቱም በብዙ የሶስተኛው ዓለም አገሮች የተለያዩ አምባገነን መንግስታት እንደነበሩና ዛሬም እንዳሉ እናውቃለን። ስታሊንና ሂትለርም አምባገነኖች ተብለው ይጠራሉ። ይሁንና እነዚህን በተለያየ የታሪክ ወቅትና በተለያየ የህብረተሰብና የባህል አወቃቀር ውስጥ ተወልደው ያደጉትን ሁሉ በአንድ ቃል አጠቃሎ መጥራት በጣም ስህተት ነው። በተጨማሪም ድርጊታቸው ሰውን በመግደልና በመጨፍጨፍ ተመሳሳይነት ቢኖረውም፣  አገርን በመገንባትም ሆነ በማፍረስ ፖለቲካቸው በብዙ እጅ ይለያያሉ። ስታሊንም ሆነ ሂትለር በአነሳሳቸው አገሮቻቸውን እናሳንስ ወይም እንከፋፍል ብለው አለተነሱም። የሁለቱም አነሳስና ርዕዮተ-ዓለም ቢለያይምና ከፍተኛ ጉዳትም ቢኖረው፣ አገሮቻቸውን ትልቅ ለማድረግ ነው የተነሱት። ወያኔ ግን ሆን ብሎ የተያያዘው በሁሉም አቅጥጫ አገርን ማዳከምና ህዝቡን በመከፋፈል ርስበርሱ እንዲበጣበጥና በዚያው መጠንም በቀላሉ ለውጭ ወረራ እንዲያመች ነው። ይሁንና ግን አንድ ማለት የሚቻል ነገር ያለ ይመስለኛል። በአብዛኛዎቹ አምባገነናዊ አገዛዝ ሰፍኖባቸዋል በሚባሉ የሶስተኛው ዓለም አገሮች በሙሉ አንድ ተመሳሳይነት ያለ ይመስለኛል። 1ኛ) ሰፋ ያለ ጭንቅላትን የሚያድስ የባህል እንቅስቃሴ የማድረግ ዕድል አላገኙም። ይህም ማለት አምባገነን የሚባሉት ድርጊታቸው የባህላቸው ነፀብራቅ ነው እንጂ አብሯቸው የተወለደ አይደለም። 2ኛ) ስለሆነም ሰፋ ያለ በስራ ክፍፍል ላይ የተመሰረተ የኢኮኖሚ ተቅዋም የላቸውም። 3ኛ) በስርዓቱ ላይ ጫና ማድረግ የሚችል የከበርቴ መደብ የለም። 4ኛ) ከዚህ ጋር ተያይዞ ሰፊ የሲቪክ ማህበር እንቅስቃሴ የለም። ቢያንስ እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ነገሮች በሌሉበት አገሮች በሙሉ ስልጣንን ተጠቅመው የራሳቸውን ፍላጎት ተግባራዊ ለማድረግ የሚፈልጉ ግለሰቦች አጋጣሚዎችን በመጠቀም አምባገነናዊ አገዛዝን ያሰፍናሉ። የስታሊንና የሂትለርም አነሳስ እንደዚሁ ከሶሽዮ-ኢኮኖሚ ሁኔታ ኋላቀርነት ጋር፣ በተለይም ሰፋ ያለ የነቃ የህብረተሰብ ኃይል ካለመኖር ጋር የተያያዘ ነው። የራሽያ አብዮት በ1917 ዓ.ም ሲፈነዳ፣ ራሽያ በአማዛኙ ኢኮኖሚዋ በእርሻ ላይ የተመሰረተና ሚድል ክላስ የሚባል የህብረተሰብ ክፍል አልነበራትም። ጀርመንም እንደዚሁ በጣም ዘግይታ ነው የኢንዱስትሪ አብዮት ማካሄድ የጀመረቺው። በፕረሽያ አገዛዝ የተዋቀረው ትራዲሽናል የሚሊታሪ ሂራርኪና በጣም ደካማ የነበረው የከበርቴ መደብ ለሂትለር አነሳስ አግዞታል ማለት ይቻላል። በተጨማሪም በጊዜው የነበሩት የተለያዩ ዲሞክራቲክ ፓርቲዎች፣ በተለይም ሶሻል ዲሞክራቶችና ኮሙኒስቶች አብሮ ለመስራት አለመፈልግና የጋራ ግምባር መመስረት አለመቻል ሂትለር ስልጣንን እንዲይዝ መንገዱን ከፍቶለታል። ያም ሆነ ይህ በየአገሩ የሚነሱ አምባገነን አገዛዞች የታሪክ ውጤቶችና የባህል ኋላ-ቀርነት ክስተቶች ናቸው እንጂ አምባገነን ሆነው የተፈጠሩ አይደሉም።

      በመጀመሪያ ደረጃ እነ መለሰ ዜናዊ ወደ ጫካ ሲገቡ የተወሰነ ርዕዮተ-ዓለም ይዘው የገቡ ቢመስልም፣ በአካባቢያቸው ከነበሩ ግለሰቦች በእርግጥ እንደሰማነው በአማራው፣ በተለይም ደግሞ በሸዋ አማራ `የበላይነት` ተቆጭተው እንደገቡ በጊዜው በቅርቡ የነበሩ ይመስክራሉ። ይህ ጥላቻና ቂም በቀል ከደማቸው ጋር ተዋህዷል ማለት ይቻላል። ከዚህ ጋር ተደምሮ በስራ-ክፍፍልና በዕድገት ያልዳበረውና ከህብረተሰብም ዕድገት አኳያ ሲታይ ብዙም ከሌላ ህዝብ ጋር ለመቀላቀል ዕድል ያላገኘ ከአንድ ብሄረሰብ የተውጣጣ ድርጅት ወደዚህ ዐይነቱ የጥላቻና የቂም በቀል አደገኛ የትግል ስልት መሸጋገሩ የሚደንቅ አይደለም። ድርጀቱ ልክ እንደሌሎች ብሄራዊ ባህርይ ካለቸውና ከተለያዩ ብሄረሰብ እንደተውጣጡት ዐይነት በዕምነት ደረጃ የተቋቋመ ስላልሆነ የግዴታ የዝቅተኝነት ወይም የመናቅ መንፈስ ማሳደሩ አያስገርምም። በሌላ አነጋገር ፖለቲካዊ ዕምነት የሌለውና አንድን ህዝብ በመንፈስ ኃይል ነፃነት እንዲወጣ አግዛለሁ ብሎ የተነሳ አይደለም። ርዕዩ የጠባብ ብሄረሰብ ርዕይ ነው እንጂ ግለሰብአዊ ነፃነትን ማበልፀግና አንድ ህዝብ በጋራ ተነሳስቶ ለጋራ ዓላማ እንዲታገል ማድረግ አልነበረም ዋና ዓላማው። ከዚህ ጋር ተያይዞ አስራ ሰባት ዐመት ያህል በጦር ሜዳ ውስጥ ከርሞ የራሱን የትግል ጓደኞች ሳይቀር እያሰቃይ ከገደለ፣ 20 ዐመት ያህል ካየነውና ከለመድነው የተለየ ፖለቲካ ልናይ በፍጽም አንችልም። ሶሻላይዜሽን የሚባል ነገር አለ። ይኸውም አንድ ሰው ወይም ድርጅት በአንድ አካባቢ ሁል ጊዜ ተመሳሳይ ነገር ካደረገና በዚያ አካባቢ ጭንቅላቱን የሚያድስና የሚገራ ነገር ካላየ በዚያ ዕምነቱ ወይም የአሰራር ስልቱ ይቀጥላል። ይህን እንደኖርማል አድርጎ በመውሰድ የህይወቱ አንድ ክፍል ያደርገዋል። ለሰው ልጅ ጥሩ ነገር መስራትና ሰውን ማስደሰት ሳይሆን ዋና ምኞቱ፣ ሰውን ማበሳጨት፣ ማሰቃየትና መግደል ተግባሩ አድርጎ በመውሰድ ደስተኛ የሚሆን ይመስለዋል። እንደዚህ ዐይነቱን ሰው ወይም ድርጅት አዲስ ሁኔታ ውስጥ ቢከቱትም ከአዲሱ ሁኔታ ጋር ተለማምዶ ሰብአዊ ባህርይ ለማግኘት በጣም ይከበደዋል። በተለይም በድርጅት መልክ እስከተደራጀ ድረስ ጥቃት ይደርስብኛል በማለት የባሰ በአረመኔ ተግባሩ ይገፋበታል። ለዚህ ነው እዚህ ምዕራብ አውሮፓ የሰለጠነ ህብርተሰብም ውስጥ ተወልደው ያደጉ እንኳ በቤተሰብ አካባቢ በጣም ሶሻላይዝድ ስለሚሆኑ እነሱ ከሚፈልጉት ውጭ እህታቸው ሌላ ወንድ ከተዋወቀች ወይም ካገባች የክብር ግድያ እየተባለ ትገደላለች። ይህ በኩርዶች ወይም በቱርኮች ዘንድ የተለመደ መጥፎ `ባህል` ነው። የፓትሪያሪካል ቤተሰብ ስለሆነ ሴት ልጅ ቤተሰቦቿ ወይም ወንድሟ የሚሏትን ሁሉ አሜን ብላ መቀበል አለባት። በአገራችንም እንደዚሁ፣ ያውም አዲስ አበባ እየኖሩ ሎጆቻቸው ከሌላ ብሄረሰብ የመጣ/የመጣች ማግባት እንደሌለባቸው እንደባህል የሚታይ፣ በተለይም በትግሬው የብሄረሰብ የህብረተሰብ ክፍል የተስፋፋ ነው። የሚያፈቅሩትን ማግባት የተከለከሉ ከፍተኛ የህሊና በሽታ ውድቀት ውስጥ እንደሚገኙ አልፎ አልፎ እንሰማለን። ይህም ማለት የተሻለ ባህልና ሁኔታም የማይለውጣቸው አሉ ማለት ነው። በሌላ አነጋገር የቤተሰብ ጭነት ያለበት ባህላዊ አሰተዳደግና ሶሻላይዜሽን የሰውን ጭንቅላት በመጥፎም በጥሩም ሊቀርጹት ይችላሉ ማለት ነው።

