[gtranslate]

 ፖለቲካ እንደ ዕምነትና እንደ መርህ ኚመታዚቱ በፊት መቅደም ዚሚገባ቞ው ነገሮቜ!

         -ዚመንፈስ ነፃነትና ተጚባጭ ሁኔታዎቜን በትክክል ዚማንበብ አስፈላጊነት! II

                                                                                             

                                                                        ፈቃዱ በቀለ(ዶ/ር)

                                                                       ህዳር 11፣ 2019

መግቢያ

አብዮቱ ኚፈነዳና ብዙ ትርምስ ኹተፈጠሹ በኋላ ደጋግሞ ዚሚነሳው ጥያቄና ክርክር አገራቜን እንደዚህ ዐይነት ምስቅልቅል ውስጥ ልትገባ ዚቻለቜው ኚታሪካቜንና ኚአስተሳሰባቜን ጋር ሊጣጣም ዚማይቜል ርዕዮተ-ዓለም በማስገባታቜን ነው ዹሚል ነው። በሌላ ወገን ማርክሲዝም ሌኒንዝም  ኚመግባቱ በፊት ኚባህላቜን ጋር „ዚማይጣጣሙ“  አስተሳሰቊቜና ዹአኗኗር ስልቶቜ  በማወቅም ሆነ ባለማወቅ አገራቜን ውስጥ ሰተት ብለው በመግባት ዚህይወታቜን አካል ለመሆን በቅተዋል። እራሳቜን ያልፈጠርና቞ው አያሌ ነገሮቜ በመግባት እንድንጠቀምባ቞ው ተደርጓል። ጥያቄው ዹውጭ ርዕዮተ-ዓለምን መዋሱ ላይ ሳይሆን እንዎት እንጠቀምበታለን ነው። በትክክል ገብቶናል ወይ? በማርክሲዝም ሌኒንዝም ቲዎሪ አማካይነት ዚኢትዮጵያን ህብሚተሰብ አወቃቀር ማጥናትና ማወቅ ይቻላል ወይ? በጊዜው ይታይ ዹነበሹውን ድህነት፣ ዚስራ-አጥነትና ሚሃብ ምክንያቶቜን ለማወቅ ማርክሲዝምንና ሌኒንዝምን እንደመመርመሪያ መሳሪያ ሊያገለግሉን ይቜላሉ ወይ?  ባጭሩ ዚኢትዮጵያን ዚፖለቲካ፣ ዚኢኮኖሚ፣ ዚማህበራዊ፣ ዚባህልና ዚስነ-ልቩና ሁኔታ በቲዎሪው አማካይነት ማወቅ ይቻላል ወይ? በተጚማሪም ዚማርክስና ዹሌኒን ቲዎሪዎቜ አገራቜንን ወደ ዘመናዊነት ለማሾጋገር ያስቜሉናል ወይ? እነዚህንና ሌሎቜ አያሌ ጥያቄዎቜን ያቀሚብን እንደሆን ብቻ ሚዛናዊ ፍርድ ለመሰጠት እንቜል ይሆናል።

ለማንኛውም በአብዮቱ ወቅት ዹተፈጠሹውን አሳዛኝ ሁኔታ አስመልክቶ ዹሚወነጀለው ዚተማሪው እንቅስቃሎና „ኮሙኒዝምን ተግባራዊ አደርጋለሁ“ ብሎ ዚተነሳውን ዹደርግን አገዛዝ ነው። ይሁንና ግን ዛሬ አገራቜንና ህዝባቜን ለገቡበት ፈታኝ ሁኔታ ተጠያቂው ዚማርክሲዝምና ዹሌኒንዝም ቲዎሪ ለመሆኑ በ቎ዎሪም ሆነ በኢምፔሪካል ደሹጃ ዹተሹጋገጠ ነገር ዚለምፀ በጊዜው በአብዮቱ ውስጥ ዚተሳተፉትና አሁንም በህይወት ዹሚገኙ አንዳንድ መሪዎቜ ማርክሲዝምን-ሌኒንዝምን ተጠያቂ ሲያደርጉ አልተሰማም። አብዮቱ ለምን እንደዚህ ዐይነት ምስቅልቅል ሁኔታዎቜን አስኚተለ? ለምንስ ሺህ በሺህ ዚሚቆጠሩ ሰዎቜ እንዲገደሉ ተደሹገ?  ለሚሉት ጥያቄዎቜ በቂ ምክንያት ሲሰጡ አልተሰማም። ይሁንና ዚቀድሞ ዚኢህአፓ አባል ዚነበሚው፣ በኋላ ዚብአዎን አባል አመራር ዹነበሹውና ኚነመለስ ዜናዊ ጋር ስልጣን ላይ ዚወጣው ታምራት ላይኔ „ማርክሲዝም ሌኒንዝም አሳስቶት“  እንደዚያ ዐይነቱን ወንጀል እንደፈጞመ እዚደጋገመ ነግሮናል።

በእርግጥ በአብዮት ስምና በማርክሲዝም ሌኒንዝም ስም እንደዚያ ዐይነት ውርጅብኝና ግድያ ሲፈጞም በጊዜው ይህንን ሁኔታ ዚተመለኚቱ ሰዎቜ፣ ወይም ደግሞ ዚዘመድ አዝማድ ዚተገደለባ቞ውን ሰዎቜ ዋናው ምክንያት ማርክሲዝም ሌኒንዝም አይደለም ብሎ ማሳመን በፍጹም አይቻልም። ማንኛውም ሰው ፍርድ ዹሚሰጠው ድርጊቱን ዹፈጾሙ ሰዎቜን አስተሳሰብ በመመርመር፣ ያደጉበትን ህብሚተሰባዊ ሁኔታ በማጥናት፣ እንደዚህ ዐይነቱ ርዕዮተ-ዓለም ኚመግባቱ በፊት ዚአብዮቱ ተዋንያን ዚተኮተኮቱበትን ርዕዮተ-ዓለም በመመርመር አይደለም። ኹዚህም በላይ ፍርድ በጅምላ ሲሰጥ ማን በመጀመሪያ ደሹጃ ተኩስ እንደኚፈተና፣ ሁኔታው ኚቁጥጥር ውጭ እንዲወጣ ለማድሚግ እንደበቃ በፍጹም ዹሚጠይቅ ዚለም። ኹዚህም ባሻገር በአብዮቱ ውስጥ ዹተደሹገው ትንቅንቅ በውስጥ ኃይሎቜ ብቻ ሳይሆን ዹውጭ ኃይሎቜም እጃ቞ው እንዳለበትና፣ በቀይና በነጭ ሜብር ውስጥ ዹማይናቅ እርኩስ ሚና እንደተጫወቱ ሊያወጣና ሊያወርድ ዹሚሞክር ሰው በፍጹም ዚለም። ኮሙኒዝምን ወይም ደግሞ ዚማርክሲዝምን ሌኒንዝም ርዕዮተ-ዓለም በጭፍን ዹሚጠላው ሰው ተጠያቂ ዚሚያደርገው ይህንኑ ርዕዮተ-ዓለም ነው። ይሁንና ግን ተደጋግሞ ዹሚዘነጋ ጉዳይ አለ። በመጀመሪያ ደሹጃ ዹጊዜ ጉዳይ(Timing) አለ። ይህም ማለት አብዮቱ ሲፈነዳ ጊዜው አመቺ ዹሆነውን ያህል፣ በሌላ ወገን ደግሞ ኢምፔሪያሊዝምና ሌሎቜ አጎራባቜ አገሮቜ እንደዚህ ዐይነቱን መሰሚታዊ ለውጥ አጥብቀው ለመዋጋት ዚሚያስቜላ቞ው ኃይልና፣ ይህንን ፍላጎታ቞ውንም ተግባራዊ ለማድሚግ ዚሚቜል ዚውስጥ ኃይል እንደነበሚ ነው። በሁለተኛ ደሚጃ፣ አብዮቱ ዚፈነዳው በግብታዊ መንግድ ወይም ሳይታሰብ በመሆኑ ዚተሰበጣጠሚውንና „ዚተለያዚ ዓላማ“ ዹነበሹውን ኃይል በአንድ መሰሹተ-ሃሳብ ዙሪያ በማሰባሰብ እንዲታገልና አገር ለመገንባት እንዲነሳ ማድሚግ በፍጹም አይቻልም ነበር። በሶስተኛ ደሚጃ፣ ዚህዝቡ አስተሳሰብና፣ በተለይም ደግሞ ዹተማሹው ዚህብሚተሰብ ክፍል ይህንን ርዕዮተ-ዓለም ዹመቀበልና ዹአገር መገንቢያ መመሪያ ዚማድሚግ አቅም አልነበሚውም። ዚአገራቜን ዚማ቎ሪያል ወይም ደግሞ ዚኢኮኖሚና ዚማህበራዊ ግኑኝነት በጣም ደካማ ስለነበር ዹነቃና ለውጥን ዹሚፈልግ ኃይል ሊፈጥር አልቻልም። ለተወሰነ ጊዜ ካልሆነ በስተቀር በቆራጥነትና በተኚታታይነት በአብዮቱ ጎራ ሊሰለፍ ዚሚቜል ኃይል ማፍራት በፍጹም አይቻልም ነበር። በአራተኛ ደሚጃ፣ ተራማጅ ነኝ በሚለው ሰፈር ዹተፈጠሹው ዚእርስ በእርስ ሹኚቻና ጥላቻ አብዮቱን አደጋ ውስጥ መጣሉ ብቻ ሳይሆን ተተኪ ዹማይገኝላቾውን በጊዜው ተማሩ ዚሚባሉ ምሁሮቜ እንዲያልቁ ተደሚገ። በተጚማሪም በብዙ ሺህ ዹሚቆጠር ህዝብና ወጣት አለቀ። አብዛኛው በማያውቀው መንገድ ዹዚህኛው ወይም ዚዚያኛው ፓርቲ አባል በመሆን ዚእሳት እራት ሊሆን በቃ። በአምስተኛ ደሚጃ፣ ካለምንም ሳይንሳዊ ጥናትና ካለበቂ ኢምፔሪካል መሹጃ „አብዮት ሊሳካ ዚሚቜለው ደም በማፍሰስ ብቻ ነው“  ዹሚለው  አስተሳሰብ በብዛት ስለተስፋፋ፣ በተለይም በቂ ዕውቀትና ግንዛቀ ሳይኖሚው አብዮቱ ውስጥ ዹተቀላቀለውና አልፎ አልፎም ብሶት ዹነበሹው አጋጣሚ አገኘሁ በማለት በወንድሞቹና በእህቶቹ ላይ እንደዚህ ዐይነቱን አሰቃቂ ድርጊት እንዲፈጜም አደሚገው። ባጭሩ አብዮቱ ዹቂም በቀል መወጣጫ ጊዜም ሊሆን በቃ።

ኹዚህ ስንነሳ መጠዹቅ ያለብን ጉዳይ እንዲያው በቁንጜልና ፊት ለፊት ዚሚታዚውን ነገር እንደዋና ምክንያት አድርገን በመውሰድ ሳይሆን ኹዚህ ባሻገር ያሉትን ምክንያቶቜ በመመርመር ነው። በተለይም አሁን በቅርቡ ዚቀድሞ ዚመኢሶን መሪ ዹነበሹውን ዚአቶ አንዳርጋ቞ው አሰግድን ዹቃለ-መጠይቅ ምልልስ ኚተመለኚትኩኝና ካዳመጥኩኝ በኋላ ጠያቂው አቶ ደሹጀ ኃይሌ በደርግ ወታደሮቜ በአሰቃቂ ሁኔታ ዚተገደሉትንና ያቀሚባ቞ውን ዚአብዮቱ ተዋንያንን ፎቶዎቜ ስመለኚት ነገሩ እንደዚህ በቀላሉ ዚሚታይ ጉዳይ አይደለም። በሌላ አነጋገር፣ ጠለቅ ብለን በመሄድ በተለይም በአብዮቱ ውስጥ ዚተሳተፈውንና በእልቂት ውስጥ ዋና አቀነባባሪ ዚሆኑትን ሰዎቜ ስነ-ልቩና መመርመር ያለብን ይመስለኛል። አሁንም በሌላ አነጋገር መጠዹቅና መመርመር ያለብን ጉዳይ አንድን ርዕዮተ-ዓለም በጭፍን ኹመወንጀል ይልቅ ዚራሳቜንን ስነ-ልቩናና እንደዚህ ዐይነቱን ህብሚተሰብአዊ ፕሮጀክት ወይም አብዮት ካለደም መፋሰስና ሳንወነጃጀል ማስተናገድ እንቜላለን ወይ? ብለን ነው መጠዹቅ ያለብን። በእኔ ዕምነት አንቜልም ዹሚል ነው። ለዚህ ዋናው ምክንያት መንፈሳቜን ለዚህ ዹተዘጋጀ አልነበሚምፀ በአንድ አስተሳሰብ ዙሪያ በመሰባሰብ ለአንድ ዓላማ ዚመታገል ሞራላዊ ብቃት አልነበሹንም ዹሚል ነው። ዞሮ ዞሮ ባህርያቜን በጣም አስ቞ጋሪ ነው ማለት ነው። ኹዚህ በመነሳት ፖለቲካን እንደ ዓላማ ወይንም ዚመታገያ መሳሪያ አድርገን ኚመውሰዳቜን በፊት መጓዝ ያለብንን ክንውናዊ ሂደት ዚተሚዳን አልነበርንም። በሌላ አነጋገር ካለመንፈሳዊ አብዮት በፊት ፖለቲካዊና ማህበራዊ ለውጥ ማምጣት በፍጹም አይቻልም። ይህም ማለት ዚግዎታ መንፈስን ኹማንኛውም እቡይ ተግባር ማጜዳት ያስፈልጋል። ዚህብሚተሰብን ጥያቄ በአርቆ-አስተዋይነት መነፅር በበቂው ማጥናትና መመርመር ዚሚያስፈልግ ይመስለኛል።  በተለይም በዛሬው ወቅት በአገራቜን ምድር ዚሚታዚውን አደገኛ ሁኔታ ለመወጣትና ሰላምና መሚጋጋት እንዲሰፍን ዹምንፈልግ ኹሆነ ኚመንፈስ አብዮትና ጠለቅ ካለ ምሁራዊ ዝግጅት ውጭ ሌላ አማራጭ ነገር በፍጹም ሊኖር አይቜልም።

 ዚመንፈስ ነፃነት አስፈላጊነት!