       ከሰፊው የህብረተሰብ አወቃቀር አንጻር ስነሳ ደግሞ በአንድ አገር ውስጥ በማውቅም ሆነ ባለማወቅ ከውጭ የመጣና የተስፋፋ ባህልና ኢኮኖሚያዊ ግኑኝነት የአንድን ህብረተሰብ ጭንቅላት የማደስ ኃይላቸው ደካማ እስከሆነ ድረስ ልዩ ዐይነት አስተሳሰብንና ድርጊትን ይፈጥራሉ። አስርና ሃያ ዐመት ያደግንበትን የተጣመመ አስተሳሰብ በዚያው ያደነድኑታል ማለት ነው። ችኮነት፣ አልበገርም ባይነት፣ አውቃለሁ ባይነትና የሌላውን ሰው ሃሳብ እስቲ ላዳምጥ ብሎ ገት አለመኖር፣ ጮሌነትና አራዳነት፣ መሸወድ፣ ሌላውን አላዋቂ አድርጎ መመልከት፣ ተንኮልን ማስቀደም፣ መተማመን እንዳይኖር የሰውን ስም ማጥፋት፣ ርሾ በርስ መጠራጠርና በግልጽ አለመነጋገር … ወዘተ. እነዚህ ሁሉ ወደ ኋላ የቀረ አስተዳደግና የዘመናዊ ጥራዝ ነጠቅ አመለካከት ጥምሮች ናቸው የወያኔን አገዛዝ ባህርይ ሊገልጹ የሚችሉት። ሰሞኑን ደግሞ ከአንዳንድ የድርጅቱ አባል ከነበሩና አምልጠው ከወጡ የሚነገረን ማፊያዊ ባህርያቸውና ተግባራቸው፣ እንዲሁም የወደፊቱ አጀንዳቸው እናራምዳለን ይሉት ከነበረው የማርክሲዝም ሌኒኒዝም ርዕዮተ-ዓለም ጋር በፍጹም እንደማይጣጣሙ ነው። እነዚህ ሁሉ አንድ ላይ በጣመርና፣ ራስን ለማዳን ሲባል ከውጭ ኃይል ጋር በማበርና የእከክልኝ ልከክልህ ፖለቲካ ማራመድ ልዩ ዐይነት በቀላል የትግል ዘዴ ሊፈታ የማይችል አደገኛ ሁኔታ ፈጥሮብናል ማለት ነው። ስለሆነም ትግላችን ለዕውነተኛ ነፃነትና አንድ ጠንካራ አገር መገንባት እስከሆነ ድረስ፣ ከሊበራል ዲሞክራሲና ከመደብለ ፓርቲ የፓርሊሜንተሪ ዲሞክራሲ የትግል ስልት ባሻገር መሆን አለበት ማለት ነው። በጣም የተወሳሰበ፣ ከፍተኛና ሁለ-ገብ የሆነ ጭንቅላትን የሚፈውስና የሚያጸዳ የትግል ዘዴ መሆን አለበት ማለት ነው። በሌላ አነጋገር፣ እንደሬናሳንስ ዐይነት፣ በሊትሬቸር፣ በግጥም፣ በሙዚቃ፣ በስዕል፣ በአርክቴክቸርና በከተማዎች ግንባታ ሊገለጽ የሚችል ሰፋ ያለ ባህላዊ እንቅስቃሴ ማካሄድ እስካልቻልን ድረስ የኢትዮጵያ ህዝብ ዕውነተኛ ነፃነቱን በፍጹም ሊቀዳች አይችልም። ይህንን ስንረዳ ብቻና የኛንም የእስካሁኑን የትግል ዘዴ መመርመር ስንችል አገራችንን ከዛሬው የአገዛዝ መዥገር ማላቀቅ እንችላለን ማለት ነው።

 ውስብስቡ የአገራችን ተጨባጭ ሁኔታና የኛ ተግባር !

      ጠጋ ብለን የአገራችንን ችግር ስንመለከትና ስንመረምር በቀላሉ የምንወጣው መስሎ አይታየኝም። ፓለቲካዊ፣ ህብረተሰብአዊና ማህበራዊ፣ የህሊና ቀውስና የቤተሰብ የአገር ባህል መከስከስ፣ ወጣቱ ትውልድ ይዞ የሚጓዘውን ዓላማ ማጣትና በተለይም ባሁኑ ወቅት የወላጆቹ ሸክም መሆን፣ ሌብነትና ማጅራች መችነት ተስፋፍቶ በተለይም አቅም በሌላቸው እናቶቻችንና አባቶቻችን ላይ የሚያደርሰው የፍርሀት ኑሮ፣ ልዩ ልዩ ዘመናዊ በሽታዎች መስፋፋትና እነዚህንም በቀላሉ ማከም የማይቻልበት ሁኔታ መፈጠር፣ ከፍተኛ የአካባቢ መቆሸሽና፣ በተለይም በከተማዎች ውስጥ ተስፋፍቶ የሚታየው የቆሻሻ መጣያ መብዛት… ወዘተ. በአጭሩ እኛን የሚመለከቱና መልስም የሚጠይቁ ችግሮች ናቸው። ከዚህም በላይ የብሄራዊ ነፃነታችን መከስከስ ጉዳይ አለ።

      የአገራችን የተወሳሰቡ ችግሮች በማወቅም ሆነ ባለማወቅ በየኢፖኩ ስልጣን በጨበጡና አገሪቱን በሚያስተዳድሩ አገዛዞች የተሰሩና የሚሰሩ ስህተቶች ናቸው። በተለይም ጣሊያን ለሁለተኛ ጊዜ  አገራችንን ከወረረችና ድል ተመታ ከተባረረች በኋላ የአፄው አገዛዝ መማር የነበረባቸው መሰረታዊ ነገሮች ነበሩ። አንድ አገር በሌላና በተሻለ ኃይል በቀላሉ ልትወረርና ልትጠቃ የማትችልበትን ሁኔታ ተገንዝቦ ዘላቂና ፍቱን መፍትሄ መውሰድ ነበረበት። ይህን ባለማድረጉ አገራችንን ለአደጋ አጋልጦ አለፈ። ከዚህም ስንነሳ አንድ አገር እንደ አገር መታየት የማትችለው፣  1ኛ) የኢኮኖሚዋ መሰረት እጅግ በጣም ደካማ ከሆነ፣ ይህም ማለት በሳይንስና በቴክኖሎጂ ላይ ያለተመሰረተ ከሆነ፣ 2ኛ) በደንብ የተዘጋጁ ከተማዎች ከሌሏትና፣ ህዝቡም እዚህና እዚያ ተበታትኖ የሚኖር ከሆነ፣ 3ኛ) ሰፋ ያለ የተማረ-ኃይልና የሲቪክ ማህበረሰብ ከሌላት፣ ከዚህ ጋር ተያይዞ ተወዳዳሪ ሊሆን የሚችል የከበርቴ መደብ ከሌላት፣ 4ኛ) በደንብ የተደራጀ የጦር ኃይል ከሌላት፣ 5ኛ) ይህንን ሊያግዝ የሚችል የጦር መሳሪያ ፋብሪካ ከሌላት በቀላሉ በውጭ ኃይሎች ልትጠቃ ችላለች። ስለሆነም አገራችን ከአንዴም ሁለቴም በጣሊያን ተወራለች። አፄው ስልጣን ከያዙ በኋላ የራሳቸውን አገዛዝ ከማደላደል በስተቀር ህብረተሰቡን የሚያስተሳስርና አገራችን በማንም የውጭ ኃይል እንዳትደፈር የወሰዱት አመርቂ የኢኮኖሚ ግንባታ እርምጃ የለም። በ1950ዎቹ መጀመሪያ ላይ የተነሱት እንደ ደቡብ ኮርያ የመሳሰሉት አገሮች በጣም ብልህ የሆነ በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ የኢኮኖሚ ግንባታ በማካሄዳቸውና የወታደር ኃይላቸውን በጥንቃቄ ስለገነቡና ለሰላይ ክፍት ስላላደረጉ ዛሬ ማንም የሚያየው የኢኮኖሚ ዕድገት ደረጃ ላይ መድረሳቸው ብቻ ሳይሆን፣ አገራቸው በቀላሉ የማይደፈርና ህዝባቸውም በሄደበት ቦታ ሁሉ የሚከበር ሊሆን ቻለ። ስትራቴጂያዊ በሆነ መልክ ማሰብ ያልቻለው ንጉሳዊ አገዛዝና ቢሮክራሲው ግን በጊዜው መወሰድ የነበረበትን የመስተካከያና የማሻሻያ እርምጃ ተግባራዊ ማድረግ ባለመቻሉ ከፍተኛ የፖለቲካ፣ የማህበራዊና የህብረተሰብ እንዲሁም የኢኮኖሚ ክፍተት ጥሎ አለፈ። የመጨረሻ መጨረሻም እየገፋ የመጣውን ኢኮኖሚያዊም ሆነ ማህበራዊ ቀውስ ሊቋቋም ባለመቻሉ እየተንገዳገደ ሊወድቅ ቻለ።

         በዚህ ዐይነት እጅግ በደቀቀና ከፍተኛ የሆነ ንቃተ-ህሊናና የህብረተሰብ ኃይል በጎደለበት ህብረተሰብ ውስጥ የተፈጠረው ደርግ በግራው እንቅስቃሴ ተገፋፍቶ አንዳንድ መሰረታዊ እርምጃዎችን መውሰድ ቢችልም፣ እሱም እንደ አፄው ስትራቴጂያዊ በሆነ መልክ ማሰብ የማይችል በመሆኑ ተገዶም ሆነ በራሱ ውስጥ ባለው የሚሊታሪ ባህርይ ከፍተኛ የሆነ የህብረተሰብ ውዝግብ ጥሎ አልፏል። በተጨማሪም የቅራኔዎችን ህግጋት በደንብ መገንዘብ ያቃተው አንዳንድ የግራው ኃይል ህዝቡን በወዳጅና በጠላት ሰፈር ውስጥ በመለየትና የማያስፈልግ ሽኩቻ በመፍጠር በአንድ መንፈስና ዓላማ ተነሳስቶ አገሩን ሊገነባ የሚችለውን ሰፊ ኃይል እንዲበታተን አድርጓል። በመጀመሪያ መፈታት የነበረባቸውን የህብረተሰቡን መሰረታዊ ችግሮች ወደ ጎን በመተውና፣ ፖለቲካ የሚባለውን ግን ደግሞ በደንብ ሳይብላላና በሰፊው ውይይት ሳይደረግበት ወደ ሰፊው ህዝብ የተበተነውን በማስቀደም ሁሉም ወደ ሽኩቻ ዓለም አመራ። ይህ ዐይነቱ ስህተት እንዴት ሊመነጭ ቻለ ?

               ወደድንም ጠላንም እስከተወሰነ ደረጃ ድረስ የደርግን የፖለቲካ ሂደት የግራው እንቅስቃሴ ተጽዕኖ አሳድሮበታል። የግራው እንቅስቃሴ ደግሞ የቀሰመውና ያዳባረው የፖለቲካ ቲዎሪና ስትራቴጂ ነበር። ይህም ማቴሪያሊስት ሲሆን፣ በአንድ አገር የሚገኝ የምርት ግኑኝነትና ስልተምርት የፓለቲካ አገዛዙን ባህርይና ፓለቲካውን ይወስናል የሚል ነው። ስለሆነም በማርክሲስት ቲዎሪ መሰረት፣ የአገዛዙን የማቴሪያል መሰረት ከተናጋና ስልጣን ከተጨበጠ ሌሎች የህብረተሰቡን ችግሮች መፍታት ይቻላል የሚል ቀላል መልስ ነው። ይህ ዐይነቱ አስተሳሰብ ምናልባት የዓለም ፖለቲካ ባልተወሳሰበበት ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት በፊት ሊሰራ ቢችልም፣ ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት በኋላ፣ በተለይም በ70ዎቹ ዐመታት ሊሰራ አይችልም። በተለይም የህብረተሰብ ኃይሎች ባልነቁበትና ባልዳበሩበት፣ እንዲሁም አንዳንድ ኃይሎች በቀላሉ በሚያፈነግጡበትና የኢምፔርያሊስት ጉያ ውስጥ ወድቀው ችግር ሊፈጥሩ በሚችሉበት ወቅት እንደ ኢትዮጵያ በመሰለው አገር ተግባራዊ ማድረግ አስቸጋሪ ነበር። በሌላ ወገን ግን ይህ ዐይነቱ የማርክሲስት የማቴሪያሊስት አቀራረብ እስከተወሰነ ደረጃ ድረስ ትክክል ነው ብለን ብንቀበልም፣ የማቴሪያል ሁኔታዎችም ሆነ የህብረተሰብ ግኑኝነቶች አብዛኛውን ጊዜ ባለማወቅ የሚዋቀሩበት ሁኔታ ይኖራል። በሌላ አነጋገር አብዛኛውን ጊዜ ሰዎች ይህ ያዋጣናል ብለው ከመጀመሪያውኑ አውቀው በከፍተኛ ንቃተ-ህሊና ታሪካቸውን የማይሰሩበት ሁኔታ አለ። ይህም ማለት ህብረተሰብአዊ ግኑኝነቶችና የተወሰኑ ስልተምርቶች በታሪክ ሂደት ውስጥ በአጋጣሚና ቀስ በቀስም አንደኛው ኃይል አሸናፊ ሆኖ ሲወጣ የሚቀናጁ እንጂ ከመጀመሪያውኑ የታቀዱ አይደሉም። ከዚህ ስንነሳ በአንድ ህብረተሰብ ውስጥ፣ በአንድ የታሪክ ወቅት አገዛዙም ሆነ ህብረተሰቡ አንድ ወደ ኋላ የሚጎትትና ለዕድገት ፀር የሆነ የህብረተሰብ ግኑኝነትና የማቴሪያል ሁኔታን ለምን ሊፈጥሩ ይችላሉ? የሚለውን ፕላቶናዊ አቀራረብ እንድንዘነጋ ያደርገናል። ስለሆነም አንድ ህዝብና አገዛዝ በአንድ የታሪክ ወቅት በሚፈጠር ህበረተሰብአዊ ግኑኝነትና የአሰራር ስልት እስረኛ ይሆናሉ። ለምን ካሉበት ሁኔታ ርቀው ማሰብ አይችሉም? ለምንስ በራሳቸው አነሳሽነት መሰረታዊም የሆነ የጥገና ለውጥ ማምጣት አይችሉም?  የሚሉትን ጥያቄዎች የተማሪው ማህበር በጊዜው ለማንሳት አልቻለም ነበር። ከዚህ በተረፈ እንደምገምተው ከሆነ የተማሪውን እንቅስቃሴ በተለይም የሌኒን አባባል፣ „የአብዮት ዋናው ጥያቄ የስልጣን ጥያቄ ነው“ የሚለው ሳያሳስተው የቀረ አይመስለኝም። ይህ መፈክር ስልጣንን ለመያዝ ችኩል አድርጎታል።

       ከዚህ ስንነሳ የማገኘው መልስ፣ ከዛሬው ካለኝ የንቃተ ሁኔታ ስነሳ፣ ሺለር እንደሚለው ተፈጥሮ መዝለልን ስለማታውቅና፣ ( Nature does not know how to jump) እንደዚሁም ህብረተሰብም እንደ ተፈጥሮ መጓዝ ያለበት ሂደት ስላለ በኃይል የሚደረግ ነገር ሁሉ በቀላሉ ሊታረም የማይችል ህብረተሰብአዊ ውዝግብ ውስጥ ይከታል። ለዚህም ነው ከግሪክ ስልጣኔ ጀምሮ እስከሪናሳንስ ድረስ በአንድ ህብረተሰብ ውስጥ ለውጥ ለማምጣት የግዴታ የአስተሳሰብ ለውጥ ማምጣት እንደሚያስፈልግና፣ በተለይም ፕላቶ እንዳለው የሰው ልጅ ችግር የዕውቀት ወይንም በትክክል የማሰብ ችግር ስለሆነ የሰዎችን ጭንቅላት በትክክለኛ ዕውቀት መቅረጽ ያስፈልጋል ያለው። ይህ ጥበባዊ የሆነ ለውጥን የማምጣት ዘዴ በመጀመሪያ በግሪክ፣ ቀጥሎም  በፍሎሬንስ፣ ጣሊያን የተሰራበትና እጅግ አመርቂ ውጤት ያስመጣ ሲሆን፣ ከዚያ በመነሳት ወደ እንግሊዝና ወደ ሌሎች የምዕራብ አገሮች በመራባት ህበረተሰብአዊ ለውጥ ማምጣት ተችሏል። ይህ ዐይነቱ አመለካከት በእንግሊዝ አገር በተነሱ ኤምፕሪሲስቶች፣ ሆበስ፣ ሎክና ኋላ ደግሞ በአዳም ስሚዝ አስተሳሰብ ሲከሽፍ፣ በ18ኛው ክፍለዘመን ግን በቫይማር የጀርመን ከተማ ውስጥ በእነ ሺለር፣ ዊንከልማን፣ ኸርደር፣ ጎተና፣ በኋላ ደግሞ በዊሌየም ሁምቦልድት በመዳበርና በመስፋፋት ጀርመንን ወደ ኋላ ከቀረ የፕረሲያ አገዛዝና የተበታተነ የመሳፍንቶች አገዛዝ ቀስ በቀስ በማላቀቅ አመርቂ ውጤት ሊያመጣ ችሏል። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ጀርመን የገጣሚዎችና የአሳቢዎች አገር ተብላ በመጠራት፣ እንግሊዝንም ሆነ ፈረንሳይን በአጭር ጊዜ ውስጥ ቀድማ ለመሄድ ችላለች።