በዚህ መሰሚታዊ ሃሳብ ላይ ሀተታ ኚመስጠ቎ በፊት እንደገና ስለ አብዮቱ አንዳንድ ነገሮቜን ላትት። አንዳንዶቜ ይህ ያለፈበት ነገር ነውፀ ለምንድነው  እዚደጋገምን እዚያው ላይ ዚምንጜፈው? ትሉ ይሆናል። እዚህ ላይ ስለአብዮቱ ግሩምነት ወይም ደግሞ ሰለተሰራው አሰቃቂ ድርጊት ለማተት ሳይሆን፣ በዚያን ጊዜ ዹተፈጾመው አሰቃቂ ድርጊት ወያኔ ስልጣን ኚያዘ በኋላምና ስልጣንን እስኪለቅ ድሚስ በሌላ መልክ መቀጠሉን ለማሳሰብ ነው። በዚህም በዚያም ብለው ስልጣንን ዚሚቀዳጁ ኃይሎቜ ስልጣን ላይ ለመቆዚትና ዚፈለጉትን ነገር ለማድሚግ ሲሉ ሰውን ኹመግደልና ኚማሰቃዚት ሌላ ዚሚታያ቞ው ነገር እንደሌለና፣ በብዙዎቻቜንም ዘንድ ይህን ዐይነቱን አሰቃቂ ድርጊት እንደተራ ወይም እንደኖርማል ነገር አድርጎ ዚመውሰድ ባህል ዚተስፋፋ መሆኑን ለማሳሰብ ነው። በተለይም አንዳንዶቻቜን  ካለምንም ፀፀት ኚድርጊቱ ፈጻሚዎቜ ጋር ስንሳሳቅ፣ ስንበላና ስንጠጣ ስመለኚት በምን ዐይነት ዚሞራል ውድቀት ውስጥ እንደምንገኝ ለማሳዚት ነው። „ለውጥ መጣ፣ በለውጥ ዓለም ውስጥ ነው ዹምንገኝው“  ኚተባለም ወዲህ ዛሬም  በሰላም ኖቭል ተሾላሚው ዘመን ይህ ዐይነቱ አሰቃቂ ድርጊት እንደባህል ሆኖ በመቀጠል ብዙዎቻቜንን ይህን ያህልም ዚሚያሳስበን ጉዳይ አይደለም። በተለይም ሰላም ዹሰፈነ ይመስል ስንትና ስንት ሰው በጜንፈኛ ኃይሎቜ ሲገደል፣ አንዳንዶቜ ደግሞ ካለምንም ወንጀል እስር ቀት ሲወሚወሩ በዚህ ዐይነቱ ቀውጢ ወቅት ለምርጫ እንወዳደር ማለት ወይንም ደግሞ ለጠቅላይ ሚኒስተሩ ዚደስታ ጋጋታ ማንጋጋት ዚቱን ያህል አሚመኔዎቜ እንደሆን ነው ዚሚያሚጋግጠው። ስለሆነም በአብዮቱ ዘመን ዹተፈጾመው አሰቃቂ ድርጊት ባለፉት 27 ዓመታትና ዛሬ ደግሞ በልማትና በብልጜግና ስም አሁንም ህዝባቜን ፍዳውን ያያልፀ አገር ትታመሳለቜፀ ጥቂቶቜ ጊዜ መጣልን ብለው ይፈነጫሉፀ ዚሚይዙት ዚሚጚብጡት ጠፍቷ቞ዋልፀ በስልጣን ተሳክሚዋል።

ኹዚህ ስንነሳ አሁንም እንደገና ወደ አቶ አንዳርጋ቞ው አሰግድ ዹቃለ-ጥያቄ ምልልስ ጋ ስመጣና፣ ጋዜጠኛው በተለይም ዚመኢሶን ታጋይ ዹነበሹውን እጅግ በሚያሳዝን መንገድ ዚተያዘውንና ዐይኑ እዚተጎለጎለ በመውጣት ዹተገደለውን ዚአቶ መስፍን ካሱን ሁኔታ ሲናገር ኢትዮጵያኖቜ እስኚዚህ ድሚስ አሚመኔዎቜ ነን ወይ? ብዬ ስጠይቅ ዹማገኘው መልስ በተለይም ንዑስ ኹበርቮው አሚመኒያዊ ባህርይ እንዳለው ነው ዚምሚዳው። በአብዮቱ ወቅት እንደዚህ ዐይነቱ ድርጊት ዹተደጋገመና በራሳ቞ውም ዚማርክሲስት ድርጅት ነን በሚሉ አንዳንድ ድርጅቶቜም ውስጥ አንዳንድ አባሎቜ ዚፓርቲው መሪዎቜ አካሄድ ያላማራ቞ው ጥያቄ ሲጠይቁና አማራጭ መንገድ ሲያመልክቱ እጅግ አሰቃቂ በሆነ መልክ ሊገደሉ በቅተዋል። ይሁንና ዛሬ በህይወት ዹሚገኙ ዹዚህ ዐይነቱ አሰቃቅ ድርጊት አቀነባባሪዎቜ አንድም ቊታ ላይ ለድርጊታ቞ው በመጞጞት ይቅርታ ሲጠይቁ አልሰማሁም። እንዲያውም አላውቅምፀ በቊታው አልነበርኩም በማለት ነበር እጅግ አሳፋሪ መልስ ዚሚሰጡት። እነዚህ ዚተለያዩ ድርጅት መሪዎቜ ልክ ዚጀግንነት ስራ ዹፈጾሙ ይመስል ጋዜጠኛ ነን በሚሉና ኃላፊነት በጎደላቾው በተደጋጋሚ ቃለ-መጠይቅ ሲጠዚቁ ስሰማ ሁላቜንም ዚቱን ያህል ዚሞራል ውድቀት ውስጥ እንደምንገኝ ነው ዚሚሰማኝ። ስለሆነም ወደፊት ማንም ዚማይገደልበት፣ ካለምንም ወንጀል ዚማይታሰርበት፣ በፖሊስ ግልምጫና ድብደባ ዚማይካሄድባት አገር ለማዚት ኹፈለግን ዚግዎታ ዚድሮ አሰቃቂ ድርጊቶቜን ማንሳት በጣም አሰፈላጊ ይመስለኛል። ይህንን እዚመላለስን ካልጠዚቅንና መልስም ለመስጠት ዚማንቜል ኹሆነ ህዝባቜን ዹዝንተ-ዓለሙን ፍዳውን እያዚ እንዲኖር ነው ዚምናደርገው። ያም ሆነ ይህ አቶ አንዳርጋ቞ው አሰግድ ዹሰጠው ዹቃለ-መጠይቅ ምልልስ በእኔ ዕምነት ሚዛናዊና ዹበሰለ መልስ ነው ብዬ እገምታለሁ። ይህ ዐይነቱ ግምት ዚእኔ ብቻ ሳይሆን ዹጠዹቅኋቾው ሰዎቜ በሙሉ ተመሳሳይ ግምት እንዳላ቞ው ገልጞውልኛል።

ለማንኛውም በፖለቲካ ዓለም ውስጥ ዹተደሹገውን ትግል ለተመለኹተ መንፈስን ኚማጜዳት በፊት ወይንም እራስን እዚደጋገሙ ኹመጠዹቅ በፊት በፖለቲካ ስም ዚሚካሄድ ትግል ዚመጚሚሻ መጚሚሻ አንድን አገር በቀላሉ ልትወጣ ዚማትቜለው ማጥ ውስጥ ነው ዚሚኚታት። ወደድንም ጠላንም  ዹሰውን ልጅ  ዕድል ወሳኞቜ እራሱ አንድ ህዝብ ሳይሆን አንድ ተማርኩ ነኝ ዹሚል ኃይል እንደመሆኑ መጠን ይህ ዐይነቱ ኃይል በቂ ምሁራዊ ዝግጅትና ዚጭንቅላት ዚጜዳት ዘመቻ ኚማካሄዱ በፊት ተግባራዊ አደርጋለሁ ዹሚለው ፖለቲካ ወደ ብልጜግናና ወደ መሚጋጋት ዚሚያመራ ሳይሆን ወደ ትርምስና ወደ ኋላ-ቀርነት ነው። በተለይም ብዙ ነገሮቜ ተጣመው በሚቀርቡበት እንደኛ ባለው አገር ውስጥ ተጹቁነን ነበር ዚሚሉ፣ ዹዚህ ወይም ዚዚያኛው ብሄሚሰብ ተወካይና ነፃ አውጭ ነን በማለት እራሳ቞ውን ዚሟሙ ግለሰቊቜም ሆነ ድርጅቶቜ አጋጣሚውን በማግኘት ዚበላይነትን ለመቀዳጀት እንጂ ወገናቜን ነው ዚሚሉትን ነፃ ለማውጣት አይደለም። በመጀመሪያ ደሹጃ ዹዚህ ወይም ዚዚያ ተወካይ ነኝ ዹሚል ዚብሄሚሰብ ኀሊት ባለፈው 27 ዐመታት እንዳዚነው ዚራሱን ጥቅም ብቻ ነው  ዚሚያስጠብቀው። በተለይም ዚኊሮሞ ክልል ወደ ኋላ ኚቀሩት ክልሎቜ ውስጥ አንዱ አካባቢ ሲሆን ዚኊሮሞ ወጣት ሎቶቜ አበባ ተካይ እንዲሆኑ ነው ዚተደሚጉት። አሁን ደግሞ አዲስ በተቋቋመው ዚኢንዱስትሪ ፓርክ ውስጥ ተቀጥሚው በመስራት በኹፍተኛ ደሹጃ እዚተበዘበዙ ና቞ው። በሁለተኛ ደሚጃ፣ ቂም በቀልን ኚማስቀደም በስተቀር እወክልሃለሁ ዚሚሉትን ብሄሚሰብ  ዚማሰብ ኃይሉን ኹፍ ለማድሚግና ሰው መሆኑን እንዲገነዘብ ዚወሰዱትና ዚሚወስዱት ዚማስተማር እርምጃ ዚለም። ሰሞኑን እንዳዚነው ምንም ዕውቀትና  ስራ ዹሌለው ዚቄሮ ወጣቶቜ ነኝ ዹሚሉ በጅምላ በመነሳት በአንዳንድ ኚተማዎቜ ውስጥ ዚሚኖሩ ንፁህ ዜጋዎቜን ገድለዋል። ብዙ ንብሚትም አውድመዋል። ዚአንድ ነፃ አውጭ ኀሊት ወይም ዚአንድ ክልል አመራር ተቀዳሚ ተግባር ለኗሪው ዜጋ፣ በተለይም ለወጣቱ ዚሙያ ስልጠና መስጠትና ዚስራ-መስክ መክፈት ነው። ይህንን ኚማድሚግ ግን ዹዹክልሉ መሪዎቜና፣ በተለይም ዚቄሮ ወጣቶቜ መሪ ነኝ ዹሚለው ጃዋር ምንም ዚማያውቀውን ወጣት በስሜት በመንዳትና በወገኑ ላይ እንዲነሳ በማድሚግ ኹፍተኛ ዹሆነ ዚታሪክ ወንጀል እዚፈጞሙ ና቞ው። ጩኞታ቞ውና ድርጊታ቞ው በሙሉ ዓላማ ዹሌለው ነው።

ያም ሆነ ይህ በኢትዮጵያ ምድር በነፃ አውጭነት ስም ሲንቀሳቀሱ ዚነበሩ ድርጅቶቜና ትላንትም ሆነ ዛሬ ስልጣንን ዚተቀዳጁ እንደምናዚው አገርን ኚመገንባት ይልቅ ዚኋሊት ጉዞ ዚሚያስኬድ „ባህል“ እዚቆፈሩ በማውጣት ኋላ-ቀርነትና ድህነት ስር እንዲሰዱ በማድሚግ ላይ ና቞ው። ሰሞኑን ዹተኹበሹው „ዚኢሬቻ በዓል“ ዚሚያሚጋግጠው ይህንን ነው። ዚበላይነትን ማሚጋገጫና ማወጃ(Macht Demonstration= Demonstration of Power) ዚሆነና፣ ዚአንዳንድ ኊሮሞ ኀሊቶቜን ባዶ ጭንቅላትነት ያሚጋገጠ ነው። ማሰብ ዚማይቜሉና ይህ ዐይነቱ ዚበላይነትን ማሚጋገጫ አኚባበር አንድ ቊታ ላይ ቡን ብሎ እንደሚበተን ግልጜ ዹሆነላቾው አይመስለኝም።

ዹዚህ ዐይነቱ ዚበላይነትን ማሚጋገጫ አኚባበርም ሆነ በወያኔ ዘመን ዹተፈጾመውን አሰቃቂ ድርጊትና አገርን አፍራሜ „ፖሊሲ“ ስንመለኚት ዚዚድርጅቶቹ መሪዎቜ ጠቅላላውን ዚኢትዮጵያ ሁኔታና ህዝባቜንና አገራቜን ዚተጓዙበትን አስ቞ጋሪ ጉዞ ዚመሚዳት ኃይላቾው እጅግ ደካማ እንደሆነ ነው። ባለፈው ጜሁፌ ላይና ቀደም ብዬ በተለያዩ ጊዜያት ባወጣኋ቞ው ጜሁፎቌ ላይ ለማሳዚት እንደሞኚርኩት በቂ ምሁራዊ ዝግጅት ሳያደርጉና፣ በተለያዩ ምሁራን ዘንድ ክርክር ሳይደሚግ በዝግ ቜሎት ወይም በጊርነት ስልጣን ላይ መውጣት ለራስ ጥቅም ካልሆነ በስተቀር አንድን ህዝብ ነፃ ሊያወጣው በፍጹም አይቜልም። ዹነፃ አውጭ እንቅስቃሎነት በተካሄደባ቞ው በአብዛኛዎቹ ዚአፍሪካ አገሮቜ ውስጥ ዚሚታዚው ይህ ሁኔታ ነው። በምሁራዊ መነፅር እዚተመሚመሚና እዚተገመገመ ዚማይካሄድ ዹጩር ትግል ዚመጚሚሻ መጚሚሻ አገርን ማዳኚምና አንድ ህዝብ በእራሱ ላይ እንዳይተማመን መደሹጉ ብቻ ሳይሆን ዹውጭ ኃይሎቜ መጥተው ዹአገርን እሎትና ዚተለያዩ ባህሎቜን እንዲያፈርሱ ዚሚጋብዝ ሁኔታ ነው ዚሚፈጠሚው። ይህ ዐይነቱ ዚአስተሳሰብ ጥበት ዚብሄሚሰብ ነፃ አውጭ ነን በሚሉ ድርጅቶቜ ውስጥ ብቻ ዚሚታይ ሳይሆን በእራሳ቞ውም „ብሄራዊ ባህርይ አለን“ በሚሉ ፖለቲኚኛ ነን ባዮቜም ውስጥ ያለ ቜግር ነው። ባጭሩ በሁላቜንም ዘንድ አንድን ነገር በጥልቀትና በሰፊው፣ እንዲሁም  ኚተለያዚ አቅጣጫ ዹመመርመር ቜግር አለ። በተለይም በፖለቲካና በኢኮኖሚ ኀሊቱ ተደጋጋሚ ጥፋትም ሆነ ወንጀል፣ እንዲሁም ዹአገርን እሎት ዚሚያጠፋ ፖሊሲ ተግባራዊ ሲሆን ለምንድነው ፖሊሲው ዹማይቀዹሹው? ሌላስ አማራጭ ዹለም ወይ? ብሎ ዹሚጠይቅ ባህል በፍጹም ዚለም።

ዹዚህ ሁሉ ቜግር አሁንም ቢሆን ሰፋ ያለ አስተሳሰብ እንዲኖሚን ጥሚት አለማድሚግ ነው። በተራ ዕውቀት ዚአንድን ህብሚተሰብ ቜግር ለመቅሹፍ ዚሚያስቜል ኃይል አለን ብለን ስለምንገምት ነው።  ካንት ዚሚባለው ፈለሳፋ መገለጜ ማለት ምን ማለት ነው?( What is Enlightenment?) በሚለው ጜሁፉ ውስጥ ዹሰው ልጅ በመሰሚቱ ሰነፍ ነው ይላል። ዝም ብሎ በጭፍን ኹመጓዝ በሰተቀር በጥልቀትና በስፋት ለመመራመር አይፈልግም ይላል። ዚነገሮቜን አመጣጥ ለመሚዳት ጥያቄ ለመጠዹቅ አይሻም። እንዲያው ብቻ ዝም ብሎ በጭፍን መጓዝን ይመርጣል። ካንት በዚህ መልክ ያስቀመጠው አገላለጜ ወይም ጥያቄ ዚአገራቜን ቜግር ብቻ ሳይሆን በብዙ አገሮቜ ውስጥ ያለና፣ በማዕኹለኛው ዘመን ዚአውሮፓን ህዝብ ወደ ድህነት፣ ዚማያቋርጥ ጊርነትና በሜታ ውስጥ ዹኹተተ ነው። ስለዚህም ኚጥንት ጊዜ ጀምሮ እስኚ ማዕኹለኛውና አስራዘጠነኛው ክፍለ-ዘመን ድሚስ ፈላስፋዎቜ ሆን ብለው ቅድሚያ ዚሰጡት በጭንቅላት ላይ ኹፍተኛና ዚማያቋርጥ ስራ መስራት ዚማሰብ ኃይልን ኹፍ ማድሚግ ሲቜልፀ  ኹቂም-በቀል ነፃ ዹሆነ በተለይም ምሁራዊ ኃይልን ማፍራት ይቻላል ዹሚል ግምት አላ቞ው። ስለሆነም በስሜት ኚመነዳት ይልቅ አርቆ-አሳቢነት በመቅደም ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ፣ እንዲሁም ዚማህበራዊ ቜግሮቜ በፍትሃዊነት መነፅር ዚመታዚትና መፍትሄ ዚማግኘትም ዕድል ያጋጥማ቞ዋል። ይህ ኹመሆኑ በፊት በፖለቲካ ስም መነገድ በአንድ አገር ውስጥ ዘለዓለማዊ ትርምስ እንዲኖር ያደርጋል።