       በኛ አገርም ሆነ በሌሎች የሶስተኛው ዓለም ተብለው በሚጠሩ አገሮች ያለው ችግር አንድን ሁኔታ በጥቁርና በነጭ በመሳል የተወሳሰበን የህብረተሰብ ችግር ለመረዳት አለመቻል ወይም አለመፈለግ እየመላለሰ ችግር ውስጥ ሲከተን ይታያል። ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት በኋላ ዓለም በሁለት ካምፕ የተከፈለች ነች ተብሎ ነበር  የሚነገረን። በዚህ ላይ በየቦታው ይካሄድ የነበረው ፀረ-ኢምፔሪያሊስት ትግል የግዴታ ግራ ነኝ የሚለውን ሳያወጣና ሳያወርድ ወደ ሶሻሊስት ካምፕ የሚያስገባ ነበር። በተጨማሪም አንድ ወጥ በሆነ መልክ የተስፋፋው በማርክሲዝም ላይ የተመሰረተው የአፃፃፍ ስልትና ሰበካ ለአንድ ህብረተሰብና ለጠቅላላውም ዓለም ጠቃሚ የሆነውን የግሪኩን፣ የሬናሳንስ፣ ቀጥሎም የጀርመኑን ክላሲክ እንዳይካተት አገደ። ወደ ፍልስፍናው ዓለም ስንመጣ፣ በተለይም የመንፈስንና የአስተሳሰብን የበላይነት በሚመለከት የግሪክ ክላሲኮች ብቻ ሳይሆኑ፣ ቻይናዎች፣ ህንዶችና በፈራኦኖች ዘመንም ግብጾች የሚጠቀሙበት ህብረተሰብን መገንቢያ ዘዴ ነበር። ይሁንና ግን በከፍተኛ ደረጃ ነገሩን በመረዳት ተግባራዊ ማድረግ የጀመሩት አውሮፓውያን ናቸው። ዛሬ ግን ብዙ ነገሮችን በማጣመም ዓለም አቀፋዊ ውዝግብ መፍጠሪያ አድርገውታል። ካፒታሊዝም በአሸናፊነት ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ የዓለም ማህበረ-ሰብ ይበልጥ ተፈጥሮን በመበዝበዝና የሰው ልጅ አትክሮ ይበልጥ ማቴሪያሊስታዊ እየሆነ ሊመጣ ቻለ። በተፈጥሮ ውስጥ የሚገኙ ነገሮችን በስነስርዓት እያወጣ በመጠቀም ውብ ውብ ነገሮች እንዳይሰራ ታገደ። የተዛባ ዕድገትና ያልተስተካከለ ኑሮ በየአገሮች ውስጥ መስፈን የካፒታሊዝም አንደኛው ገጽታ ሆኑ።

      ከዚህ ስንነሳ በመሰረቱ በደርግ ዘመን የተፈጠረው ውዝግብ ሰዎቹ ልዩ ፍጡሮችና አውሬዎች በመሆናቸው፣ ወይም ማርክሲዝም በቀጥታ ስላሳሳታቸው ሳይሆን፣ ለብዙ ዘመናት በህብረተሰብአችን ውስጥ የተከማቸው የአስተሳሰብ ጉደለትና በሰፊውና በጥልቀት ለማሰብ የማያስችል የትምህርት አቀሳሰምና ልማዳዊ የአኗኗር ዘዴ ነው። በሌላ አነጋገር እስከ 1974 ዓ.ም ድረስ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ የፊዩዳል ፓትሪያሪካል ስርዓት የሰፈነበትና፣ የአስተሳሰብ ነፃነት ያልዳበረበት ስለነበር ህብረተሰብአዊ ውዝግቦች ሲነሱ በውይይት ከመፍታት ይልቅ በጉልበት መፍታቱ ዋናው መፍትሄ ተደርጎ የሚወሰድ ነበር። በዚህ ዐይነት ሁኔታ ውስጥ በደንብ ያልተጣሩና በደንብ ግንዛቤ ውስጥ ያልገቡ አስተሳሰቦች ጭንቅላት ውስጥ በሚገቡበት ጊዜ ጭንቅላትን ከማሾል ይልቅ በማደንደን የግዴታ ወደ አመጽ ይገፋፋሉ። ሰው መሆንን ያስረሳሉ። የሰው ልጅ ወደ አውሬነት ባህርይ የሚለወጥበት ሁኔታ ግልጽ ይሆናል። ሰው ለሰው መድሃኒቱ መሆኑ ቀርቶ፣ አንዱ ሌላውን የሚፈራበት ሁኔታ በመፈጠር አለመተማመን ጥቅላላውን ህብረተሰብ ይገዛሉ። ለማሰብ፣ ለመፍጠርና በጋራ በመነሳሳት አንድን አገር ገንብቶ ሰላምንና ፍቅር ለማሳደር የማይቻልበት ሁኔታ ይፈጠራል።

      አብዮቱ ከከሸፈና የደርግ አገዛዝ ከወደቀ ወዲህ ደግሞ፣ በአዲሱ ፖለቲከኞች የተያዘው ፈሊጥ ዓለም በተወሰኑ ነገሮች የምትገለጽ ሆነች። ቅራኔዎች የማይታዩባት፣ የሰው ልጅ ሁሉም እጅ ለእጅ ተያይዞ የሚጓዝባት፣ ግሎባላይዜሽንና ሊበራሊዝም በሚባሉ ፅንሰ-ሃሳቦች የምትገለጽ ሆነች። ወያኔ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ ይህ ዐይነቱ አመለካከትና አስተሳሰብ በአገራችን ምድር በመስፋፋቱ ሁሉም ሊበራል ሆነ። ልክ በአብዮቱ ወቅት ሁሉም ማርክሲስት እንደሆነና ጓድ እየተባባለ እንደሚጠራው ዐይነት ሊበራሊዝምና የነፃ ገበያ በማያሻማ መንገድ ተቀባይነትን አገኙ። በዚህ መልክ የፅንሰ-ሃሳብ አመጣጣቸውንና ዕድገቶቻቸውን ሳያወጡና ሳያወርዱ መቀበልና መስበክ፣ በአብዮቱ ዘመን ለምን እንደዚያ ዐነት አስከፊ ሁኔታ ሊደርስ ቻለ ብሎ ሳያወጡ ሳያወርዱና፣ እንዲያው በደፈናው በዚያን ጊዜ ሊበራሊዝምን ብንቀበል ኖሮ እንደዚህ ዐይነቱ መቀመቅ ውስጥ አንገባም ነበር ብሎ ማውራት፣ በራሱ የተወሳሰበውን፣ በግሎባል ካፒታሊዝም የሚደርሰውን መበዝበዝ፣ የሀብት ዘረፋና፣ በየአገሮች ውስጥ ሚዛናዊ የሆነ አገዛዝ እንዳይሰፍን በማድረግና፣ ህብረተሰቦች በደሀና ጥቂት በናጠጡ ሀብታሞች ተከፋፍሎ ርስ በራሳቸው እየተፋጠጡ እንዲኖሩ የሚያደርገውን ሁኔታ ጠለቅ ብለን እንዳንመራመርና እንዳናጠና የሚያደርገን ነው። በመሰረቱ ዛሬ በዓለም አቀፍ ደራጃ የሚካሄደው ዝቅተኛና ሰፋ ያለ ጦርነት ከአሜሪካንና ከእንግሊዝ፣ በተዘዋዋሪ ደግሞ ከተቀረው የምዕራብ አውሮፓ ቁጥጥር ውጭ የሚካሄድ አይደለም። የተወሳሰቡ የጦር መሳሪያዎችም የሚመረቱትና በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚራቡት በአሜሪካን፣ በራሺያ፣ በጀርመንና በፈረንሳይ ነው። ይህም ማለት፣ ከሰላሳ ዐመት ጀምሮ ዓለም ወደ አንድ መንደር እያመራች ነው ተብሎ ቢነገረንም፣ ከምንጊዜውም የበለጠ ዓለም በጭንቀት ውስጥ የምትገኝበት፣ ሰላም የታጣበት፣ ህጻናት የሚሰቃዩበትና፣ ሰው-አልባ በሆነ አውሮፕላን የሚገደሉበት፣ የዓለም ደሀ-ህዝብ በአገሩ ሰርቶ እንዳይኖር ከመሬቱ እየተፈናቀለ የሚሰደድበትን ዓለም ነው የምናየው። በአጭሩ የፊናንስ ካፒታልና የሚሊታሪ-ኢንዱስትሪ ውስብስቦች ሰለጠንኩ የሚለውን የምዕራቡን አገዛዝ በቁጥጥር ስር በማድረግ ዓለም የሚበወዝበት ሁኔታ ተፈጥሯል። በዚህ ዓይነቱ የተወሳሰበና እጅግ ግዙፍ የሆነ የምዕራቡ የፖለቲካ አገዛዝ ፊት እኛ ምስኪኖች እንደ ሰው የማንቆጠርበት ሁኔታ ውስጥ እንገኛለን። ከዚህ ስንነሳ እንዴት አድርገን ነው ይህንን ውስብስብ ሁኔታ በመገንዝብ ኃይላችንን አሰባስበን ለጋራ ዓላማ የምንነሳው? የሚለውን ነው ማውጣት ማውረድ ያለብን።