በጣም ዹሚገርመው ነገር ይህ ዐይነቱ ጭንቅላትን መነሻ አድርጎ ምርምር ማድሚግ በግሪኩ ስልጣኔና በአውሮፓ ምድር ውስጥ ዹተለመደ ሲሆን ለምን በእኛ አገር ውስጥ ይህ ዐይነት ባህል ሊፈጠር አልቻለም?  ዚመጀመሪያዎቹም ሆነ በኋላ ዚተነሱት ዚግሪክ ፈላስፋዎቜ ለምንስና እንዎትስ በጭንቅላትና በተፈጥሮ ላይ ምርምራ቞ውን እንዲያደርጉ አስገደዳ቞ው? ፍልስፍና ኹተፈጠሹና ኚዳበሚ ኚሶስት ሺህ ዐመት በኋላ ለእኛ ይህ ጉዳይ ለምንስ አልተገለጾልንም? ለምንስ እዚተንደፋደፍን እዚያው በዚያው በተመሳሳይ ነገሮቜ ላይ እንፋለጣለን?  እስኚማውቀው ድሚስ እስኚዛሬ ድሚስ አንድም ሰው ጥያቄ ዹጠዹቀ ዚለም። አንዳንድ ሰዎቜ ነገሩ ታይቷ቞ው ጥያቄ ሲያቀርቡ በነገሩ እንዳይገፋበት ቶሎ ብሎ ይዘጋል። አብዛኛዎቻቜን በቁም ነገር ላይ ለመወያዚት ፍላጎት አናሳይም። ስሜትን ዚሚነካና ዚሚቀሰቅስ ነገርን ብቻ ነው ለመስማት ዚምንፈልገው።  በጣም ዚሚያሳዝን ድርጊትና አስተሳሰብ በሁላቜንም ዘንድ ተስፋፍቷል ማለት ነው። በቁም ነገር ላይ ኚማውራትና ኚመኚራኚር ይልቅ ሆን ብለን ዚያዝነው ነገር ተራ ዹሆኑ ነገሮቜን እያነሳን መጹቃጹቅ ነው። ዚህዝባቜንን ቜግሮቜ ዹሚቀርፉ መሰሚታዊ ጉዳዮቜና ዕውቀት ላይ ኚመኚራኚርና ኚማጥናት ይልቅ ወደ ኋላ ተመልሰን ታሪካቜን እንደዚህ ነበር ብለን ነው ለመዝናናት ዚምንሞክሚው። ሌላው ደግሞ ዚኢትዮጵያን ታሪክ ወደ ወራሪነትና ወደ መቶ ዘመን ብቻ ዹለወጠው ታሪካቜሁ እንደዚህ አይደለምፀ ዚሚያስተሳስሚንም ታሪክ ዹለም በማለት ዹአገርንና ዚህብሚተሰብን ጥያቄዎቜ እርግፍ አድርገን እንድንተው በማድሚግ በማያስፈልጉ ነገሮቜ ላይ እንድንጚቃጚቅ ያስገድደናል።

ለማንኛውም አመንም አላመንም ዚግሪክ ፈላስፋዎቜ በአብዛኛው ጎኑ ፍልስፍናን ዚተማሩትና ዚኮሚጁት ኚጥቁር አፍርካ፣ በተለይም ኚግብጜ ነው። ፕላቶንም ሆነ ፕይታጎራስ እንዲሁም ሶሎን ግብጜ አገር ለትምህርት እንደቆዩና ኚቀሳውስቱ ጋር ዹጠበቀ ግኑኝነት እንደነበራ቞ው ዚታወቀ ጉዳይ ነው። ይህ ጉዳይ ዚተሚት ተሚት ሳይሆን ዹተሹጋገጠና በመጜሀፍ ተመዝግቩ ያለ ነገር ነው። ዚግሪክ ፈላስፋዎቜ ያደሚጉት ነገር በጥቂት ምሁራን ዘንድ ይሜኚሚኚር ዹነበሹውን ዕውቀት ወይም ፍልስፍና ወደ ውጭ በማውጣት ዚማስተማሪያና ዚመኚራኚሪያ መሳሪያ ነው ያደሚጉት። በዚህ መልክ ቀሰ በቀስም አዳዲስ ደቀ-መዝሙሮቜን በማፍራት በጊዜው ዹነበሹውን ዚዘልማድ አኗኗር መጋፈጥ ቻሉ። አስተሳሰብን በማሟል ለሚነሱ ቜግሮቜ መልስ ለመመለስ ሙኚራ ማድሚግ ጀመሩ። ቀስ በቀስም ዚሳይንስን መሰሚት ጣሉ። ባጭሩ በዚያን ጊዜም ሆነ በኋላ እንደዚህ ዐይነት ጭንቅላትን ዚሚያስጚንቅ ስራ ባይሰራ ኖሮ ዹሰው ልጅ ዛሬ ዚደሚሰበት ደሹጃ ላይ በፍጹም ሊደርስ አይቜልም  ነበር።

ይህ ዐይነቱ ጭንቅላትን ዚማስጚነቅና ዚማስገደድ ሁኔታ በካቶሊክ ኃይማኖት ትታመስ ወደ ነበሚቜው አውሮፓ በመሜጋገር ለእነ ዳን቎፣ ኩዛኑስና ለሌሎቜ አያሌ ተመራማሪዎቜና ፈላስፋዎቜ መመራመሪያ ዘዮ በመሆን ወደ ተግባርነት ሊለወጥ ቻለ። እነ ኮፐርኒኚስ፣ ጋሊሊዮ፣ ኬፕለር፣ በሰዕልና በአርክቮክቾር ደግሞ፣ ሊዎናድርዶ ዳቪንቺ፣ ሚካኀል አንጀሎ፣ ራፋኀልና ብዙ ዚማቲማቲክስና ዚሳይንስ ሰዎቜ ብቅ ማለት ቻሉ። ይህ ዐይነቱ ዕውቀት ወደ እንግሊዝ አገር በመሜጋገር እነ ኒውተን ዚመሳሰሉ ሰዎቜን አፈራ። በፈሚንሳይ ደግሞ እነ ሬኔ  ዎካና ቮል቎ር ዚመሳሰሉ ፈላስፋዎቜንና ሳይንቲስቶቜ ብቅ ማለት ጀመሩ።  ወደ ጀርመን አገር ስንመጣ ደግሞ ኚኬፕለርና ኚኩዛኑስ ባሻገር፣ እነ ላይብኒዝ፣ ካንትና  ሄገል፣ እንዲሁም ጎተና ሺለር፣ ሜንደልሰንና ሌሲንግ  ወዘተ. በመነሳት ዋናው ትግላ቞ውን በጭንቅላትና በምርምር ላይ አደሚጉት። ዚመደብ ትግል ሳይሆን ዚጭንቅላት ስራና ምርምር ዋናው ዚነፃነት መሳሪያ መሆኑን አሚጋገጡ።  በዕውቀት አማካይነትም ዚአንድን መደብ ዚፖለቲካና ዚኢኮኖሚ እንዲሁም ዚርዕዮተ-ዓለም ዚበላይነት እንደሚያሞንፉ አሚጋገጡ። ዕውቀትና ኹዚህ ዹሚፈልቀው ኀስ቎ቲክስ ለአንድ ህብሚተሰብ ዕድገትና ስልጣኔ መመሪያ መሆኑን አመለኚቱ። በሌላ አነጋገር በተሳሳተ መልክ ዹሚቀርበውንና ዹተወሰነውን ወይም ጠቅላላውን ማህበሚሰብ ጭንቅላቱን ለማሳሳት(Manipulate) ዚሚራባ ትምህርትን መዋጋት ዚሚቻለው ዚመደብ ትግል እያሉ በመጮህ ሳይሆን ዚተሳሳተ ዕውቀት ፍልስፍናዊና ሳይንሳዊ መሰሚት ዹሌለው መሆኑን ማሚጋገጥ ሲቻል እንደሆነ ብቻ አወጁ። በተለይም ላይብኒዝ ለእንግሊዞቹ  ዚኢምፔሪሲስት ዕውቀት፣ ለእነ ጆን ሎክ ዹሰጠው አጥጋቢ ትንተና ዹሰው ልጅ ጭንቅላት እንደ ባዶ(Tabula Rasa) ወሚቀት ሆኖ እንዳልተፈጠሚ ዚሚያሚጋግጥ ሲሆን፣ ማንኛውም ዕውቀት ሊፈልቅ ዚሚቜለው በጭንቅላት አማካይነትና ተፈጥሮንና ህብሚተሰብአዊ ግኑኝነትን በትክክል ማንበብ ሲቻል ብቻ  ነው። በዚህ መልክ ዹሚደሹግ ትግል ዕውነተኛ ነፃነትን እንደሚያቀዳጅና በአንድ ህብሚተሰብ ውስጥም ስምምነትንና ሰላምን ማምጣት እንደሚቻል አሚጋገጠ።  ይሁንና ዚላይብኒዝና በኋላም ዚእነሺለርና ዊሊሄልም ሁምቊልድት አንድን መንግስት ጥበባዊ አድርጎ ማደራጀትና(The Aesthetic state) ለአንድ መደብ ብቻ እንዳያደላ ማድሚግ በዘመነ ካፒታሊዝምና በግሎባላይዜሜን ዘመን ሊታሰብ ዚሚቜል ነገር አይደለም። ዚካፒታሊዝም አይሎ መውጣት፣ ውስብስብ መሆንና ዚበላይነቱን ይዞ እንዲቆይ ለማድሚግ በአፈ-ቀላጀዎቹ በዹጊዜው ዚሚወጣው መንፈስን ዚሚሰልብ ወይም ሰፊው ህዝብ በፍጆታ አጠቃቀም ላይ ብቻ እንዲያተኩር ዚሚያደርግ ማስታወቂያና ቲዎሪ ዚሚመስል ቅስቀሳ መንግስትን ወገነ-አልባ ሊያደርገው በፍጹም አልቻለም። ዚካፒታሊዝም ዚማኒፑሌሜን ኃይል ዚተወሳሰበና ጠንካራ ኹመሆኑ ዚተነሳ ወደድንም ጠላንም መንግስት በካፒታል ቁጥጥር ስር እንዲወድቅ አድርጎታል ማለት ይቻላል። ስለዚህም በካፒታሊስት አገሮቜ ውስጥ ያለው መንግስት ህዝባዊ ሳይሆን ዚካፒታሊስት መንግስት(The Capitalist State) እዚተባለ ነው ዚሚጠራው። ይህ ጉዳይ በቲዎሪና በኢምፔሪካል ደሹጃ ዹተሹጋገጠ በመሆኑ ሊያኚራክሚን ዚሚገባ ጉዳይ አይደለም። ስለሆነም ዚእነ ላይብኒዙ ጥበባዊ መንግስት ተምኔታዊ ነው ማለት ይቻላል።

ለማንኛውም ዚአንድን ህብሚተሰብ ዕድል ኚራስ ፍላጎት አንፃር በመመልኚት ዹሚደሹግ ትግል ወይም ፖለቲካዊ አካሄድ አንድ ህዝብ ነፃ እንዳይወጣ መንገዱን እንደመዝጋት ይቆጠራል። በትንሜ ዕውቀት መኩራትና መዝናናት ዚመጚሚሻ መጚሚሻ አንድ አገርና ህዝብ እንዲፈራርሱና አቅጣጫም እንዲያጡ እንደማድሚግ ይቆጠራል። መንፈስን ሳያድሱ ወይም ኹማንኛውም ዕቡይ ፀባይ ነፃ ሳይሆኑ ዹሚደሹግ ፖለቲካዊ አካሄድ ዚሳይንስንና ዹቮክኖሎጂ ዕድገትን ይገታል። አንድ ህዝብ ፈጣሪ እንዳይሆንና ዚእራሱን ዕድል በእራሱ በመወሰን ጠንካራና ዹተኹበሹ ማህበሚሰብ እንዳይመሰርት ያደርጋል። በተለይም በዛሬው ወቅት ዚተለያዩ ኃይሎቜ ዝም ብለው በሚፈነጩበትና በብዙ ሚሊዮን ዚሚቆጠሩ ሰዎቜን በሚያሳስቱበት ወቅት ሀቀኛውን ኚሀሰተኛው፣ አልሚውን ኚአጥፊው ለመለዚት በጣም አስ቞ጋሪ ይሆናል። አንድን ድርጅትም ሆነ ግለሰብ፣ ኚዚትኛውም ብሄሚሰብ ይምጣ መመርመርና፣ ዹሚናገሹው ነገር ትክክልና ትክክል አለመሆኑን መሚዳት ዚሚቻለው በትክክለኛ ዚዕውቀት መነፅር  መመርመር ዚተቻለ እንደሆን ብቻ ነው። ማንኛውም ህብሚተሰብን ዚሚመለኚት ነገር ሁሉ በሳይንሱ መመርመርና ማሚጋገጥ ዚሚያስፈልግ ይመስለኛል። ይህንን ትቶ በጭፍን እንጓዝ ማለት አገርን እንደማጥፋት ይቆጠራል።

ተጚባጭ ሁኔታዎቜን በትክክል ዚማንበብ አስፈላጊነት!

በአውሮፓ ዚህብሚተሰብ ታሪክ ውስጥ ዚአንድን ህብሚተሰብ ዕድገትና ሁኔታ መመርመሪያ ዘዎዎቜ ፍልስፋናና ዚማርክሱ ዚማ቎ሪያሊስት መንገዶቜ ና቞ው።  ዚመጀመሪያው በአንድ ህብሚተሰብ ውስጥ ዹሚገኝ ፖለቲካዊም ሆነ ዚኢኮኖሚና ዚማህበራዊ ቜግር ዹሰው ልጅ ጭንቅላት በትክክለኛ ዕውቀት ለመታነፅ ባለመቻሉ ዹሚል ሲሆን፣ ዚማርክሱ አካሄድ ደግሞ በአንድ ህብሚተሰብ ውስጥ ዹሰፈነ ዚምርት ግኑኝነት ሁኔታና(Social Relationship) አብዛኛውንና ስትራ቎ጂክ ዹሆኑ ሀብቶቜን ዚሚቆጣጠር  ዚህብሚተሰብ ክፍል በፖለቲካው ላይ ተፅዕኖ ማሳደርና ዚአንድን ህዝብ አኗኗር ሁኔታ መደንገግ ይቜላል ይላል። በሌላ ወገን ግን በፍልስፍና ዓለም ውስጥ፣ ወይንም አንድን ሁኔታ በማንበብ ሚገድ ሁለት ዐይነት አመለካኚቶቜ አሉ። አንደኛው አንድን ነገር ሁለንታዊ በሆነ ዘዮ ማንበብ ሲሆን፣ በተለያዩ ነገሮ መሀኹል መተሳሰርና ተፅዕና መደራሚግ አለ ይላል። ስለዚህም አንድ ነገር ኚታቜ  በመነሳት ኹፍ እያለና እዚተወሳሰበ ዚሚያድግ ሲሆን፣ በተለይም ህይወት ያለውና አርጋኒክ ዹሆኑ ነገሮቜ ለማደግ ውስጣዊ ኃይል አላ቞ው። ስለሆነም በዚህ ፍልስፍና መሰሚት ቋሚ ነገር ወይም እዚያው ባለበት ሚግቶ ዹሚቀር ነገር ዚለም። ሁለተኛው፣ ኢምፔሪካል ሳይንስ በመባል ዚሚታወቅ ሲሆን፣ ዚጥናቱ መነሻም ነገሮቜን በተናጠል ወስዶ መመርመርና አንድ ውጀት ላይ መድሚስ ነው። ይህ ሳይንስ ፖዝቲቭ ሳይንስ ተብሎ በመጠራት ሲታወቅ ወደ ኋላ በመሄድ ዚነገሮቜን አመጣጥ እንድንመሚመር አያስቜለንም። „በተጚባጭ“ ነገሮቜ ላይ ወይም ፋክትስ ተብለው በሚጠሩ ነገሮቜ ላይ ዚሚመሚኮዝ ሲሆን በነገሮቜ መሀኹል መተሳሰርና ተፅዕኖ መደራሚግ ዚለም። ስለዚህም ነገሮቜ ውስጣዊ ዹሆነ ዹማደግ ኃይል ዚላ቞ውም። ህብሚተሰብም እንደዚሁ ዚሚለወጥና ዚሚሻሻል ሳይሆን በተወሰኑ ስዎቜ ቁጥጥር ስር በመውደቅ እዚያው በዚያው ዚሚሜኚሚኚር ነው። ይህ ዐይነቱ „ሳይንስ“ በዓለም አቀፍ ደሹጃ ተቀባይነትን ያገኘና በተለይም እንደኛ ያሉ አገሮቜን ዚሚያተሚማምስና ለጊርነት ዚሚጋብዘን ነው። በአጠቃላይ በዓለም ላይ ያሉ ዚታወቁ ዓለም አቀፋዊ ተቋማት በሙሉ ይህንን ሳይንስ መመሪያ በማድሚግ ነው ዓለምን ዚሚያተሚማምሱት።

ዚመጀመሪያውን ዚፍልስፍና አመለካኚት ኹተቀበልን አንድ ህዝብ በመንፈስ ተሀድሶ አማካይነት ነው ነፃነቱን መቀዳጀት ዚሚቜለው። በአንድ ህብሚተሰብ ውስጥ በግልጜ ዚሚታዩ ማህበራዊ ቜግሮቜ ዚፍትህ ጥያቄዎቜ ና቞ው። ይህም ዚሚሆንበት ምክንያት ራሱ ዚገዢው መደብ በራሱ ዓለም ውስጥ ስለሚኖር ዚህዝብን ቜግሮቜ ዚማዚት ኃይሉ ዹደኹመ ነው። ቜግሩን መፍታት ዚሚቻለው በጊርነት ሳይሆን ሁሉ-ገብ ዹሆነ ንቃተ-ህሊና እንቅስቃሎ ማካሄድ ሲቻል ብቻ ነው ይላል። ወደ ማርክሱ ዚማ቎ሪያሊስት ቲዎሪ ስንመጣ ደግሞ በመደብ ትግል አማካይነት ነው በተለይም ዚሰራተኛውን መደብ ኚተተበተበበት ዹጭቆና ሰንሰለት ነፃ ማውጣት ዚሚቻለው። ይሁንና ግን ማርክስ ዚምርት ኃይሎቜ ኹማደጋቾው ወይም ኚመዳበራ቞ውና በተለይም ዹወዝ አደሩ መደብ ንቃተ-ህሊናው ኹፍ ኚማለቱ በፊት አብዮት መካሄድ አለበት ብሎ አልሰበኚም። ማርክስ ዚሳይንስንና ዹቮክኖሎጂን ዕድገት በማንሳት በዚህና በተስፋፋ ዚኢንዱስትሪ አብዮት አማካይነት ዚወዝአደሩ መደብ በመተሳሰር እንደ ኃይል ይወጣል ይላል። በዚህም አማካይነት ንቃት-ህሊናውን በማዳበር ማንነቱን ያውቃል። ባጭሩ በአንድ አገር ውስጥ አብዮት ለማካሄድ ዚግዎታ ዚማ቎ሪያልና ዚመንፍስ ሁኔታዎቜ እንዲሁም ድርጅታዊ ዝግጅት እንደሚያስፈልግ በደንብ ያስቀምጣል። ሌኒንዝም ይህንን ዚማርክስን አስተሳሰብ ይደግፋል። ለምሳሌ ስዊዘርላንድ ወደ 17 ዓመታት ይህል በኖሚበት ጊዜያት ዚህብሚተሰቡን አደሚጃጀትና ጠቅላላውን ዚመንገድና ዚቀት አሰራሮቜ ይመለኚታል። ህዝቡም ተመቻቜቶ ዹሚኖር መሆኑን ሲመለኚት „እዚህ አገር ስለአብዮት ማውራት እንደ ዕብድነት ይቆጠራል“ ብሎ ይናገር ነበር። በተጚማሪም ኹሙኒክ ሆኖ ዚቅስቀሳ ጋዜጣዎቜን እያሳተመ ወደ ራሺያ ለመላክ ሙኒክ ይመላለስ ስለነበር ቡና ወይም ቢራ ቀቶቜ ይገባ ነበር። ይህንን በጥብቅ ዚተኚታተለው ሌኒን „ቢራቀት ውስጥ ዚመደብ ልዩነት ዚማይታይበት“ ነው ብሎ ተናግሯል። ይህ ዚሚያሳዚው ምንድነው? ማርክስም ሆነ ሌኒን በጭፍኑ ዚግዎታ አብዮት መካሄድ አለበት ብለው አልሰበኩም ወይም አላስተማሩም። ይህንን ዚማነሳው አለመግባባትን ለማስወገድና ተጚባጭ ሁኔታዎቜን ወይም አንድ ህዝብ ዚሚገኝበትን ዚማ቎ሪያልና ዚስነ-ልቊና፣ እንዲሁም ዚባህል ሁኔታ በቅጡ ማጥናትና ማንበብ ኚብዙ ስህተቶቜ እንድንቆጠብ ስለሚያደርገን ነው።

ያም ሆነ ይህ በአውሮፓ ዚህብሚተሰብ ታሪክ ውስጥ ምርምር ኚህብሚተሰብአዊ ድርጊትና፣ ዹሰው ልጅ ኚተፈጥሮ ጋር ያለው ግኑኝነትና እርስ በእርሱ በኢኮኖሚም ሆነ በሌላ ነገር ኚሚያደርጋ቞ው ግኑኝነቶቜ ውጭ በመሆን አይደሚግም። ታሪክን ታሪክ ዚሚያሰኘው አንድ ህዝብ እራሱን ለማሜነፍ ሲል በተፈጥሮ ላይ ዚሚያደርገው ቁጥጥርና፣ በተፈጥሮ ውስጥ ዹሚገኙ ነገሮቜን (Organic and non-organic) በመለወጥ መጠቀሚያ ሲያደርጋ቞ው ብቻ ነው። በመቀጠልም፣ ታሪክን ታሪክ ዚሚያሰኘው አንድ ማህበሚሰብ ኹተማን ሲገነባ፣ ዚባህል ወይም ዚሃይማኖት ማዕኚሎቜን ሲያቋቅም፣ ንግድና ዕደ-ጥበብን በማስፋፋት እንደ ማህበሚሰብ ሲተሳሰርና ወደ ሲቪል ህብሚተሰብ ሲለወጥ እንደዚህ ዐይነቱ አገር ታሪክ አለው ይባላል። በሄገልም ሆነ በካንት መሰሚት ኹዚህ ውጭ ዚሚታዩ ታሪኮቜ እንደ ሚቶሎጂ ዚሚቆጠሩ ና቞ው። በእነሱ ዕምነት ታሪክን መስራት ዚሚቻለው ካለህበት ሁኔታ በመነሳት እንጂ ወደ ኋላ በመጓዝና እንደዚህ ነበርን በማለት አይደለም። ባጭሩ ታሪክ ዚአንድን ህብሚተሰብ ቜግር መፍቻና ዚሳይንስና ዹቮክኖሎጂ ማፍለቂያ መሳሪያ ሊሆን በፍጹም አይቜልም። በሌላ ወገን ግን ዚሳይንስና ዹቮክኖሎጂ ዕድገቶቜ በህብሚተሰብ ታሪክ ውስጥ ዚሚገለጹና ዚሚካሄዱ ወይም ዹተወሰኑ ቅድመ-ሁኔታዎቜ ሲሟሉ ዚሚፈጠሩ ና቞ው።  ኹዚህ ባሻገር በአውሮፓ ዚህብሚተሰብና ዚባህል ታሪክ ውስጥ ዹሰው ልጅ ወደ ፊት መመልኚትና በግልጜ ዚሚታዩ ቜግሮቜን ለመፍታት ዚሚጣደፍና አትኩሮውም ቜግርን በማስወገድ ላይ ዚሚያተኩር ሲሆን፣ አንድ ማህበሚሰብ ታሪክን ለመስራት እንደሚቜል ያሚጋግጣሉ። አዲስ ታሪክ መስራት ዚሚቻለው ለመንፈስ ተሃድሶ ዚሚያመቹ ዚቀድሞ ባህሎቜን ወይም ዕውቀቶቜን በማስፋፋትና ኚአዲሱ ሁኔታ ጋር እንዲዛመዱ በማድሚግ እንጂ፣ እንደ ኢሬቻንና አባገዳ ዚመሳሰሉትን ለፈጠራና ለዕድገት ዚማያመቹ፣ ዹሰው ልጅ በዝቅተኛ ደሹጃ ላይ በሚገኝበት ወቅት ያደርጋ቞ው ዚነበሩ ነገሮቜን እንደባህል በመቁጠርና፣ ህዝብን በተለይም ወጣቱን በማደንቆር አይደለም ዕውነተኛ ነፃነትና ዕድገት ዚሚገኘው። በሌላ አነጋገር፣ በአንድ ዚታሪክ ወቅት ካለማወቅ ዚተነሳ ዹተደሹጉ ድርጊቶቜን በማንሳትና በማውራት ወይም ለሳይንስና ለቮክኖሎጂ ዕድገት ዚማያመቹ ነገሮቜን እንደባህል አድርጎ በመቁጠርና በማክበር አይደለም ስልጣኔ ሊመጣ ዚሚቜለው።  በዚህም መልክ አንድ ማህበሚሰብ መፍጠርና ዕውነተኛ ነፃነቱን ሊቀዳጅ በፍጹም አይቜልም። አንድ ባህል ዚማሰብ ኃይልን ኹፍ ዚማድሚግ ብቃትነት እስኚሌለው ድሚስ በሳይንስና በቮክኖሎጂ ዚሚገለጜ ዕድገትን ይገታል። በሌላ ወገን ደግሞ ዹሰው ልጅ ማ቎ሪያላዊ ብቻ ሳይሆን መንፈሳዊ እንደመሆኑም መጠን እራሱን ኚአንድ ዐይነት ዕምነት ጋር ቢያገናኝ ክፋት አይኖሚውም። እንዲያውም ዚማ቎ርያል ዕድገትና አንዳቜ ዐይነት ዕምነት ሲጣመሩ ማንኛውም ሰው ሞራሉ ይጠነክራል። ይሁንና ግን እንደዚህ ዐይነት ዕምነት ዚዚግለሰቊቜ ምርጫ መሆን ያለበት እንጂ ኹላይ በአንድ አካል ዚሚጫን መሆን ዚለበትም። ለማንኛውም ዚአውሮፓው ምሁራዊ እንቅስቃሎ ቜግሮቜን በመፍታት ላይ ያተኮሚ ሲሆን፣ ወደ ፊት መመልኚትን እንጂ ወደ ኋላ በመመለስ እንደዚህ እንባል ነበር፣ እንጚቆን ነበር፣ እንቋሞሜ ነበር፣ ባህላቜንን ወይም ዕምነታቜንን እንዳናኚብር ግፊት ይደሚግብን ነበር
ወዘተ. እዚተባለ ኚህብሚተሰብ ዕድገትና ኹንቃተ-ህሊና ውጭ ነገሮቜ እዚታዩ ጊዜ ማሳለፍ ዹተለመደ ነገር አይደለም።

ወደ ኢትዮጵያቜን ስንመጣ  ዹምናዹውና ዹምንሰማው ነገር በሙሉ ስልት ዹሌለውና በአንድ ወቅት ዹነበሹን ዚማህበሚሰብ ንቃተ-ህሊናና ዚማ቎ሪያል ዚዕድገት ደሹጃ ያላገናዘበ ብቻ ሳይሆን ዚራስንም ታሪክ በደንብ ያልመሚመሚ ነው። በስሜት ላይና በወሬ ወሬ ላይ ዹተመሰሹተ እንጂ አንዳቜም ዐይነት ፍልስፍናዊም ሆነ ሳይንሳዊ፣ እንዲሁም ዚቲዎሪ መሰሚት ዹሌለው ነው። በኢምፔሪካል ደሹጃም ዹተሹጋገጠ አይድለም።  በሌላ አነጋገር፣ አንድ ድርጅትም ሆነ ምሁር ነኝ ባይ ወይም ዚፖለቲካ አክቲቪስት ነኝ ባይ ዚአንድን ህብሚተሰብ ታሪክ በአንዳቜ ዚፍልስፍና መነፅርና ሳይንስ ሳያነብና በሳይንስ ዚሚሚጋገጥ ሀተታ እስካልሰጠ ድሚስ እንደዚህ ዐይነቱ ድርጅትም ሆነ ግለሰብ ተልዕኮው ጥፋትና በተጚባጭ ሲታይ ዕድገት እንዳይመጣ ዚሚታገል ነው። አንድ ህዝብ ዚሳይንስና ዹቮክኖሎጂ ባለቀት በመሆን ቜግሮቜን እንዳይቀርፍ እንቅፋት ለመፍጠር ዚሚሯሯርጥ ነው። ዚአንድ ህዝብም ሆነ፣ ዹዚህም ሆነ ዚዚያኛው ብሄሚሰብ አባል ዹሆነ ለመኖር ዚግዎታ መብላትና መጠጣት እንዲሁም መጠለያ ማግኘት አለባ቞ው። ለዚህ ደግሞ  ለመስራት ዚሚቜልና ለአቅመ-አዳም ዹደሹሰ ሰው መስራት አለበት። ራሱን በመቻል ዚህብሚተሰብ አካል መሆኑን ማሚጋገጥ መቻል አለበት። በዚህ መልክ ብቻ ነው በአንደ በአካባቢም ሆነ በአንድ አገር ውስጥ ብሄራዊ ሀብት ሊፈጠር ዚሚቜለው። ኹዚህ ውጭ ብሄሚሰብን ወይም ጭቆናን አስታኮ ዹሚደሹግ ቅስቀሳ በተጚባጭ ሲታይ አንድ ማህበሚሰብ ዹዝንተ-ዓለሙን በድህነት ዓለም ውስጥ ዘፍቆ እንዲኖር ዚሚያደርግ አካሄድ ነው። ይሁንና ግን በዚህ ዐይነቱ መሰሚታዊ በሆነው ዹአገር ግንባታ ክንዋኔ ውስጥ ኚመሳተፍና ራስን ኚመቻል ይልቅ አንዳንድ ዚኊሮሞ አክቲቪስቶቜ ነን ዹሚሉ ምንም ሳይሰሩ ወዲህና ወዲያ በመንቀሳቀስ ወይም በቪላ ቬት ውስጥ በመቀመጥ በፌስ ቡክ አማካይነት፣ ወይም ደግሞ መንግስት በፈቀደላቾው  ዚ቎ሌቪዥን ጣቢያ ላይ በመውጣት በማስሚጃ ያልተሚጋገጠ ወሬ በማራገብና ዚጥላቻ ወሬ በማውራት ህዝባቜን ሰላም እንዳይኖሚው ለማድሚግ በቅተዋል። በአንዳንድ ኚተማዎቜ ውስጥ ኹሌላ አካባቢ ዚመጣ ሰውና ለብዙ ዐመታት እዚያው ዹሚኖር በነፃ እንዳይንቀሳቀስ እዚተደሚገ ነው። በዚህም አማካይነት በብዙ ዚኊሮሚያ ኚተማዎቜ ዚንግድ እንቅስቃሎና ዚምርት ክንውን እዚተዳኚሙ በመምጣት ላይ ና቞ው። ለመሆኑ መንግስትና ዹክልሉ አስተዳዳሪ ይህንን ሁኔታ ነው ወይ ዚሚፈልጉት? በግልጜ ቢነግሩን ለመዘጋጀትና ዚቁርጣቜንን ለማወቅ ይሚዳናል።

እኔ እስኚማውቀው ድሚስ ዚኢትዮጵያ ታሪክ እንደ ህብሚተሰብና እንደ ባህላዊ(Social and Cultural History) ታሪክ በደንብ አልተተሚጎመምፀ አልተጻፈምም። ዚኢትዮጵያ ታሪክ አጻጻፍ በንጉሶቜ ላይ ዹተመሰሹተ እንጂ ዚህዝቡን ዹቀን ተቀን ኑሮ፣ ኚተፈጥሮ ጋር ዹነበሹውን ግኑኝነትና፣ እንዲሁም እርስ በእርሱ በሚያገናኘው እንደ ንግድና እንደ ስራ-ክፍፍል ዐይነት ላይ ያተኮሚ ዚታሪክ አጻጻፍ አይደለም ዚተለመደው። ይህ ብቻ ሳይሆን፣ ህዝቡ እራሱ በግብታዊነት ወይም ተገልጟለት ዚፈጠራ቞ው እንደ እርሻ ባህል፣ ምግብ አሰራር ዐይነት፣ እንደ ጠላና ጠጅ፣ እንዲሁም ካቲካላ አጠማመቅ፣ ዚልብስ አሰራርና ዚተለያዩ ዹዕደ-ጥበብ ስራዎቜ እንደ ታሪክ ቅርጜና ባህላዊ ክንውን ተደርገው ባለመወሰዳ቞ው ሁላቜንም ስንሚባሚብ ዹነበሹው ዚኢትዮጵያ ማህበሚሰብ ዹጹቋኝ ስርዓት እንደነበሚና፣ ስርዓቱም በጹቋኝና በተጹቋኝ ብቻ እንደሚገለጜ ተደርጎ ዚሚወሰድ እንጂ በፊዩዳሊቱ ኢትዮጵያም እዚያው በዚያው ባህላዊ ክንውኖቜና እስኚተወሰነ ደሹጃም ድሚስ ዕድገት እንደነበር በፍጹም ለጥናትም ሆነ ለክርክር አይቀርብም። በተለይም በሙዚቃ ላይ ዹተደሹገው ለውጥ፣ ዹፊደል አቀራሚጜ ዕድገት፣ ግዕዝና አማርኛ እንደመነጋገሪያና ሃሳብን መግለጫ ቋንቋ በመሆን ለስነ-ጜሁፍ ዕድገት ዚነበራ቞ውንና ያላ቞ውን ኹፍተኛ ሚናና አስተዋፅዖ በደንብ ዹተነተነ ዚለም። በዚህ ሚገድ ዛሬ ዘመቻ ዚሚካሄድበት ዚኊርቶዶክስ ሃይማኖትና ቀተክርስቲያን ለህብሚተሰቡ መተሳሰርና ለዕድገትም ዚነበራ቞ውን አስተዋፅዖ ተብራርቶ አይቀመጥም። በፊዩዳሊቱ ኢትዮጵያ ዕውቀት ዚሚባለው ነገር ዹሚፈልቀው ኚቀተክርስቲያን በኩል ነው። አብዛኛዎቜ ነገሮቜ ዚፈለቁት በዚህ ዐይነቱ ተቋም አማካይነት ነው። ኹዚህ ስንነሳ ዚባህልን ዕድገትና አንዳንድ ተቋማት ለዕድገት ያላ቞ውን አስተዋፅዖ ሳይመሚምሩ ቀተክርስቲያንን ማቃጠልና ዚሃማኖት አባቶቜን መግደል ትልቅ ዚታሪክ ወንጀልና በይቅርታ ዚማይታለፍ ጉዳይ ነው። ዚኊርቶዶክስ ሃይማኖትን ለማዳኚምና እንዲያም ሲል ለማጥፋት በውጭ ኃይሎቜ በሚደገፉ ዚእስላም አክራሪዎቜና አግሬሲብ በሆነና በሹቀቀ መልክ ዹዘመኑ ዚክርስትና ሃማኖት አራማጆቜ ዚሚያደርጉት ዘመቻ አለመሚጋጋትን መፍጠሩ ብቻ ሳይሆን ዚእርስ በእርስ ጊርነትም እንዲመጣ ዚሚጋብዝ ነው። እነዚህ ኃይሎቜ እንደዚህ ዐይነቱን ጭንቅላትን ዚሚያደነዝዝ ሰበካና ቅስቀሳ ኚማድሚግ ይልቅ በፈጠራ ስራ ላይ ቢያተኩሩና ዚህበሚተሰብአቜንም ዚተወሳሰቡ ቜግሮቜ ዚሚቀሚፉበትን ዘዎዎቜ ቢያሳዩን ዚታሪክ ተልዕኮአ቞ውን ተወጡ ማለት ነው።