        ሊበራሊዝም ለኢትዮጵያ የሚያዋጣው አማራጭ የሌለው ዲሞክራሲያዊ አስተዳደር ነው ተብሎ በብዙዎች ተቃዋሚ ድርጅቶች ሲቀርብ መብራራት ያለባቸው አስፈላጊና መሰረታዊ ነገሮች አሉ። በመጀመሪያ ደረጃ ሊበራሊዝም ማለት ይህ ነወና እንደፈለክ ተወዳደር ተብሎ በአዋጅ የሚታወጅ ሳይሆን ወደ ተጨባጭ ሁኔታ ሲተረጎም በራሱ ብዙ ነገሮችን ይዞ ይመጣል። በሁለተኛ ደረጃ፣ በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ባለ አገር ውስጥና፣ ገና ህብረተሰብአዊ ኃይሎች በደንብ በስራ-ክፍፍል ባልዳበሩበት፣ የተወሳሰቡ የኢኮኖሚና የማህበራዊ እንዲሁም የባህልና የኢኮኖሚ ቀውስ አፍጠው አግጠው በሚገኙበት አገር ውስጥ ሊበራሊዝምን እንደ ህብረተሰብአዊ ፕሮጀክት ተግባራዊ ለማድረግ በጣም ያስቸግራል። በሶስተኛ ደረጃ፣ በታሪክ ውስጥ እንደታየው ሊበራሊዝም ሁሉንም ሊጠቅም የሚችል ዲሞክራሲያዊ ፕሮጀክት ሳይሆን የግዴታ የተወሰነውን የህብረተሰብክፍል መጥቀሚያ መሳሪያ ነው። በ17ኛውና በ18ኛው ክፍለ-ዘመን የሊበራሊዝም አስተሳሰብ ሲነሳና ሲስፋፋ በመሰረቱ በአንድ በኩል በመርካንትሊዝም ተግባራዊ ይሆን የነበረውን የኢኮኖሚ ፖሊሲ መቃወም ሲሆን፣ በሌላ ወገን ደግሞ በጊዜው ብቅ ማለት የጀመረውን የከበርቴ መደብ ጥቅም ለማስጠበቅና፣ በዚያውም መጠን የፊዩዳል-አርስቶክራሲውን የኢኮኖሚ መሰረት ለመበጣጠስ ነበር። ስለሆነም በአራተኛ ደረጃ፣ በተለይም የግል ሀብት ህጋዊ እንዲሆን የህግ የበላይነት የሚለው አስተሳሰብ ተቀባይነት እንዲኖረው በማድረግ የካፒታሊስት ስልተምርት በእርግጠኛ መሰረት ላይ እንዲቆም የተደረገበት ሁኔታ ነው። ይሁንና በተለይም እንደኛ ባለህብረተሰብ ውስጥ ገና ህብረተሰብአዊና ምሁራዊ እንቅስቃሴዎች ባላደጉበት አገር ውስጥ  ስለሊበራሊዝም በሚወራበትና በሚሰበክበት ጊዜ ድህነትን ማጥፋት እንደሚቻልና እኩልነት እንደሚያሰፍን ተደርጎ ነው የሚወሰደው። እንደዚህ ዐይነቱ በደንብ ሳይታኘክና ሳይብላላ የተወሰደ ፅንሰ-ሃሳብ በብዙ የሶስተኛው ዓለም አገሮችና በድሮው የኮሙኒስት አገሮች ውስጥ ከፍተኛ ቀውስን አስከትሏል። ስለሆነም ብዙም ሳናወጣ ሳናወርድ የምናስተጋባው ፅንሰ-ሃሳብ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ ያመዝናል። ሌሎች የተሻሉ አማራጭ የመፍትሄ መንገዶች እንዳይስፋፉ ከመጀመሪያውኑ ይታፈናሉ። የአብዛኛው ህዝብ አስተሳሰብ አንድ ወጥ አመለካከት እንዲይዝ በማድረግ ህብረተሰባዊ ችግሮች እንዳይፈቱ ይደረጋሉ። ከዚህ ስንነሳ የሊበራሊዝምን አርማ አንግቦ የሚታገለው የተወሰነው ተቃዋሚ ኃይል ስለሊበራሊዝም ያለውን አስተሳሰብ በሰፊው ቢያብራራልንና የህብረተስብአችንን ችግሮችን እንዴት ደረጃ በደረጃ መቅረፍ እንደሚችል ቢያስረዳን ምናልባት ከውዥንብር ለመዳን እንችል ይሆናል።

        በዚህ መልክ የሚናፈሰውን ፅንሰ-ሃሳብ ስሰማ የብዙዎቻችን ትግል የሚያተኩረው እንዴት አድርገን የህብረተሰብአችንን ችግር ቀርፈን ጠንካራ አገር እንገነባለን በሚለው ዙሪያ የሚሽከረከር ሳይሆን ለስልጣን የሚደረግ ትግል ነው የሚመስለኝ። በመሰረቱ የወያኔን የኢኮኖሚና `የሶሻል ፓለቲካ` እየተነተኑና እየበለቱ ምን ያህል አገራችንን እንደሚጎዳ ማሳየቱ ላይ የሚያተኩር ሳይሆን፣ እንዲያውም አንዳንዶቹ አገዛዙን በሶሾሊስትና በአብዮታዊ ዲሞክራሲ ፖሊሲው ሲወነጅሉት ነው የሚሰማው። ይህ ዐይነቱ ውንጀላ በአንድ በኩል ተጨባጭ ሁኔታዎችን ካለማንበብ የሚመነጭ ሲሆን፣ በሌላ ወገን ደግሞ ህዝቡን፣ በተለይም ወጣቱን የሚያሳስት አካሄድ ነው። ከዚህ ሌላ ከዛሬው አገዛዝ ጋር ያለንን ቅራኔ ግልጽ ሊያደርግ የማይችለው የአንዳንድ ድርጅቶች የፖለቲካ ስሌት ነው። አንዳንድ ግለሰቦችም ሆነ ድርጅቶች ከሌላ ጋር ተዋህደው ወይም ተጣምረው ቢሰሩም እስካሁን ድረስ ብሄራዊ ባህርይ ወይም ሶሻል ኤቶስ(Social Ethos) ያለው እንቅስቃሴ ሲያካሂዱ አይታዩም። በመጀመሪያ የሚሰጡት ቅድሚያ ለመጡበት ብሄረሰብ ነው። በዚህ ደግሞ ችግሩ እንዳማይፈታና፣ ማንኛውም ብሄረሰብ ተጠቃሚ ሊሆን አይችልም። ስለዚህም ተቃዋሚ ነን እስካሉን ድረስ የብሄረሰብ አጀንዳን ይዞ ብሄራዊ አጀንዳ አለን ከሚሉት ጋር ለጊዜው የትግል ግምባር መፍጠር የኋላ ኋላ ስልጣን ሲጨበት ትግሉ ለስልጣን የሚደረግ አጉል ሽኩቻ ነው የሚሆነው እንጂ ህብረተሰብአዊ ፕሮጀክትን ተግባራዊ ሊያደርግ የሚችል አይደለም። ከዚህ ዐይነቱ ውዝግብና የፖለቲካ መሰናክል ለመውጣት የግዴታ ወደ ግምባር ከማምራት በፊት መወያየት እጅግ አስፈላጊ ነው። ይህም ማለት፣ በብሄራዊ ነፃነት ጥያቄ ላይ፣ አጠቃላይ ለሆነ የኢኮኖሚ ዕድገት ጉዳይና በሪጂናል ደረጃ መደረግ ስላለበት የስራ-ክፍፍልና የሀብት ሽግሽግ(Resource Transfer)፣ ሾለ ማህበራዊና ሾለ ባህል ጥያቄ፣ የአማርኛ ቋንቋ በትምህርት ዓለም ውስጥ ስለሚኖረው ሚና፣ በህብረተሰብአዊ ጥያቄና በብሄረሰብ መሀከል ስለሚደረገው ግኑኝነትና፣ ቀደም ብለው ያሉና ባለፉት ሃያ ዐመታት አርቲፊሻል በሆነ መልክ የተከሰቱ ችግሮች፣ ስለክልል ጉዳይና በዚህ መልክ ስለመቀጠሉና አለመቀጠሉ፣ በሌላ ተግባራዊ ሊሆንና ለዕድገትና ለሀብት እንቅስቃሴ አመቺ የሆነ አገሪቱን በሪጂናል ደረጃ ስለማዋቀሩ ጉዳይ፣ ለአፋጣኝ ዕድገት የሚያመች የትምህርት ስርዓት ስለማዋቀሩ ጉዳይ፣ … ወዘተ. የመወያያ አጀንዳዎች ቢሆኑ የሁላችንም አስተሳሰብ ወደ ቁም ነገሮች ላይ ማምራቱ ብቻ ሳይሆን ከስልጣን ሽኩቻም ያድነናል ብዬ አምናለሁ። እንደሚታወቅው አብዛኛውን ጊዜ እንደኛ ባለው አገር በአንገብጋቢና ለህብረተሰቡ አስፈላጊ ናቸው በሚባሉ ነጥቦች ላይ ውይይት ስለማይደረግ ሁልጊዜ ንትርክና ተከታታይነት ያለው ሾል እንዳይሰራ እንቅፋት ይሆናል።

        በመሰረቱ ለስልጣን ካልሆነ በስተቀር እኛን ኢትዮጵያውያን ነን የምንለውንና፣ ከዚያች የተጎሳቆለች አገር የበቀልነውን የሚያጣላን ነገር አልነበረም። የለም እኔም እሱም ስልጣን የምንፈልግ ስለሆነ፣ ያሸነፈ ብቻ ስልጣን ይውሰድ የምንል ከሆነና ለፍጥጫ የምንዘጋጅ ከሆነ የምንመኛትን ኢትየጵያን ሳናይ ነው የምናልፈው። የለም ዋናው ዓላማችን ስልጣን ሳይሆን የሰለጠነችና የተከበረች ኢትዮጵያን መገንባትና ለመጭው ትውልድ ጥለን ማለፍ ነው የምንፈልገው የሚባል ከሆነ ደግሞ እስከዛሬ ድረስ የተጓዝንበትን የትግል ጎዳና ለምን እንደከሸፈና መቀመቅም ውስጥ እንደከተተን መጠየቅ አለብን። ይህንን ስናደርግ ብቻ ነው የተሻለ ህብረተሰብአዊ አስተዋፅዖ ማድረግ የምንችለው። ይህንን በአናሎጊ መረዳት ይቻላል። ለምሳሌ አንድ የምርት ዐይነት እያመረተ የሚሽጥ የኢንዱስትሪ ከበርቴ ከተወሰነ ወቅት በኋላ እንደወትሮው የሚያመርተው በብዛት አይሸጥለት ይሆናል፤ ስለሆነም የገበያው ድርሻና ትርፉም በከፍተኛ ደረጃ ዝቅ እያለ ይመጣ ይሆናል። በዚህን ጊዜ ምንድነው ማድረግ ያለበት? በድሮው የአሰራርና የአመራረት ዘዴ መቀጠል ወይስ ጠቅላላውን አደረጃጀቱን በመመርመርና የገበያውን ሁኔታ በማጥናት የቀድሞውን የገበያውን ድርሻ መመለስና ትርፋማ መሆን ? በቀድሞው የአሰራርና የአደረጃጀት ስልቱ ከቀጠለ ከገበያ ተስፈናጥሮ መውጣቱ ብቻ ሳይሆን በሱ ስር ተቀጥረው የሚሰሩ ሁሉ ከስራ ቦታቸው የመፈናቀል ዕድል ያጋጥማቸዋል። ብዙ ቤተሰብ የገቢው ሁኔታ ይቀንሳል ማለት ነው። ሁለተኛውን መንገድ ከተከተለ ራሱንም ሆነ ቢያንስ የተወሰነውን ሰራተኛውን ከመባረር አዳነ ማለት ነው። የፖለቲካ ድርጅቶችም እንደዚህ ናቸው። በየጊዜው የድርጅታቸውን ስኬታነትና ብቃት መመርመር አለባቸው። አንድን ተጨባጭ ሁኔታ በደንብ ማንበብ መቻላቸውንና አለመቻላቸውን የውስጥ ለውስጥ ውይይትና ክርክር ማድረግ አለባቸው። የህብረተሰብ ሃላፊነትን እንሸከማለን ብለው የተነሱ ስለሆነ በተቻለ መጠን ሆደ ሰፊ በመሆንና ቅራኔዎችን በማርገብ ብዙ ኃይል ሊሰባሰብ የሚችልበትን ሁኔታ መፍጠር መቻል አለባቸው። ለዚህ ደግሞ የሚሰሩበትንና የሚመሩበትን ቲዎሪ ትክክል መሆኑንና አለመሆኑን መጠየቅ አለባቸው። ይህ ብቻ ሳይሆን በአንድ አገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች እንደ አሸናፊና ተሸናፊ ወይም እንደጠላት መተያየት የለባቸውም። አንደኛው ፓርቲ አሸናፊ ሆኖ ስልጣን በሚረከብበት ጊዜ ሌሎችን ማራቅ የለበትም። በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ያለ በቆዳ ስፋት ትልቅ አገርና በህዝብም ቁጡር እያደገ የሚሄድ በተለይም በመጀመሪያው ወቅት በፓርልሜንት ውስጥ ተመርጠው የሚገቡትን ሁሉ ትብብር የሚጠይቅ ነው። በፓርቲዎች መሀከል የሚደረግ አጉል መቃቃርና ሽኩቻ ለውጭ ኃይሎች ጣልቃ-ገብነት ያመቻል።

      እንደሚታወቀው በአንድ ህብረተሰብ ውስጥ የተለያዩ ድርጅቶች በተለያየ ርዕይ ለተለያየ ዓላማ የሚነሱበት ሁኔታ አለ። እነሱ ትክክል ነው ብለው በሚያምኑበት ርዕይ ህብረተሰብአቸውን ሊቀርጹ ይፈልጋሉ። በሌላ ወገን ግን እንደዚህ ዐይነቱ አመለካከት የመቻቻልና የመከረካር፣ እንዲሁም የረዥም ጊዜ የፖለቲካ ትግል ልምድ ካለው የምዕራብ አውሮፓ ውስጥ የተለመደና አስቸጋሪ ባይሆንም፣ እንደኛ አገር ባለው ከፖለቲካ ዕምነት ይልቅ የቡድንና የግለሰቦች አምልኮ በሚያይልበት አገር የተለያዩ ርዕዮተ-ዓለም እንከተላለን የሚሉ ርዕያቸውን ተግባራዊ ለማድረግ የሚታገሉ ሳይሆን በራሳቸው ጥቅም ወይም ኤጎ በመጠመድ ሌላ ርዕይ አለኝ፣ ወይም ሌላ የፖለቲካ መስመር ነው የምከተለው ከሚለው ጋር ግብግብ ይፈጥራሉ። በዚህ መልክ አንድ ህብረተሰብ የተለያዩ ፓርቲዎች ግን ደግሞ ተልዕኮአቸውን በሚገባ ባልተረዱ በመጠመድ ዕውነተኛ ስልጣኔ ተግባራዊ እንዳይሆንና ህብረተሰቡም በዘለዓለም ውዝግብ ውስጥ እንዲኖር ይገደዳል። ይህ ዐይነቱ ውዝግብ በብዙ የሶስተኛው ዓለም አገሮችና የድሮው የኮሙኒስት አገሮች በጉልህ የሚታይና ለማስተዳደር የማያመች ሁኔታ እንዲፈጠር ያደረገ ኋላ-ቀር አመለካከት ነው። ከዚህ ዐይነቱ ውዝግብና ግልጽ ያልሆነ ሁኔታ ለመውጣት የነቁ ኃይሎች በከፍተኛ ደረጃ በሁሉም አቅጣጫ ምሁራዊ እንቅስቃሴ ማድረግ አለባቸው። ትግላቸውን ከርዕዮተ-ዓለም ባሻገር በማድረግ ዕውነተኛና ነፃ ውድድር የሚፈጠርበትን ሁኔታ ማዘጋጀት መቻል አለባቸው። ሳይፈሩ ሳይቸሩ አንገብጋቢ የሆኑ ህብረተሰብአዊ ጥያቄዎችን በማንሳት ለክርክር መጋበዝ አለባቸው። ከረዥሙ የግሪክና የአውሮፓ የስልጣኔ ግንባታ ታሪክ የምንማረው ቁም ነገር አለ። ይኸውም ማንኛውንም ሰው በክርክርና በውይይት(Persussivness) ለማሳመን መሞከር። ማንኛውም ህብረተሰብአዊ ጥያቄ በሃሳብ ዙሪያ እንዲሽከረከር ማድረግ።