ለማንኛውም ካርል ማርክስ አንድ ቊታ ላይ እንዳለው በአውሮፓው ማህበሚሰብ ውስጥ ለካፒታሊዝም ዕድገት መሰሚቱ ዚተጣለው በፊዩዳሉ ስርዓት ውስጥ ነው። ቀተ-ክርስቲያናት ዚተቋቋሙት፣ ዚገበያ አዳራሟቜ ዚተገነቡት፣ ዹዕደ-ጥበብና ንግድ ዚተስፋፉት፣ እንዲሁም ዚመጀመሪያው ዚሳይንስና ዚፍልስፍና ምርምሮቜ ዚተፈጠሩትና ዚተስፋፉትም በፊዩዳሉ ስርዓት ውስጥ ነው። እነዚህ እያበቡና እዚተስፋፉ ሲሄዱ ኹአሹጀው ስርዓት ጋር አብሚው ለመኖር ያልቻሉበት ሁኔታ ተፈጠሚ። ሄገልስም ሆነ ማርክስ ዲያሌክቲክ በሚለው ሀተታ቞ው ዚአንድን አዲስ ሁኔታ መፈጠርና ወደሌላና ወደ ተወሳሰበ ነገር መቀዹር ዚህብሚተሰብ ዕድገት ህግ መሆኑን ያስተምራሉ። አንድ ዘር ኚተዘራ በኋላ ወደ ስር፣ ወደ ግንድና ቅጠላ ቅጥል፣ እንዲሁም ፍሬውን ዚሚይዙት ቅርንጫፎቜ እንደሚለወጥ ሁሉ አንድም ህብሚተሰብ በዚህ ዐይነቱ ዲያሌክቲካዊ ሂደት( Thesis, Anti-thesis and syntehsis) ኹዝቅተኛ ደሹጃ ወደ ተሻሻለና ወደ ተወሳሰበ ዚመለወጡ ጉዳይ ተፈጥሮአዊ  ህግ ነው።  ወደ ኢትዮጵያም ስንመጣ ህብሚተሰቡን ሊያሰታስስሩ ዚሚቜሉ ነገሮቜና አገሩን አገሬ ብሎ እንዲጠራ ያሰኙት ነገሮቜ በሙሉ በአብዛኛው መልኩ በፊዩዳሉ ስርዓት ውስጥ ዹፈለቁና ዚዳበሩ ና቞ው። በኢትዮጵያ ማህበሚሰብ ውስጥ ለምን ዹቮክኖሎጂ ምጥቀት ሊታይ አልቻለም? ለምንስ ሳይንስና ሊዳብር አልቻለም? ለምንስ ዚስራ-ክፍፍል በመዳበርና ንግድ በመስፋፋት ኚተማዎቜና መንደሮቜ ሊገነቡ አልቻሉም? ለሚሉት ጥያቄዎቜ ለጊዜው በቂ መልስ መስጠት አይቻልም። ይሁንና ግን በዚህ ላይ ጥናት ማጥናቱና መመራመሩ አንድን አገር እንደ ማህበሚሰብ ለመገንባት እንደ አስፈላጊ ነገር ሆኖ መታዚት ያለበት ጉዳይ ይመስለኛል።

ለማንኛውም ዚፊዩዳሉ ስርዓት በሰሜኑ ዚኢትዮጵያ ክፍል ዚተስፋፋ እንደነበሚና፣ በተለይም ገበሬው ወደ ስምንት መቶ ዐመታት ያህል በዚህ ስርዓት ውስጥ በመበዝበዝ አሪስቶክራሲውንና ዚፊዩዳሉን መደብ፣ እንዲሁም ቀተክርስቲያንን ሲመግብ ዹነበሹ ዚህብሚተሰብ ኃይል እንደነበር ይታወቃል። ይህም ማለት ወደ ደቡቡ ዚኢትዮጵያ ክፍል ስንመጣ እስኚ አስራ ዘጠነኛው ክፍለ-ዘመን ድሚስ ዚፊዩዳሉ ስርዓት በፍጹም አይታወቅም ወይም ደግሞ በዝቅተኛ ደሹጃ ያለ ስርዓት ነበር ብሎ አፍን ሞልቶ መናገር ይቻላል። በሌላ አነጋገር በደቡብ ዹሚገኘውን ዚኢትዮጵያ ህዝብ ይበዘብዙ ዚነበሩ በዚያን ጊዜ በዚአካባቢው ዚነበሩ ዚገዢ መደቊቜ እንጂ በሰሜኑ ክፍል ዹሚገኘው ፊዩዳላዊ አገዛዝ አልነበሚም። ይህ ጉዳይ በተለይም አምስቱ ነገስታት በሚባሉት እንደ ኹፋና ሃዲያ በመሳሰሉት ግዛት ውስጥ ዹነበሹና ገና እንደ ፊዩዳሉ ስርዓት በደንብ ጎልቶ ባልወጣበት አካባቢ ዚሚታወቅ ነበር። ይሁንና ግን በደቡብ ዚሚገኙት ነገስታት ለክርስቲያኑ ነገስታት ግብር ይኹፍሉ እንደነበር ይታወቃል።

ይህ ማለት ምን ማለት ነው? እራሱ አማራ ዚሚባለው ዚህብሚተሰብ ክፍል በእራሱ በአማራ ዚገዢ መደብ ዹሚበዘበዝ እንጂ ጠቅላላው አማራ በደቡቡ ህዝብ ላይ በመዝመት ዚሚበዘብዘው አልነበሚም። በሌላ ወገን ግን በ19ኛው ክፍለ-ዘመን ዚፊዩዳሉ ስርዓት ወደ ደቡቡ ክፍል ሲስፋፋ አዲስ ዐይነት ዚህብሚተሰብ ግኑኝነት(Social and Political Relationship) እንደተፈጠሚ ዚማይታበል ሀቅ ነው። ይህ ዐይነቱ መስፋፋት በራሱ እንደ አዲስ ዐይነት ዚማህበሚሰብ ለውጥም መታዚት ያለበት ጉዳይ ነው። እስኚዚያን ጊዜ ድሚስ በአደንና በኚብት አርቢነት ዚሚተዳደሩ ጎሳዎቜን ተቀማጭ እንዲሆኑ በማድሚግ ዚእርሻ ባህል ሊስፋፋ ቜሏል። በዚያው በነበርንበት እንቅር ካልተባለ በስተቀር ዚፊዩዳሉ ስርዓትና ዚክርስትና ሃይማኖት መስፋፋት በዚያ ለሚገኘው ማህበሚሰብ አዲስ ዕምርታ ሊሰጠው ቜሏል ማለት ይቻላል። ይሁንና ይህ ዐይነቱ መስፋፋት በኹፍተኛ ዕውቀት ያልተደገፈ ስለነበር ዕድገቱ ወደ ተሻለ ደሹጃ ለመሾጋገር አልቻለም። ይህ ዐይነቱ ድክመት ዹጠቅላላው ዚአገሪቱ ድክመት ጉዳይ ስለሆነ ሁኔታውን ኚአጠቃላዩ ዚኢትዮጵያ ዚፖለቲካና ዚኢኮኖሚ ሁኔታ ጋር ማገናኘት ዚሚያስፈልግ ይመስለኛል። ይህን ሳያደርጉ በጹቋኝና በተጹቋኝ ብሄሚሰቊቜ መሀኹል ዚነበሚና፣ ስርዓቱም በነፍጠኞቜ ይመራ ነበር እያሉ በጭፍኑ ዚተሳሳተና በማስሚጃ ያልተደገፈ አስተሳሰብን ማስፋፋትና ቅስቀሳ ማድሚግ በቀላሉ ልንወጣ ዚማንቜለው ማጥ ውስጥ ነው ዚሚኚተንፀ ኚቶናልም ማለት ይቻላል።

ይህንን ጉዳይ ኚአውሮፓው፣ በተለይም ኹጀርመኑ ዚባህል ለውጥና ዕድገት ጋር ብናወዳድሚው በፕሚሺያ አካባቢ ስልጣንን ያዚዙት ነገስታትና ዚገዢ መደቊቜ አካባቢያ቞ውን ለማሰልጠን ሲሉ ዚተማሩ ሰዎቜን ወይም ደግሞ በሃይማኖት ሰበብ ዚተባሚሩ፣ በተለይም ሁጎኖቶቜ በመባል ዚሚታወቁትን ኚሆላንድና ኚፈሚንሳይ በመጋበዝ ወይም መጠጊያ በመስጠት ህዝባ቞ውን እንዲያሰለጥኑና ግዛታ቞ውም እንዲያድጉ ያደርጉ ነበር። በዚህ መልክ ነው በብዙ አውሮፓ አገሮቜ ውስጥ ዕድገት ዚሚባለው ነገር ሊታይ ዚቻለውና ዚካፒታሊዝም ዕድገት ሊፋጠን ዚቻለው።  ወደ ኢትዮጵያቜን ስንመጣም ግን በነፍጠኛ ስም ዚሚሰደቡትና ይገደሉ ዚነበሩት ዚቀተ-ክህነት ትምህርት ዚነበራ቞ውና መጻፍና ማንበብም ዚሚቜሉ ነበሩ። በጊዜው ኚእነዚህ ዚተሻለ ዹተማሹ ሰው ስላልነበር  እነዚህን ዚመሳሰሉትን ዚቀተ-ክህነት ትምህርት ዚነበራ቞ውን ለአስተዳደር ስራ በአዳዲሶቹ ግዛት ማሰማራት ታሪካዊ ግዎታ ነበር። ይሁንና ግን ይህንን ጠምዝዞ  አቅኚዎቜን እንደወራሪዎቜ አድርጎ መቁጠርና እያሳደዱ መግደል ዚህብሚተሰብን ዕድገት ካለማወቅ ዹሚመነጭ አደገኛ አስተሳሰብ ነው።

ወደ ሌላ ጉዳይ ስንመጣ አንድ ማዕኹላዊ መንግስት ሲቋቋምና ካፒታሊዝም ወደ አገራቜን ሲገባ ይህ ሁኔታ አዲስ ዚፖለቲካና ዚኢኮኖሚ ግኑኝነት እንደፈጠሚ ዚማይታበል ጉዳይ ነው። በአፄ ምኒልክ ዘመንም ሆነ ዹኋላ ኋላ አማራውን ብቻ ዹሚወክልና ዹሚጠቅም ዚገዢ መደብ አዲስ አበባ ውስጥ በፍጹም አልተቀመጠም። በተለይም ይህ ጉዳይ በአፄ ኃይለስላሎ ዘመን ግልጜ ሆኖ ዚወጣና፣ ዕድገት አለ ዚሚባል ኹሆነ በዕድገት ስም ዹሚደሹገው እንቅስቃሎ በአብዛኛው መልኩ ወደ ደቡቡ ኢትዮጵያ ክፍል ያደላ ነበር። በዚህ መልክ ኚሩቅ ሆነው ዚሚያሳርሱ ባላባቶቜ(Absentee Landlords) በመፈጠር ዚብዝበዛው መጠንና ግኑኝነቱ  ለዚት ባለ መልክ ዚሚካሄድ ነበር። ስለሆነም በካፒታሊዝም መስፋፋት አዲስ ዚፖለቲካና ዚህብሚተሰብ ግኑኝነት ሊፈጠር ቻለ እንጂ ብሄሚሰብን ተገን ያደሚገና፣ አንድን ብሄሚሰብ ብቻ በመጥቀምና ሌላውን በመጉዳት ወይም በመበዝበዝ ዚሚገለጜ ስርዓት በኢትዮጵያ ምድር አልሰፈነም። ዚካፒታሊዝም መስፋፋት በህብሚተሰቡ ውስጥ ያለውን ግኑኝነት በአዲስ መልክ እንዲዋቀር በማድሚግ ዚተለያዩ ዚህብሚተሰብ ክፍሎቜና በተለያዚ ሙያ ለመሰልጠን ዚቻሉ ብቅ ብቅ ማለት እንደቻሉ ዚኢትዮጵያን ዚህብሚተሰብ ዕድገት ታሪክ ለመሚመሚ በደንብ ሊሚዳው ይቜላል። ይህንን ሁኔታ በተሻለ መልክ ዚሚለውጥና ሪፑብሊካናዊ አገዛዝ ሊቋቋም አለመቻሉ በጊዜው ዹነበሹውን ዚአስተሳሰብና ዚህብሚተሰብ ዕድገት ሁኔታ ዚሚያሳይ ነው። በሌላ አነጋገር፣ ማዕኹላዊ መንግስቱ ኹዚህ ዐይነቱ መጠነኛ ዹሆነ ዚጥገና ለውጥ አልፎ ለመሄድና ሁለ-ገብና መሰሚታዊ ዹሆነ ዕድገት ዚማምጣት ኃይልም ሆነ ንቃተ-ህሊና አልነበሚውም። ኹዚህም በላይ ደግሞ ዚሪፑብሊክን አርማ ይዞ ዚሚታገል ዚተገለጞለት ምሁራዊ ኃይልና ህዝባዊ እንቅስቃሎ ባለመኖራ቞ው ዚፊዩዳሉና ዚተዘበራሚቀው ዚካፒታሊስት ዚአመራሚት ስልት እዚያው በዚያው ዚህብሚተሰባቜንን ዕድገትና ዹመኖር ሁኔታ ዹሚደነግጉ ለመሆን በቁ። ዚአውሮፓን ዚባህልና ዚህብሚተሰብ ታሪክ ዚተመለኚትን እንደሆነ ለውጥ ዚሚባለው በሳይንስና በቮክኖሎጂ መልክ ዚሚገለጜ ሊመጣ ዚቻለው ኚስልጣን ውጭ በነበሩ ምሁሮቜ አማካይነት ነው። በጊዜው እያደገ በመጣው ዕውቀትና አዲስና ዚተገለጞለት ህብሚተሰብአዊ ኃይል በመገፋት ነው መንግስታት ወደ ውስጥ ያተኮሚና ሁለ-ገብ ዹሆነ ዚኢኮኖሚና ዚባህል ፖሊሲ መኹተል ዚቻሉት። ምሁራዊ ኃይል በሌለበት፣ ዚሳይንስና ዹቮክኖሎጂ ፈጠራ በማይታወቅበት፣ በፍልስፍና ላይ ርብርቊሜ በማይደሚግበት አገር ውስጥ ውስጣዊ-ኃይል ያለውና ዕድገትን ወይም ለውጥን ዹሚፈልግ ዚህብሚተሰብ-ኃይል ለማፍለቅ በፍጹም አይቻልም።