     እስከዛሬ ድረስ በአገራችን ያለው ትልቁ ችግር በሃሳብ ዙሪያ ትግል አለማድረግ ነው። በሁለተኛ ደረጃ ጠለቅ ብሎ ለማሰብ አለመጣር። ከላይ እንዳስቀመጥኩት ነገሮችን በጥቁርና በነጭ እየሳሉ በማስቀመጥ ሃሳብ በሰፊው እንዳይብራራና እንዳይሽከረከር ማድረግ። ይህ ሁኔታ ደግሞ በራሱ ቡድናዊ ስሜትን ያጎለምሳል። ያሰራር ግልጽነት እንዳይኖር ያደርጋል። በሶስተኛ ደረጃ፣ መነሳትና ለክርክር መቅረብ ያለባቸውን ነገሮች ትቶ በሌሎች ግን ደግሞ ከረዥም ጊዜ አንፃር ሊፈቱ በሚችሉ ነገሮች ላይ መረባረብ የብዙ ሰዎችን አስተሳሰብ ይበታትናል። ለጊዜው መነሳት ያለበትን ትተን በሌላ ላይ በመረባረብ የአንድን ጨቋኝ አገዛዝ ዕድሜ አብዛኛውን ጊዜ ባለማወቅ የሚራዘምበት ሁኔታ ይፈጠራል ማለት ነው። የዚህ ሁሉ ችግር አሁንም ቢሆን በቲዎሪ አለመመራትና በየጊዜው ራስን አለመጠየቅና ወደ ውስጥ ደግሞ ክርክር አለማድረግ። ሊቀመንበሮች ወይም ራሳቸውን የሾሙ የፓርቲ ሃላፊዎች ስህተት ሲሰሩ ዝም ብሎ መመልከት አደገኛ ሁኔታን እየፈጠረ ነው። በተጨማሪም የፓርቲ መሪዎች ጊዜያቸውን ጠብቀው ሌላው እንዲመራ ዕድል አለመስጠትና አንድ ድርጅት በየጊዜው በአዳዲስ ኃይሎች እንዲመራ ፈቃደኛ አለመሆን ለአሰራር አስቸጋሪና ለፖለቲካ ባህል መዳብር አልመች ያሉ ናቸው። ስለሆነም ማንኛውም ሰው እንደ እግዚአብሄር ሊጠየቅና ወይም በክርክር ሊጋፈጥ እንድማይችል እየታየ ነው። በአንድ ፓርቲ ውስጥ የአሰራር ሂራርኪ ቢኖርም፣ ማንኛውም አባል በድርጅቱ ፊት እኩል መብት ያለው መሆኑን ለብዙዎች ግልጽ አይደለም። ከዚህ ስንነሳ ማንኛውም ለስልጣን እታገለላሁ የሚል የፖለቲካ ሰው የድርጅቱን ፕሮግራም ብቻ ሳይሆን፣ የሚሰራቸው ስራዎች ሁሉ ከአገሪቱ ዕድገትና ጥቅም ጋር መጓዛቸውንና አለመጓዛቸውን መመርመር ያስፈልጋል። የራሱንም ችሎታና ቦታ በየጊዜው መመርመር አለበት።

     ሌላው አገራችንን ከድሮው ባህልና ከዛሬው አገዛዝ ማላቀቅ እንዳንችል ቆልፈው የያዙን ለኛ ብቻ ሳይሆን ለማንኛውም ህብረተሰብ ጠቃሚ የሆኑ መሰረተ-ሃሳቦች አሉ። የሥራ ፍላጎታችን የመነመነ ነው። እንደሚታውቀው ለአንድ አገር ዋናው የዕድገት ቁልፍ የስራ ፍላጎት መኖሩ ብቻ ሳይሆን፣ የአሰራር ዘዴንና ጥበብን ማወቅ ነው። ማንኛውም ስራ ጥበባዊ(aesthetic) ባህርይ እንዲኖረው ያስፈልጋል። የምንሰራቸው ስራዎች ሁሉ የመጨረሻ መጨረሻ ማቴሪያላዊ ብቻ ሳይሆኑ፣ የመንፈስም ደስታም የሚሰጡን መሆን አለባቸው። በሁለተኛ ደረጃ፣ አንድን ነገር በተቀላጠፈ መልክ ለመስራት የአደረጃጀት ችሎታ(Organizational Capacity) እጅግ ወሳኝ ነው። በተቀላጠፈና በደንብ በተዋቀረ የአደረጃጀት ስልት ዘዴ ብቻ ነው ብዙ ጊዜ ሳይባክን ስኬታማ ውጤት የሚገኘው። በሶስተኛ ደረጃ የዲስፕሊን ጉዳይ ነው። ሰዓትን ማክበርና ለተረከቡት ስራ በኃላፊነት መሰራት ለአንድ አገር ዕድገት ወሳኝ ሚናን ይጫወታሉ። በአራተኛ ደረጃ፣ ማህበራዊ ወይም ህብረተሰብአዊ(Social Awareness) ኃላፊነት መሰማት ለዕድገት ብቻ ሳይሆን አንድን ህብረተሰብ ተሳስቦ እንዲኖር ያግዘዋል። ይህ ጉዳይ ከብዙ ሁኔታዎች አንፃር መታየት ያለበት ጉዳይ ሲሆን፣ በሰውና በሰው መሀከልና፣ በሰውና በተፈጥሮ መሀከል ያለውን ግኑኝነት የሚያጠቀላል ጉዳይ ነው።

       ከልዩነቶቻችንና ብዙ ግልጽ ካልሆኑ ነገሮች ባሻገር ሁላችንንም የሚያስተባብረን ሁኔታ አለ። ወደድንም ጠላንም ዛሬ ለድርድር የማይቀርብ  ከፊታችን ተደቅኖ የሚገኝ ነገር አለ። የወያኔ አገዛዝ የስልጣኔን የዕድገት ጠንቅ ነው። የራሱን እጅግ የጠበበ አስተሳሰብ ተግባራዊ ለማድረግ ህዝባችንን በሃይማኖት፣ በጎሳ፣ በጾታና በልዩ ልዩ ነገሮች ማመስ ከጀመረ 20 ዐመታት አስቆጥሯል። ከዚህ ባሻገር የአገራችንን መሬት ለውጭ „ከበርቴዎች“፣ በመሰረቱ ዘራፊዎች እየሸጠ ወይም እያከራየ አዲስ ሁኔታ(Social Realities)እየፈጠረብን ነው። በዚህ ላይ የተወሰነ ቦታ ለአሜሪካን የሰው-አልባ አውሮፕላን ማረፊያ በመስጠትና ከዚያ እየተነሳ ሽብረተኞች የሚላቸውን እንዲደበድብ በማድረግ የፓኪስትን ዐይነት ሁኔታ እየፈጠረብን ነው። በተለይም ከወንድማችን የሶማሌ ህዝብ ጋር ቅራኔ ውስጥ በማስገባት ዘለዓለሙን ፍጥጫ ውስጥ እንድንኖር በማድረግ ሁላችንም የስልጣኔና የሰላም በላቤት እንዳንሆን እያደረገን ነው። ሀብት በመዝረፍና ሌላው ሰርቶ እንዳያድርና እንዳያድግ በማድረግ ህብረተሰብአዊ ድህነት እያስፋፋ ነው። ስለሆነም ህብረተሰብአችን አቅመቢስ ሆኗል። 50 በመቶ የሚሆነው ህዝባችን በአስፈላጊ የምግብ ዐይነቶች ዕጥረት ይሰቃያል። ልዩ ልዩ ቪታሚኖችና ሚኒራሎች ይጎድሉታል። እንደሚታውቀው አስፈላጊውን ለሰውነትና ለጭንቅላት ገንቢ የሆኑ ነገሮችን የማይመገብ ህዝብ አስተሳሰቡ የጠበበ ይሆናል። በተወሳሰበ መልክ በማሰብ ችግሮችን ሊፈታ አይችልም። በአገራችን ብቻ ሳይሆን በብዙ አፍሪካ አገሮችም ተመሳሳይ ችግር አለ። እንደሚባለው ከሆነ ይህ ዐይነት ቪታሚንና ሚኒራሎች የጎደሉት የአመጋገብ ዘዴ ለዕድገት ፀር ሆኗል። አሁን ባለው የዋጋ ግሽበት አብዛኛው ህዝብ  ምግብ አማርጦ ሊበላ ቀርቶ፣ በጣም አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን እየገዛ ሊመገብ የማይችልበት ሁኔታ ተፈጥሯል። ባጭሩ ድህነትና ድብቅ ረሃብ በአገራችን ውስጥ በመስፋፋት የታሪክ ውርደት ውስጥ ወድቀናል። ከዚህ ስንነሳ ይህ አገዛዝ ወንበዴ በመሆኑና በገንዘብ ኃይል ናላው በመዞር አገራችንን በከፍተኛ ደረጃ የሚያምስ በመሆኑ ይቅርታ የሚደረግለት አይደለም። ይህንን እጅግ አደገኛ ስራ የሚሰራው ከምዕራቡ ዓለም፣ በተለይም ከአሜሪካን ጋር እየተባበረ ነው።

       በአገራችን ያለው ሁኔታ እንደዚህ ግልጽ ከሆነ አገራችንን ለማዳን ሁላችንም በአንድነትና ለአንድ ዓላማ መነሳት አለብን ማለት ነው። የማያስፈልጉ ቅራኔዎችንና አለመተማመንን እየፈጠርን በህዝባችን ላይ የሚደረሰውን ግፍ አጋዥ መሆን የለብንም። በአገራችን ውስጥ የሚከሰተው ረሃብ፣ ድህነት፣ በሽታ፣ መሰደድ፣ መታሰርና ሌሎች መዐት በደሎች በአንድ ብሄረሰብ ብቻ ላይ የሚደርሱ አይደሉም። ድህነትና ረሃብ አንዱን ጎሳ ብቻ ነጥሎ በማውጣት ሌላውን የሚያጠቃበት ሁኔታ የለም። ችግሩ በሃይማኖትና በብሄረሰብ ግድግዳ የሚገደብ አይደለም። ችግሩ የሁላችንም ስለሆነ በአንድነት መነሳት አለብን ማለት ነው።

      በመሀከላችን ያለው ትልቁ መሰናክል በያለንበት የጥናት ክበቦች በመመስረት ሶሻል ኔት ወርክ ለማደራጀት አለመቻል ወይም አለመፈለግ ለስራ አላመችም ብሏል። በተጨማሪም በግለሰብ ተነሳሺነትና ፍላጎት መሰራት ያለባቸውን ነገሮች ላይ አለማትኮር ሌላው ችግራችን ነው። በስልጣኔ ታሪክ ውስጥም ሆነ በኋላ በአውሮፓው ምድር የተነሱትን ፈላስፋዎችና የሳይንስ ሰዎችን ህይወት ታሪክ ስንመለከት በራሳቸው ጥረት የሰውን ልጅ ከጨለማ እናወጣለን ብለው ተነሳሱ እንጂ ከኋላቸው ሆኖ እንደዚህ አድርጉ እያለ የገፋፋቸው ኃይል አለነበረም። በመንፈሳቸው ኃይል ብቻ በመነሳትና ከብዙ ነገሮች ራሳቸውን በመቆጠብ ነው የስልጣኔውን ፋና ሊቀዱ የቻሉት። ስለዚህም ሁሉም በችሎታው አስተዋጽዖ ማድረግ መቻል አለበት። በሌላ ወገን ደግሞ ዕውቀቱ የጋን መብራት ሆኖ ብቻውን የሚከንፍ ከሆነ ለህብረተሰብ ግንባታ የሚያደርገው አስተዋፅዖ የለም ማለት ነው። አንዱ ያዳበረው ሃሳብ ወደሌላውም በመሸጋገር መስፋፋትና መሰረት መያዝ አለበት።

        ከዚህ ባሻገር በብዙ አካባቢዎች የዕውቀትም ሆነ የኢንፎርሜሽን ችግር አለ። እንደሚታውቀው አንድ ህብረተሰብ በጠነከረ መሰረት ላይ ለመገንባት ከተፈለገ ዕውቀት መሰረታዊ ነገር ነው። ከተፈጥሮ ሳይንስ ጀምሮ እስከህብረተሰብ ሳይንስ፣ ከከተማ ዕቅድ እሰከ አርክቴክቸር፣ ከአካባቢ ጥናት አንስቶ አካባቢን በልዩ ሁኔታ ማዘጋጀት፣ የህሊና ሳይንስና ሌሎችም አያሌ ለአገር ግንባታ የሚጠቅሙና የሚያስፈልጉ ዕውቀቶች በየአካባቢው በአዋቂዎች እየተጠኑ መቅረብ አለባቸው። ይህንን የተወሳሰበ ዓለምና ዛሬ ዓለምን የሚያሽከረክሯትን ለመቋቋም የምንችለው በሁሉም አቅጣጫ ብቃትነት ሲኖረን ነው። ራሳችንን የምናግዘውና ነፃ የምናወጣው ራሳችን ብቻ ነን። ዓለም ውድድር የሚደረግባት እንደመሆኗ መጠን አንዱ ሌላውን ለመዋጥ ይሯሯጣል። በአገሮች መሀከል መፈቃቀር የለም። መከበባር ሊኖረው የሚችለው ግን አንድ አገርና ህዝብ በዕልህ ተነሳስቶ አገርን ሲገነባና ብሄራዊ ነፃነቱን ማስከበር ሲችል ብቻ ነው። በሌላ ወገን ግን የካፒታሊዝም የበላይነት በሁሉም አቅጣጫ ድርጊታችንና የፍጆታ ልምዳችንንም ሆነ አጠቃቀም ደንጋጊ በመሆኑ ለዕድገታችን በሚያስፈልጉና በማያስፈልጉ መሀከል ያለውን ልዩነት መለየት የተቸገርንበት ሁኔታ ውስጥ ወድቀናል። ሁላችንም በውዥንብር ዓለም ውስጥ እንገኛለን። ዛሬ ግሎባል ካፒታሊዝም እንዴት እንድምንኖር ህይወታችንን ይደነግጋል። ምን እንደምንበላ፣ ምን መስራት እንዳለብን፣ መቼ መተኛትና መነሳት እንዳለብን ህይወታችን የሚደነገገው ካፒታሊዝም ባዋቀረው የአሰራርና የአደረጃጀት ሎጂክ ነው። በሚያስፈልጉን ማቴርያላዊ ነገሮችና ሚዛናዊ ለሆነ የአኗኗር ህይወታቸን እጅግ ጠቃሚ በሆነው የመንፈስ ደስታ መሀከል መለየት የማንችልበት ደረጃ ደርሰናል። የፍጆታ ዕቃዎች መብዛት፣ ለምሳሌ እንደ ሞባይል ዐይነት፣ ኢፓድና ኢፖድ፣ ስማርት ፎንና ታብሌት ፒሲ እንዲሁም እጅግ የሚያማምሩና የሚያሳስቱ ሌሎች ነገሮች ለህብረተሰብአችን ዕድገት በሚያመቸው መልክና መንገድ እንዳናሳብ ተገደናል። የተሸብረቀረው የካፒታሊስት ዓለም በየጊዜው አዳዲስ የፍጆታ ዕቃዎችን በማምረትና በዓለም ገበያ ላይ በመበተን በመጀመሪያ ደረጃ መፍታት ያሉብንን መሰረታዊ ነገሮች፣ እንደምግብ፣ ንጹህ ውሃ ማግኘት፣ ህክምናና መጠለያ ላይ እንዳናተኩርና ደረጃ በደረጃ ቀስ እያልን ህብረተሰብአችንን እንዳንገነባ ሆነናል። ይህ ዐይነቱ ችግር በብዙ የሶስተኛው ዓለም አገሮች ያለና ጥቂት ከካፒታሊስት ዓለም ጋር የተሳሰሩ ግለሰቦችና ቡድኖች የሚሆነውን የማይሆነውን በማምጣትና ገበያው ላይ በማራገፍ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠርን ህዝብ በውዥንብር ዓለም ውስጥ እንዲኖር አድርገውታል። ስለዚህም ለውድ እናት አገራችን እናስባለን፣ እንታገላለንም የምንል ከሆነ ስልጣኔና ዕድገትን በሚመለከት በግልጽ መነጋገር ያለብን ጉዳዮች ብዙ ናቸው። እዚህ ምዕራቡ ዓለም በየጊዜውም አዳዲስ ነገሮች ብቅ ሲሉ ሁኔታውን በመመርመር ጠቃሚነቱንና ጉዳቱን በግልጽ እያወጡ ይወያዩበታል። እኛም ዝም ብለን ተቀባዮች ሳንሆን የግዴታ ክሪቲካል አመለካከት ማዳበር መቻል አለብን። በዚህ መልክ ብቻ ነው ለአገራችን ዕድገት የሚሆን ቁም ነገር ልናበረክት የምንችለው።መልካም የገና በዓልና፣መጪው ዐመት ደግሞ በጋራ የምንታገልበት፣ የድል፣ የሰላም፣ የፍቅርና የመተሳሰብ እንዲሆን እመኛለሁ!  መልካም ንባብ !

                                    fekadubekele@gmx.de

*በወይዘሮ  አስቴር ሰይፈ የተደረሰው „ፈተና“ የሚለው መጽሀፍ እጅግ የሚያሳዝን

ታሪክ በመሆኑ መነበብ ያለበት ነው። በተለይም ዕውቀት የጎደለውና ማመዛዘን

የማይችል የህብረተሰብ ክፍል በአንድ ታዳጊ ህፃን ልጅ ላይ ሳይቀር የሚያደርሰውን

የህሊና አደጋ ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው። እንዴት አድርጎ የሰው ልጅ በራሱ

ልጅ ላይ፣ በተለይም በአንድ ታዳጊ ህፃን ላይ እንደዚህ ዐይነቱን ጭካኔ ያሳያል?

በዚህ መልክ በተለይም በእህቶቻችን ላይ የደረሱትንና የሚደርሱትን ግፎች የሚያሳዩ

መጽሀፎች በአለፉት ዐመታት በተከታታይ ታትመው በመውጣት የአንዳንድ ሰዎችንና

የህብረተሰብ ክፍሎችን ክፉ ስራ እያጋለጡ ነው። ባጭሩ የአገራችን ጉድ ሰፊና ውስ

ብስብ እንደመሆኑ መጠን፣ በተለይም የነቁ ሴት እህቶቻችን መታገል አለባቸው። በየ

ቦታው ሶሻል ኔትዎርክ በመመስረት በዚህ ዐይነቱ አንገብጋቢ ጥያቄ ላይ በግልጽ መወያየት አለባቸው።

ህብረተሰብአዊ ኃላፊነት ያለው አገዛዝና ኢንስቲቱሽኖች በሌሉ

በት አገር ውስጥ ኃላፊነቱ የሚጫነው በሲቪክ ማህበራት ትከሻ ላይ ነው።