ለማንኛውም ዚተማሪው እንቅስቃሎና፣ ዹዚህ ወይም ዚዚያኛው ብሄሚሰብ ነፃ አውጭ ነን ዹሚሉ አፈንጋጭና ጜንፈኛ ኃይሎቜ በሚተሚጉሙት መልክ ሳይሆን ዚኢትዮጵያ ዚህብሚተሰብ ታሪክ መተርጎም ያለበት በሌላ መልክ ነው። ይህ ዐይነቱ ዚተሳሳተና በምድር ላይ ዚሚታዚውን ሁኔታ በደንብ ያላገናዘበ አተሹጓጎም በተለይም በአማራው ማህበሚሰብ ላይ ጥርጣሬ በማሳደርና ነፍጠኛ ዹሚል ስድብ በማንጋጋት በህብሚተሰቡ ዘንድ መቃቃር እንዲፈጠር ተደርጓል። ጠቅላላው ህዝብ እርስ በእርሱ እዚተጠራጠሚ እንዲኖር ዹማይሆን ቃላቶቜ በማስፋፋት ኹቁም ነገር እንድንዘናጋ ተደርገናል። በአንድ አገር ውስጥ ዹሚነዙ ፅንሰ-ሃሳቊቜ በደንብ ካልተጠኑና ኚሁኔታው ጋር እስካለተገናዘቡ ድሚስ እንደ እነዚህ ዐይነት ፅንሰ-ሃሳቊቜ እንደ ተፈጥሮአዊ ባህርይ ተደርገው ሊወሰዱ ይቜላሉ። በሌላ አነጋገር፣ አማራ ነፍጠኛና ጉሚኛ፣ እንዲሁም ሌላውን ዚሚንቅና፣ ይህም ተፈጥሮአዊ ባህርይው  እንደሆነ ተደርጎ ይወራል። ሌላው ይህንን ሲሰማ ትክክል ነው ብሎ በማመን ማስተጋባት ይጀምራል። በውሜት ዚተካኑት ሻቢያና ወያኔ አሁን ደግሞ ኩነግና ሌሎቜ ዚኊሮሞ ጜንፈኞቜ እንደዚህ እያሉ በማውራት ነው ህብሚተሰቡ በአንድነት በመነሳት አገሩን እንዳይገነባ ዚሚጥሩት። ስራ቞ው በሙሉ እጅግ ወደ ኋላ ዹቀሹና አሚመኒያዊ ተግባር ነው። እንደዚህ ዐይነቱ ሁኔታ በፊዩዳሊቱ ኢትዮጵያ ዚሚታወቅ ጉዳይ አልነበሚም። ካለ ደግሞ ኹንቃተ-ህሊናና ኚዕውቀት ማነስ ዹሚመነጭ እንጂ ሆን ብሎ ዹሚደሹግ ወይም ዚሚወራና ሌሎቜን ዝቅ አድርጎ ለመመልኚት ተብሎ አልነበሚም።

ለማንኛውም በፊዩዳሉ መደብና በተቀሹው ማህበሚሰብ ዹነበሹው ግኑኝነትና ስርዓቱ በአጠቃላይ ሲታይ እንደጚለማ ስርዓትና ምንም ዐይነት ዚሞራል ሚዛን ወይም መመሪያ እንደሌለው ተደርጎ መቅሚብ ያለበት ነገር አይደለም።  አንዳንዶቜ ሌላውን ዹጠቀሙ ይመስል ሁኔታውን በደንብ ሳያጠኑ ዝምብለው ዚፊዩዳሉ ስርዓት ጹለማና በዝባዥ ብቻ ነበር ብለው ዚሚያወሩ  በጊዜው  ዹነበሹውን  ዹንቃተ-ህሊና ሁኔታና ዚተገለጞለት ምሁራዊ ኃይል አለመኖርን ያላገናዘበ አባባል ይመስለኛል። በአጠቃላይ ሲታይ በአንዳንድ ኚተሞቜ ዚፊዩዳሉ መደብ አንዳንድ በዓሎቜን ምክንያት በማድሚግ በሬ ለክርስቲያኑም ሆነ ለእስላሙ በማሚድና በመጋበዝ ዚህብሚተሰቡ አካል እንደሆነ ያሳይ እንደነበር ዹተሹጋገጠ ጉዳይ ነው። በተለይም ሰርግና ሌሎቜ ባህላዊ በዓሎቜ በሚኚበሩበት ጊዜ ዚፊዩዳሉ መደብ በአካባቢው ዹሚገኙ ኗሪዎቜን በመጋበዝ በደህና ጊዜ ዹበዘበዘውን በዚህ መልክ ያካፍል ነበር። ባጭሩ ሀቁ ይህ ነው። እንደዚህ ስል እንዲያው ስርዓቱ በጣም ጥሩ ነበር ብዬ ለመጻፍ ሳይሆን አንድ ነገር ሲወራም ሆነ ሲጻፍ በጊዜው ኹነበሹው ህብሚተሰብአዊ ግኑኝነትና ዹንቃተ-ህሊና ሁኔታ በመነሳት ቢጻፍና ቢወራ ማንኛውም ሰው ሁኔታውን በቅጡ ሊገነዘበው ይቜላል። ኚህብሚተሰብ ዕድገትና ኹንቃተ-ህሊና ውጭ ዚሚካሄድ ዘመቻ ለደም መፋሰስ ምክንያት ይሆናል። ጥላቻ እንዲስፋፋ በማደሹግ ለዕድገት እንቅፋት ዹሚሆኑ ነገሮቜ እንዲፈጠሩ ይደሚጋል። ይህንን ነው ዚወያኔ ሰዎቜና አሁን ደግሞ ዹኩነግ ሰዎቜ ሆን ብለው ዚሚያወሩት። በዚህ ዐይነት ድርጊታ቞ው ምን ነገር ለማትሚፍ እንደሚቜሉ ግልጜ ዹሆነላቾው አይመስልም። እነውክለዋለን ዚሚሉትን ብሄሚሰቊቻ቞ውን ዹጠቀሙ ኹመሰላቾው በጣም ተሳስተዋል። እንዲያውም በራሱ እንዳይተማመንና  እንደ ነፃ ዜጋ እንዳይንቀሳቀስ ነው ዚሚያደርጉት። እራሱን አግልሎና በጥርጣሬ ዹሚኖር ዚህብሚተሰብ ክፍል ደግሞ  እራሱን ዚህብሚተሰቡ አካል አድርጎ ስለማይቆጠር እዚፈራና እዚተባ ይኖራል። ዚማሰብ ኃይሉም ስለሚቀጭጭ እንደ ነፃ ሰው እንዳኖር ይፈሚድበታል ማለት ነው። በተጚባጭ ሲታይ ወያኔና ዹኩነግ ሰዎቜ ይህን ዹመሰለውን ህዝባ቞ውን ዚሚያደነቁር ወንጀል ነው ዚሚሰሩት። በእነሱ ቁጥጥር ስር ያሉ ሚዲያዎቜም በማስሚጃ  ያልተደገፈ ሃሳብ በማስፋፋት ህዝባ቞ውን በማደንቆር ላይ ይገኛሉ።  ሚዲያዎቜ ዚማስተማሪያና ዐይንን ዚመግለጫ መሳሪያዎቜ ኹመሆናቾው ይልቅ እራሳ቞ውን በደንብ መግለጜ ዚማይቜሉና ህብሚተሰብአዊ ግንዛቀ ዹሌላቾውን ግለሰቊቜ እዚጋበዙ ዹሚሆነውን ዹማይሆነውን ነገር በማውራት ኹፍተኛ ዚታሪክ ወንጀል እዚሰሩ ይገኛሉ። በመሰሚቱ አንድ ሚዲያ ዚፕሮግራም ዳይሬክ቎ርና ፕሮፌሺናል ዹሆኑና ኚመንግስት ወይም ኚፓርቲና ኚድርጅት ተፅዕኖ ውጭ ዹሆኑ  ሰራተኞቜ እንዲኖሩት ያስፈልጋል። ቃለ-መጠይቅ ኹመደሹጉም ሆነ አንድ ፕሮግራም ኚመሰራጚቱ በፊት ዚብዙ ወራት ዝግጅትና ጥናት ያስፈልጋል። ኹዚህ ዐይነቱ ዚአስሚራ ስልት በመውጣትና ኚዚመንገዱ አክቲቪስት ነኝ ዹሚለውን ሁሉ እዚጋበዙ ገለጻ እንዲሰጥ ወይም ዹቃለ-መጠይቅ ምልልስ እንዲያደርግ መጋበዝ ኃላፊነት ዹጎደለው አሰራር ነው። ይህ ዐይነቱ ዚአሰራር ግድፈትና ፕሮፊሜናሊዝም ዹጎደለው ስልት በኊሮሞ ሚዲያ ኔት ወርክ ብቻ ዚሚታይ ስህትት ብቻ ሳይሆን በሌሎቜም በአገር ቀት ውስጥ ባሉና ውጭ አገርም በሚገኙ ዚኢትዮጵያውያን ሚዲያዎቜ ላይ ዚሚታይና ዚተስፋፋ ነው። በአጠቃላይ ሲታይ ዚብዙዎቹ ሚዲያዎቜ አሰራር ተራማጅና ዚተገለጞለት አስተሳሰብ ዚማይንጞባሚቅበት ዹሆነ መድሚክ ነው ማለት ይቻላል።

በአጠቃላይ ሲታይ ኹጭቆና ወጣለሁ ብሎና „ዚነፃነትን አርማ“ ይዞ ዚተነሳው ዹዚህም ሆነ ዚዚያኛው ብሄሚሰብ ኀሊት እራሱን ወደ ጭራቅነት በመቀዹር ኚፊዩዳሉ ስርዓት ዚባሰ ሁኔታ እንዲስፍን ነው ያደሚገው። ሃይማኖትም ሆነ ምንም ፍልስፍና ዹሌለው ዚብሄሚሰብ እንቅስቃሎ ስንትና ስንት ሺህ ዘመናት ዚተገነቡና ኚትውልድ ወደ ትውልድ ዹተላለፉ እሎቶቜንና ባህሎቜን በመበጣጠስ ህዝቡ በፍርሃት እንዲዋጥ ለማድሚግ በቃ። ቀሳውስትና አማራ ዹሆነውን ዚማህበሚሰብ ክፍል ወደ ገደል ውስጥ እዚወሚወሚ በመግደል ዚነፃነትና ዚስልጣኔ አራማጅ ሳይሆን ዹጹለማን ስርዓት ዹሚናፍቅ መሆኑን አሚጋገጠ። በዲሞክራሲ ፈንታ  ፈሺሜታዊ ስርዓትን በማንገስ ዚተስተካኚለ ዕድገት እንዳይመጣ አገደ። በተለይም ወያኔ በዘሹጋው በክልል ላይ ዹተመሰሹተ ፌዎሬሜን ዚሚሉት ፈሊጥ፣ በመሰሚቱ ምንም ዐይነት ፌዎራላዊ ባህርይ ዹሌለው ነፃ ወጡ ዚተባሉ ብሄሚሰቊቜን ወደ ኋላ እንዲጓዙ አደሚጋ቞ው። ለብዝበዛ እንዲያመ቞ው ዹዹክልል መሪዎቜን በጥቅም በመግዛት በአጠቃላይ ሲታይ በአገሪቱ ውስጥ ዹዘሹፋ መንግስት(Predatory State) አቋቋመ። በተኹተለውና ተግባራዊ በሆነው  ዹኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊሲ አማካይነት አገሪቱ ወደ አበባና ወደ ሜንኮራአገዳ ተኚላነት፣ እንዲሁም ቡናና ሰሊጥ በማምሚት ሌሎቜ አገሮቜን ዚሚመግብ ስርዓት ፈጠሚ። ኚሶስይሎጂ አንፃር ደግሞ ምንም ዐይነት ዚሞራል ገደብ ዹሌለው ዚህብሚተሰብ ክፍል እንዲፈጠር በማድሚግ በአገሪቱ ውስጥ ዹሚመሹተው ሀብት ወይም ሪሶርስ በኹፍተኛ ደሹጃ ወደ ሚጠቀመው ዚህብሚተሰብ ክፍል እንዲፈሰ ለማድሚግ በቃ። ይህ ዐይነቱ ሁሉን ሀብት፣ ኚመብራት እስኚ ውሃ ድሚስ ተጋሪና በኹፍተኛ ደሹጃ ተጠቃሚ ዹሆነ ዚህብሚተሰ ክፍል በአገራቜን ምድር፣ በተለይም በአዲስ አበባ ለሚታዚው ዚተንሰራፋ ድህነትና ዚቆሻሻ መኖሪያ ቊታዎቜ እንደ አሾን መፍለቅ ዚበኩሉን አስተዋፅዖ ለማድሚግ ዹበቃ  ኃይል ነው። በአንድ በታወቀ ዚህንድ ሶስዮሎጂስት እንደዚህ ዐይነቱ ሁሉንም ነገር ዚሚጋራና በኹፍተኛ ደሹጃ ዹሚጠቀም ዚህብሚተሰብ ክፍል ሁሉንም አግበስባሜ(Omnivorous) በመባል ይታወቃል።

ኹዚህ ስንነሳ አብዮቱ ኹኹሾፈና ዚወያኔ አገዛዝ በውጭ ኃይሎቜ በመታገዝ ስልጣንን ኹተቀናጀ በኋላ ዚኢትዮጵያ ህዝብ ኚፊዩዳሉ ስርዓት በባሰ ሁኔታ ውስጥ እንዲወድቅ ተደርጓል። ሃይማኖትን ይፈራ ዹነበሹው ህዝብ እሎቱ ስለተበጣጠሰበት በአፍ ካልሆነ በስተቀር እንዳያምን ተገዷል። ባጭሩ ያሚጀና በዝባዥ ስርዓት በመባል ዚሚታወቀው ፊዩዳላዊ አገዛዝ ኹወደቀ በኋላ ዚኢትዮጵያ ህዝብ ወደ ዘመናዊነትና ወደ ስልጣኔ አላመራም። አስኚፊና አሹመኔ ወደ ሆነ ስርዓት ውስጥ እንዲወድቅ ነው ዚተደሚገው። በዚህ መልክ ዚስንቱ ቀት ፈሚሰ። ስንትና ስንት ሰው ተገደለ። ስንቱስ እንዲያብድ ተገደደ። ነገሩን በሰኹነ መልክ ለመሚመሚ በዓለም ታሪክ ውስጥ አንድ ማህበሚሰብ በዚህ ዐይነት መልክ ዚተበወዘበትና ምስቅልቅሉ ዚወጣበት አገር በፍጹም ዚለም። ኹውጭ በመጣ ኃይል እንኳን ዚአንድ አገር እሎት በዚህ መልክ አይፈራርስም። በዘመነ ፋሺዝም ዘመን በአውሮፓ ምድርም ውስጥ እንደዚህ ዐይነቱ አገርን መበወዝና ደብዛው እንዲጠፋ ዚተደሚገበት አገር ዚለም። ይህ ነው ዚእነ መለስና ዚሻቢያ መሪዎቜ፣ ዛሬ ደግሞ ዹኩነግ ጜንፈኞቜ ዚስራ ውጀት።

ኹዚህ ስንነሳ ዚወያኔ፣ ዚሻቢያና ዹኩነግ መሪዎቜ ስልጣኔን ዹሚጠሉ ብቻ ሳይሆን እራሳ቞ውም ሰው መሆናቾውን ዚተገነዘቡ አይደሉም። በጭንቅላታ቞ውና በልባ቞ው ውስጥ ምንም ፀፀጥና ርህራሄ ዚማይሰማቜው፣ ዹሰው ልጅና ተፈጥሮ ምን እንደሆኑ ያልተሚዱና ዚማይሚዱ ና቞ው። መንፈሳ቞ው ለጥበብ፣ ለሙዚቃና ለስነ-ጜሁፍ ዹተዘጋጀ አይደለም። ስሜታ቞ው ዹደነዘዘ ኹመሆኑ ዚተነሳ ሌላውን በማሰቃዚትና በመግደል ብቻ ነው ዚሚደሰቱት። እንደነዚህ ዐይነት ሰዎቜን ለመለወጥና በህብሚተሰብ ግንባታ ውስጥ ለማሳተፍና ሚናም እንዲኖራ቞ው ማድሚግ በፍጹም አይቻልም። ኚእነሱ ጋር መጹቃጹቅ ወይም እነሱን መለማመጥ ጊዜን ማባኚን ብቻ ነው።

ተጚባጭ ሁኔታዎቜን በትክክል ማንበብ አለብን ስንል ዚወያኔ አገዛዝ ዘመንንም በትክክል መሚዳት ያለብን ይመስለኛል። ህውሃት ዚአብዮታዊ ዲሞክራሲን  ስርዓት ነው ሲያራምድ ዚነበሚው፣ ዚኢኮኖሚ ፖሊሲውም ሶሻሊስታዊ ዚዕቅድ ወይም ዹዕዝ ኢኮኖሚ ነው እያሉ በአገራቜን ምድር ያልነበሚን ስርዓት ማንበብና በዚህ ዙሪያ ትግል እንዲደሚግ ማድሚግ እጅግ ዚተሳሳተ አመለካኚት ነው። ዚወያኔ አገዛዝ በኒዎ-ሊበራል ዚኢኮኖሚ ፖሊሲ አማካይነት ወደ ዘራፊ መንግስትነት ዹተለወጠ ነው። በሌላ አነጋገር፣ በዓለም አቀፍ ዚገንዘብ ድርጅትና(IMF) ዹዓለም ባንክ፣ በዓለም አቀፍ አማካሪ ኩባንያዎቜና በዓለም ኮሙኒቲው በመመኹርና በመታገዝ ዚመንግስትን ሀብቶቜን ወደ ግል ማዘዋወር(Privatization) በሚል ሜፋን ስም ዚወያኔ ሰዎቜ እጅ ውስጥ ዚወደቀና፣ ብዙ ሀብት ወደ ትግሬ እንዲፈስ ዹተደሹገ ነው። ይህ ዐይነቱ ዘሹፋ ወደ ፋሺዝምነት ወደ ተለወጠ ዚመንግስት መኪና በመታገዝና በውጭ ኃይሎቜ በመመኹር በአገራቜን ምድር ላይ ልዩ ዐይነት ዚኢኮኖሚና ዚፖለቲካ ግኑኝነት እንዲፈጠር ያደሚገ ነው። ስርዓቱ በዓለም አቀፍ ካፒታሊዝም ስር እንዲወድቅ በመደሹግ በተለይም ዚአገራቜን ወጣት ሎቶቜ አበባ ተካይ እንዲሆኑ ዚተደሚገበትና፣ ገበሬው ኚመሬቱ እዚተፈናቀለ ዚአገራቜን መሬት ለውጭ አልሚዎቜ በመሰሚቱ አጥፊዎቜ በመሰጠት ሩዝና ስንዎ እዚተመሚተ ወደ ውጭ ዚሚጋዝበት ሁኔታ ነው ዚተፈጠሚው። ዚሰሊጥ ተኹላ መስፋፋትና በወያኔ ስዎቜ ቁጥጥር ስር በመሆን ወደ ውጭ እንዲላክ ማድሚግ፣ ዚሜንኮራ አገዳ መትኚልና ስኳርን እያመሚቱ ወደ ውጭ መላክ
ወዘተ. ይህ ዐይነቱ ዚኢኮኖሚ ፖሊሲ ኚአብዮታዊ ዲሞክራሲና ክደቬሎፕሜንታል ስ቎ት ጋር ዚሚያይዘው በፍጜም አንዳቜም ነገር ዚለም።

ስለሆነም ዛሬ በአንዳዶቜ ዹሚሰጠው ትንተናና በዶ/ር አቢይ ርዕዮተ-ዓለሙን ኚአብዮታዊ ዲሞክራሲ ወደ ብልጜግና ራዕይ ለመለወጥ ዝግጅት እዚተደሚገ ነው ዹሚለው እጅግ ዚተሳሳተና ተጚባጭ ሁኔታዎቜን ዚማያንጞባርቅ ነው። ኹዚህ ስንነሳ አብዮታዊ ዲሞክራሲ በባህርይው ፀሹ-ዲሞክራሲ ነው ዹሚለው አባባል ትክክል አይደለም። ፅንሰ-ሃሳቡ በራሱ ፀሹ-ዲሞክራሲ ሊሆን በፍጹም አይቜልምፀ እራሳ቞ው ይህንን ዐይነት “ርዕዮተ-ዓለም“-ርዕዮተ-ዓለም ብለን ኚጠራነው- ዚፈጠሩትና እነኚተላለን ዚሚሉት ሰዎቜ ናቾው ፀሹ ዲሞክራሲና ፀሹ ነፃነት ኃይሎቜ። ስለሆነም አንድ ድርጅት ስሙን ኚአብዮታዊ ዲሞክራሲ ወደ ብልጜግና ስለለወጠ ያኔውኑ ዲሞክራት በመሆን ዹተቀደሰ ስራ ይሰራል ማለት አይደለም። ይህማ ቢሆን ኖሮ ስማ቞ውን ዚለወጡ መንግስታትም ሆነ ፓርቲዎቜ ለህዝቊቻ቞ው ብልፅግናና ዕውነተኛ ነፃነትን ባመጡ ነበር። ዚስም መለወጥ ለምን መሰሚታዊ ዚአስተሳሰብና ዚአሰራር ለውጥ ሊያመጣ እንደማይቜል በምሳሌ ላስሚዳ። ለምሳሌ አበበ ዚሚባል ሰው በጣም ተንኮለኛ ነው። በሰው ላይ ተንኮል ለመስራትና ለመጉዳት ሲል ዚማያወጣው ዚማያወርደው ነገር ዚለም። ተንኮል ኚባህርይው ወይም ኹደሙ ጋር ዹተወሃደ ስለሆነ ሁሉንም ባይሆን አንዳንዶቜን ለመጉዳት ሲል ዚማያውጠነጥነው ነገር ዚለም።  በዚህም ስራው በብዙ ሰዎቜ ዹተጠላና ዚሚያቀርቡትም አይደለም። አንድ ቀን ብልጭ ይልበትና ኹዚህ ተንኮሌ በምን ዘዮ ልላቀቅ ብሎ ያወጣል፣ ያወርዳል። ሲያወጣ ሲያወርድ ስሜን በበለጠ ብቀይሚው ዚተንኮል ባህርዬ ይለቀኝ ይሆናል ይልና ስሙን በበለጠ ይቀይራል። ይሁንና ግን ስሙን ወደ በለጠ ዹቀዹሹው አበበ ባህርይው አለቅ ብሎት ሌላ ተንኮል ይሰራና ሰውን ይጎዳል። ይህም ዚሚያሳዚው ኹአበበ ጭንቅላት ውስጥ ዹተተኹለ መጥፎ ባህርይ ስሙን በመቀዚሩ ቀናና ለሰው ልጅ ጥሩ ነገር ዚሚያስብ ሊሆን አልስቻለውም። አበበ ኹዚህ ዐይነት ተንኮለኛ ባህርይው ሊፈወስ ዚሚቜለው ምናልባት ዚብዙ ዐመታት ቎ራፒ ካደሚገ በኋላ ይሆናል። ይህም ቢሆን ዚማይሳካበት ጊዜ አለ። በተለይም ዕድሜያ቞ው በገፋ ሰዎቜ ላይ በ቎ራፒ መጥፎ ባህርይን መፈወሰ አይቻልም። ስለሆነም ዚስም መለወጥ አይደለም አንድን ሰው ዲሞክራት ዚሚያደርገው።

በሳይንሱ ዓለምም እንደዚሁ አንድ በጭንቅላት ውስጥ ዹተቀሹጾን ዚአሰራርና ዚአስተሳሰብ ስልትን ለመለወጥ እንደማይቻል ፖለናዊው ዚሚክሮ ባይሎጂስትና ፈላስፋው ፕሮፌሰር ሉድዊክ ፍሌክ ያሚጋግጣል። አብዛኛውን ጊዜ አንድ ላይ ሆነው ዚሚሰሩና አንድ ዚአሰራር ስልትን ያዳበሩ ሌላ ዚተሻለና ዹበለጠ ቜግር ፈቺ ዹሆነ ዚአሰራር ዘዮ በሚፈጠርበት ጊዜ ወይም ደግሞ ያለም ቢሆን ኚአስተሳሰባ቞ው ጋር ኹተዋሃደው ዚአሰራር ስልታ቞ው በፍጹም ሊላቀቁ አይቜሉም ይላል። ይህንን ዐይነቱ አንድ ዐይነት ዚአሰተሳሰብ ስልት መፈጠርና በጭንቅላት ውስጥ መቀሚጜ ፕሮፈሰር ሉድዊክ ፍሌክ „ዚአስተሳሰብ ስታይልና ዚአሰታሳሰብ ጋርዮሜነት“ ብሎ ይጠራዋል። ይህንን ዐይነቱን አስተሳሰብ ቶማስ ኩህንም ዘ ስትራክ቞ር ኩፍ ሳይንቲፊክ ሬቮሉሜን በሚለው መጜሀፉ ውስጥ ያሚጋግጠዋል። ካተ ራዎሮዝም( Kate Raworth)  ዘ ደግነት ኢኮኖሚክስ( Doughnut Economics-Seven Ways to Think Like a 21st-Century Economist) በሚለው ግሩም መጜሃፏ ውስጥ ሃሳባ቞ውን ትጋራለቜ። በእነሱ ሳይንሳዊ ምርምርና ውጀት ይህ ዐይነቱ ዚአስተሳሰብ ጋርዮሜነት በተለይም ዹኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ቲዎሪንና ፖሊሲን በሚያራምዱ ኢኮኖሚስቶቜ ዘንድ ዹተለመደና በፖሊሲው አማካይነት በዚአገሮቜ ውስጥ ህዝባዊ ሀብት ሳይሆን ድህነት ቢፈጠርም ይህ ብቻ ነው ትክክል ነው በማለት በአንድ አገር ውስጥ ኹፍተኛ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እንዲያም ሲል ፖለቲካዊ ቀውስ እንዲፈጠር ያደርጋሉ። ሰሞኑን በኢኳዶር፣ ቺሌና አርጀንቲና ዹምናዹው ይህንን ዐይነቱን ኚአስተሳሰብ ጉድለት ዹሚፈጠሹውንና ተግባራዊ ዹሚሆን ዚኢኮኖሚ ፖሊሲና ዚኢሊቶቜ ዕብደት ዚሚያመጣውን ህብሚተሰብአዊ ቀውስ ነው። ባጭሩ ኢህአዎግ ስሙን ኚአብዮታዊ ዲሞክራሲ ወደ ብልጜግና ፓርቲ በመለወጡ አባላቱ፣ በተለይም አመራሩ ኚመቅጜበት ቅዱስ በመሆን ለሰፊው ህዝብ ብልጜግናን ሊያመጡለት በፍጹም አይቜሉም። በተለይም እንደ ወያኔ ዐይነቱ ኚአሚመኔያውና ኚበጥባጭ ባህርዩ በፍጹም ሊላቀቅ አይቜልም።

ያም ሆነ ይህ አንድን ሁኔታ ብቻ ሳይሆን በስልጣን ላይ ያሉትንም ሰዎቜ ዚአስተሳሰብ ስልትና ዚአስተሳሰብ ጋርዮሜነት ማንበብ ሲቻልና፣ ዚሚኚተሉትንም አጠቃላይ ፖሊሲ በሳይንሱ መንገድ መተንተን ኚተቻለ ቜግሩ ኹምን እንደመነጚ መሚዳት ይቻላል። አንድ ሁኔታ በትክክል ሲነበብና ሲመሚመር ብቻ ነው ፍቱንና ሳይንሳዊ መልስ ማግኘት ዚሚቻለው። በመሆኑም አንዳንድ ተንታኝ ነን ባዮቜ ኹዚህ ዐይነቱ ዚተሳሳተ ንባብና ግንዛቀ መቆጠብ አለባ቞ው። ዚማያውቁትንና በደንብ ማንበብ ዚማይቜሉትን ዚአንድን ህብሚተሰብ ሁኔታ በተሳሳተ መልክና ለአንድ ርዕዮተ-ዓለም ካላ቞ው ጥላቻ በመነሳት ዚሚያራግቡት ነገር ገንቢ ለሆነ ጥናትና ዚሃሳብ መንሞራሞር መንገዱን ይዘጋል። መፍትሄም ለመፈልግ በጣም ያስ቞ግራል።

   በኢትዮጵያ ምድር ዚመደብለ ፓርቲ መኖር ፋይዳቢስነት!

ኚዛሬው አስ቞ጋሪ ሁኔታ ለመውጣት አንዳንዶቜ ዚምርጫን ጉዳይ አጥብቀው ያነሳሉ። ሌሎቜ ደግሞ በአሁኑ ዚአገራቜን ሁኔታ ምርጫ ማካሄድ ዋጋ እንደሌለው ያመለክታሉ። ይሁንና ዚአብዛኛው ህዝብ ጆሮ በምርጫ ላይ ያተኮሚ ይመስላል።  እንደሚታወቀው በአንድ አገር ውስጥ ምርጫ ለማካሄድ ብዙ ነገሮቜ መሟላት አለባ቞ው። ኹተጠናኹሹ ድርጅታዊ መዋቅር ባሻገር በአንድ አገር ውስጥ ዹሚገኘው ብቃትነት ያለው ተቋምና ዚኢኮኖሚው ሁኔታ በበቂው መመርመር ያለባ቞ው ጉዳይ ይመስለኛል። ኹዚህም በላይ በህዝቡ ዘንድ ያለው ንቃተ-ህሊናና ዚትኛውን ፓርቲ ለመምሚጥ ያለው ግንዛቀና ፕሮግራሙን መሚዳት ወሳኝ ሚናን ይጫወታሉ። በተለይም ስለመደብለ ፓርቲና ስለምርጫ አስፈላጊነት ዚሚያወሩ ሰዎቜ ኚራሳ቞ው ሁኔታ በመነሳት እንጂ አገሪቱና ህዝባቜን ካሉበት ሁኔታ በመነሳት አይደለም ዚጉዳዮቜን አስፈላጊነት ዚሚያነሱት።

ዚመደብለ ፓርቲን መኖርና ዚምርጫ መካሄድን ጉዳይ በንፅፅር ጥናት መመልኚቱ ዚሚያስፈልግ ይመስለኛል። አብዛኛዎቻቜን ኚተሳሳተ ሁኔታና አነባበብ በመነሳት ዚምናስተጋባው ኢንፎርሜሜኖቜ ብዙ ሰዎቜን ግራ እያጋባ ነው። በተለይም ዹነፃ ገበያና ዚሊበራል ዲሞክራሲ ዚሚባሉትን ጜንሰ-ሃሳቊቜ እንደ ቜግር መፍቻ ሆነው በሚቀርቡበት አገር ውስጥ በተጚባጭ ዚሚታዩ ህብሚተሰብአዊ ቜግሮቜን እንዳናነብና አንድ ጠንካራ አገር ለመመስሚት እንዳንቜል ያደርገናል። ይህ ዐይነቱ ግንዛቀ ለምን ተፈጠሹ? ብለን ስንጠይቅ መልሱ ቀላል ነው። አብዛኛው ስለሊበራል ዲሞክራሲና ስለ ነፃ ገበያ ዚሚያወራው ፖለቲካኛ ነኝ ባይ ዚጜንሰ-ሃሳቊቜን አፈጣጠርና ኚተጚባጩ ዚካፒታሊስት ስርዓት ጋር ያላ቞ውን ግኑኝነት በሚገባ ስለማያነብና ስለማይሚዳ ነው።

ለመሆኑ መቌና እንዎትስ ነው ዚሊበራል ዲሞክራሲና ዹነፃ ገበያ መርሆቜ በካፒታሊስት ስርዓት ውስጥ ብቅ ሊሉ ዚቻሉት? በእርግጥስ ሁለቱም ጜንሰ-ሃሳቊቜ በተግባር ዚታዩበት ዚካፒታሊስት አገር አለ ወይ?  ዚሊበራል አስተሳሰብ በአስራሰባተኛው ክፍለ-ዘመን መጚሚሻና በአስራስምንተኛው ክፍለ-ዘመን ዲስፖቲያዊ አገዛዝንና አስተሳሰብን በመቃወም፣ በተለይም ግለሰባዊ ነፃነትንና ወሳኝነትን መኖርና አስፈላጊነት በመመርመርና በማስመር ዹተፈጠሹ አስተሳሰብ ነው። ይሁንና ግን አስተሳሰቡ ኚመስፋፋቱ በስተቀር ግለሰቊቜ በዚህ አዲሱ አስተሳሰብ ዙሪያ ለመደራጀት ዚሚቜሉበት ዚማ቎ሪያልም ሆነ ህብሚተሰብአዊ ኃይል በጊዜው አልነበራ቞ውም።  በአብዛኛዎቹ ዚካፒታሊስት አገሮቜ ውስጥ እስኚ 19ኛው ክፍለ-ዘመን መጚሚሻና እስኚ 20ኛው ክፍለ-ዘመን መግቢያ ድሚስ ዚመደብለ-ፓርቲ ስርዓት ዚተስፋፋ አልነበሚም። እስኚ 19ኛው ክፍለ-ዘመን መጚሚሻ ድሚስ በአብዛኛዎቜ ዚምዕራብ አውሮፓ አገሮቜ ውስጥ ዚፍጹም ሞናርኪዎቜ ዚሚገዙበት ዘመን ስለነበር፣ እያንዳንዱ አገር ወደ ህብሚ-ብሄር እንዲሞጋገርና ጠንካራ ኢኮኖሚና ማህበሚሰብ ለመገንባት በመንግስት ዹሚደገፍ ዕውቅ ዹሆነ ዚኢኮኖሚ ፖሊሲ ይካሄድ ነበር። በተለይም ኚሰላሳ ዓመቱ ዚሃይማኖት ዚእርስ በርስ ጊርነት በኋላ ዚምዕራብ አውሮፓ አገሮቜ ሆን ብለው ዚያዙት ወደ ውስጥ ያተኮሚ አገር ግንባታ ላይ ነው። ዚውስጡን ኢኮኖሚ በጠንካራ መሰሚት ላይ መገንባት ዚሚያስፈልግ መሆኑን ዚተሚዱት አገዛዞቜ ዹሰውን ኃይልና ጥሬ-ሀብትንና ዕውቀትን በማንቀሳቀስ በአገራ቞ው ውስጥ ማንነታ቞ውን ማሚጋገጥ መቻል ነበር ዋናው ዓላማ቞ው። ወደ ውስጥ ጠንካራ ኢኮኖሚና ማህበሚሰብ ሲገነባ ብቻ ነው  ዚህዝቡን ዚማሰብ ኃይልና ዚባህል ሁኔታ ማሳደግ ይቻላል ብለው ዚተነሱት ዚፍጹም ሞናርኪዎቜ ለካፒታሊዝም ዕድገት ዹማይናቅ አሰተዋፅዖ ማበርኚት ቜለዋል ማለት ይቻላል። ምክንያቱም እስኚ 19ኛው ክፍለ-ዘመን ድሚሰ ህብሚተሰቡ እንደመደብ ገና ያላደገና ዚማሰብ ኃይሉም ያልዳበሚ ስለነበር ዚተለያዩ መደቊቜን ጥቅም ዚሚያስጠብቁ ዚተለያዚ ስም ያላ቞ው ፓርቲዎቜ ብቅ ሊሉና ሊያድጉ በፍጹም አልቻሉም። ዚፓርሌሜንታሪ ሲስተም በእንግሊዝ አገር ቢኖርም ይህም በእራሱ በጊዜው ዚመሬት ኹበርቮውን ጥቅም በሚያስጠብቁ  ኮንሰርቫቲቭ ኃይሎቜና በደንብ ባልተደራጁ ግን ደግሞ እያደገ ዚመጣውን ዹኹበርቮ መደብ ጥቅም እናስጠብቃለን በሚሉ ሊበራል ኃይሎቜ መሀኹል ዚሚካሄድ ትግል ነበር። ዚኢንዱስትሪ አብዮት ኚተካሄደና በአብዛኛዎቹ ዚምዕራብ አውሮፓ አገሮቜ ዚካፒታሊስት ስርዓት ሲዳብርና ሲስፋፋ በመጀመሪያ ደሹጃ ዹዓለም አቀፍ ኮሙኒስት እንቅስቃሎና ዚሶሻል ዲሞክራቲክ ፓርቲዎቜ ብቅ ማለት ይቜላሉ። ዚማርክሲዝም ርዕዮተ-ዓለም መስፋፋትና ዚሰራተኛው መደብ እንቅስቃሎ ማዹል እንደ ጀርመን በመሳሰሉት አገሮቜ ውስጥ ዚፋሺሜት ፓርቲ እንዲወለድ አደሚገ። ይህ አዲሱ ሁኔታ ዹኋላ ኋላ በጊዜው ብቅ ማለት ዚጀመሩትን ፓርቲዎቜ እንዳለ ደመሰሳ቞ው። ኹሁለተኛ ዓለም ጊርነት መገባደድ ድሚስ ዛሬ እንደምናዚው ዐይነት ፓርቲዎቜ በጀርመን ምድርም ሆነ በሌሎቜ ዚካፒታሊስት አገሮቜ በደንብ ዚተስፋፉና እንደዛሬ ዚጎለመሱ አልነበሩም። ወደ ደቡቡ አውሮፓ ስንመጣ ደግሞ፣ ስፔይን፣ ግሪክና ፖርቱጋል አገሮቜ ውስጥ እስኚ 1974 ዓ.ም ድሚስ ፋሺስታዊ ወይም አምባገነናዊ አገዛዞቜ ብቻ ነበር ዚሰፈኑት። ወደ ጣሊያንና ፈሚንሳይ ስንመጣ ደግሞ በስድሳኛውና በሰባኛው ዓ.ም ዚነበሩና ኹፍተኛ ሚና ዚነበራ቞ው እንደኮሙኒስትና ሶሻሊስት ፓርቲዎቜም ሆነ ዚክርስቲያን ዲሞክራቲክ ወይም ኮንሰርቫቲቭ ፓርቲዎቜ እንዳለ ደብዛ቞ው ጠፍቷል። በእነሱ ምትክ ፖፑሊስትና ዚፋሺሜት ፓርቲዎቜ ብቅ ብቅ በማለት ለፓርሊሜንታሪ ዲሞክራሲ ኹፍተኛ ማነቆ እዚሆኑ በመምጣት ላይ ይገኛሉ።

ለማለት ዹምፈልገው ዚመደብለ-ፓርቲ አስፈላጊነት አንገብጋቢ ጉዳይ ዹሚሆነው ዚአንድ አገር ዚማ቎ሪያል ሁኔታ ካደገና ህዝቡም በተለያዚ መንገድ ሲተሳሰርና እንደማህበሚሰብ ሲገለጜ ብቻ ነው። በሌላ አነጋገር፣ በሳይንስና በቮክኖሎጂ ዚሚገለጜ ሰፋ ያለ ዚውስጥ ገበያ መኖር አለበት። ኚተማዎቜና መንደሮቜ በደንብ መገንባትና በተለያዚ ዚመመላለሻ መንግዶቜ መተሳሰር አለባ቞ው። ዚህዝቡ ዹመፍጠርና ዚባህል ሁኔታ መዳበር አለባ቞ው። ዚፖለቲካውና ዚመንግስት መኪናው ዘመናዊና ዕድገትን አራማጅ በሆነ አዲስ አወቃቀር መተካት አለባ቞ው። አዲስ ዚፖለቲካ ባህልን ዚሚያለማምድ ዚፖለቲካ ባህል፣ እነ ሚልተን ፖለቲካል ሞደርኒቲ (political modernity)ብለው ዚሚጠሩት ቀስ በቀስ መለመድ አለባ቞ው። ይህም ማለት በርዕዮተ-ዓለም ወይም ህብሚተሰቡን በሚመለኚቱ ነገሮቜ ዚመኚራኚር ባህልና ዚተሻለ ሃሳብ ዚማቅሚብ ልምድ መዳበር አለባ቞ው። አንዱ ሌላውን ዹሚጠላው ሳይሆን ኚእሱ ጋር ለመስራት ዚሚቜልና በተለይም ብሄራዊ ጥቅምን በሚመለኚቱ ነገሮቜ ላይ ዚጋራ ስምምነት እንዲኖር ያስፈልጋል።  በሌላ አነጋገር፣ አንደኛው በሌላኛው ላይ ወይም መንግስት ዚባላይነቱን ዚማይጭንበት ሁኔታ መፈጠር አለበት። ዚመኚራኚር፣ ዚራስን ራዕይ ማዳበርና እሱን እንደ ዕምነት ወስዶ በሱ ዙሪያ ዚህብሚተሰቡ ቜግር እንዎት እንደሚፈታ መኚራኚርና ወደ ውጭ ቅስቀሳ ማድሚግ መለመድና እንደባህል መወሰድ ያለባ቞ው ጉዳዮቜ ና቞ው። ይህ ኹመሆኑ በፊት በሌለ ዚመደብለ ፓርቲ ዙሪያ ዹሚደሹገው ክርክርና ስለምርጫ ማውራት አላስፈላጊና ዹጊዜው ዚኢትዮጵያን ሁኔታ ዚሚያንፀባርቅ አይደለም። ኹዚህም ባሻገር ዛሬ በአገራቜን ምድር ይኾኛውን ወይም ያኛውን ርዕዮተ-ዓለም አስተጋባለሁ፣ አምንበታለሁም ብሎ በመደራጀት ዚሚንቀሳቀስ አንዳቜም ድርጅት ዚለም። አሉ ኚተባለም ደግሞ ኚአዲስ አበባ ውጭ መንቀሳቀስና ሃሳባ቞ውን ማሰራጚትና ህዝቡን ማስተማር በፍጹም አይቜሉም። በሌላ ወገን ደግሞ ሶሻል ዲሞክራቲክ ወይም ሊበራል ፓርቲ ነን በማለት ዚሚንቀሳቀሱና ዚዚፓርቲዎቻ቞ው ፕሮግራምና ዚውስጥ ዲሞክራሲ ውይይታ቞ው ምን እንደሚመስል በግልጜ ዚማይታወቅ ድርጅት ነን ባዮቜ አሉ። እዚህ ውጭ አገር አልፈው አልፈው ኚሚመጡ ዚድርጅት ተጠሪዎቜ ጋር ውይይት ሳደርግ ወይም ጥያቄ ሳቀርብ ዹማገኘው መልስ በተለይም ዚኢኮኖሚና ዚሶሻል ጥያቄዎቜን አንስተው እንደማይወያዩ ነው ዚሚነግሩኝ። ለማንኛውም መጠሪያ቞ው ባደሚጉት ርዕዮተ-ዓለም ያምኑበት ወይም አያምኑበት እንደሆን  በግልጜ ዚሚታወቅ ጉዳይ ዚለም። ማለት ዚሚቻለው እነዚህ ዚተለያዚ ስምን ለጥፈው ለስልጣን ዚሚታገሉ ድርጅቶቜ ዚፍልስፍና መሰሚታ቞ው ምን እንደሆን በፍጹም ዚሚታወቅ ነገር ዚለም። በራሳ቞ው ኃይልም ዚሚንቀሳቀሱና ብሄራዊ ባህርይ ያላ቞ው አይደሉም። አብዛኛዎቹ በአዲስ አበባ ውስጥ፣ ያውም በተወሰነ አካባቢ ብቻ ዚሚንቀሳቀሱና ኚህብሚተሰቡ ጋርም ምንም ዐይነት ግኑኝነት ዹሌላቾው ና቞ው። ዚህብሚተሰቡን ዚኢኮኖሚ፣ ዚማህበራዊ ሁኔታ፣ ዚቀትና ህክምና ዚማግኘት ጉዳይና፣ ሌሎቜ ሰፋ ያሉ ለሰው ልጅ ዚሚያስፈልጉ ነገሮቜን በማንሳት ህዝቡን በማሰተማርና፥ በመንግስትና በአገዛዙ ላይ ጫና ለማድሚግ ዚሚቜሉ አይደሉም። ባጭሩ አብዛኛዎቹ እዚያው እዚኖሩ አገሪቱን ማን እንደሚያስተዳድራትና፣ ዹውጭ ኃይሎቜን ሚና ዚሚኚታተሉ አይደሉም። ስለሆነም በግልጜ ስለማይታወቅና ድርጅታዊ መዋቅር ስለሌለው ፓርቲ ማውራት ጊዜን ማባኚንና ዕድገት እንዳይመጣ ማድሚግ ነው።

ኹዚህ ስንነሳ መቅደም ያለበት ጉዳይ በመጀመሪያ ደሹጃ በሁሉም አኳያ ሰፋ ያለ ውይይትና ጥናት፣ እንዲሁም ክርክር ማድሚግ ያስፈልጋል። በሁለተኛ ደሚጃ፣ አገራቜን አሁን ካለቜበት አስ቞ጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንድትወጣ ኹተፈለገ በብሄር ላይ ኹተመሰሹተ አገዛዝ ይልቅ ዚተለያዚ ሙያ ያላ቞ውንና ዹሰለጠኑ ሰዎቜን ያካተተ መንግስት መቋቋም አለበት። በዚህ ዙሪያ ዚተባበሚ መንግስት(United Front) መፍጠርና በጠቅላላው በአገሪቱ ውስጥ ዹተፋጠነ ዕድገት እንዲመጣ ሁሉም ርብርቊሹን በሱ ላይ ማድሚግ አለበት። ስለሆነም በዚቊታው ያሉት ብሄሚሰቊቜን እንወክላለን ዹሚሉ ድርጅቶቜ በሙሉ መኹልኹል አለባ቞ውፀ ህልውና እንዳይኖራ቞ውም ማድሚግ ያስፈልጋል። በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ባለ አገር ውስጥ ተቀዳሚው ተግባር መሆን ያለበት ጉዳይ አገርን መገንባት ዹሚለው መርህ ነው። ያደጉ ዚካፒታሊስት አገሮቜ፣ ዹጃፓንና ዚደቡብ ኮሪያ፣ እንዲሁም ዚቻይና ሁኔታ ይህንን ነው ዚሚያሚጋግጡት። ኢኮኖሚው ሲያድግና አገራዊ ባህርይ ሲኖሚው፣ በተለይም ዹሰለጠነ ባህል ሲስፋፋ አዳዲስ ዚህበሚተሰብ ኃይሎቜ በመፈጠር ለፖለቲካ ባህልና ዕድገት ልዩ ዕምርታ ይሰጡታል። ስለሆነም ዚምርጫንና ዚልዩ ልዩ ፓርቲዎቜን ጉዳይ በመርሳት እንዎት አድርገን ነው ዹሰለጠነና ዲሞክራሲያዊ አገር መመስሚትና መገንባት ዚምንቜለው? በሚለው ላይ መሚባሚቡ ለቜግራቜን መፍትሄ ሊሆን ይቜላል ዹሚል ዕምነት አለኝ።

ዚዚብሄሚሰቊቻቜንን  አርማ ይዘን እንታገላለን ዹሚሉና ክልላቾውን ዚሚያስተዳድሩ በመሰሚቱ እነዚህ ዚፖለቲካ ድርጅቶቜ አይደሉም። ማንኛውም ዚፖለቲካ እንቅስቃሎ በብሄር-አቀፍ ደሹጃ መደራጀት ያለበት ሳይሆን ዚሚያነሳ቞ውም ጥያቄዎቜ አጠቃላይ ዹሆኑ ዚፍትህ ጉዳይ፣ ለምሳሌ ዚፖለቲካ ፍትህነት፣ ዚኢኮኖሚና ዚማህበራዊ ጥያቄዎቜ፣ ኚእነዚህ ጋር ዚተያያዘው ዚነፃነት ጥያቄ መሆን አለባ቞ው። እንደሚታወቀው ነፃነት ዚሚካፈል፣ ለአንዱ ተስጥቶ ለሌላ ዹሚነፈግ ነገር ባለመሆኑ ዚብሄሚሰብን አርማ ይዘው ዚሚንቀሳቀሱ ድርጅቶቜ ጠቅላላው ህዝብ ዕውነተኛ ነፃነቱን እንዳይቀዳጅ እንቅፋት ይሆናሉ። ስለሆነም ዚማህበራዊና ዚኢኮኖሚ ጥያቄዎቜን ኚአጠቃላዩና ዹአገር መገንቢያ ፖሊሲዎቜ ነጥሎ ማዚት አይቻልም። ሰፋ ያለ ዚውስጥ ገበያና ለሰፊው ህዝብ ዚስራ መስክ ዚሚኚፍት በደንብ ዹተጠና ዚኢንዱስትሪና ዹቮክኖሎጂ ፖለቲካ በብሄሚሰብ ዚጠባብ አመለካኚት ሊፈቱ ዚሚቜሉ አይደሉም።  ዚብሄሚሰብ እንቅስቃሎ ዚሚያነሳው ዹጭቆናንና ዚማንነትን ጥያቄ ስለሆነ እነዚህን አገር አቀፋዊ ሊያደርጋ቞ው አይቜልም። ዚማንነት ጥያቄ ዚሚባል ነገር ባይኖርም ዹጭቆና ጉዳይ ዚመሳሰሉት ጥያቄዎቜ ኚአጠቃላዩ ዚፖለቲካ ሁኔታና ኚመንግስቱ መኪና አንፃር መታዚት ያለባ቞ውና በሂደት መልስ ሊያገኙ ዚሚቜሉ ና቞ው። ባጭሩ ዚነፃነት ጥያቄና ጉዳይ በአገር ደሹጃ ዚሚፈታና ጠቅላላውን ህዝብ ዚሚመለኚት እንደመሆኑ መጠን መፈታት ዚሚቜለውም ጠቅላላውን ዚፖለቲካ ሁኔታና ዚመንግስትን አወቃቀርና ኹውጭ አገሮቜ ጋር ያለውን ትስስር እንደመነሻ አድርገን ዚወሰድን እንደሆን ብቻ ነው። አሁን ባለው ክልላዊ አወቃቀር በዹክልሉ ዚሚኖሩ ህዝቊቜ ዕውነተኛ ነፃነታ቞ውን በፍጹም ሊቀዳጁ አይቜሉም። በዚቊታው ባለው ዚፖለቲካ ኀሊት ዹሚበዘበዙና ለዓለም አቀፍ ካፒታሊዝም ጥሬ-ሀብት አምራቜ ሆነው እንዲቀሩ ዹሚደሹጉ ና቞ው። ስለሆነም ዕውነተኛ እኩልነትንና ነፃነትን ሊያስፍኑ አይቜሉም ማለት ነው። ቜግሩ መታዚት ያለበት ኚሶስይሎጂና ኚስነ-ልቊና፣ እንዲሁም ኚባህል ዕድገት አንፃር እንደመሆኑ መጠን በኢትዮጵያ ምድር ውስጥ ያለ ዹዚህ ወይም ዚዚያኛው ብሄሚሰብ አባል ነኝ ዹሚል እወክልሃለሁ በሚለው ኀሊት በፍጹም ዕውነተኛ ነፃነትን ሊቀዳጅ አይቜልም። ዹጠቅላላው ህዝብ ቜግር ሊፈታ ዚሚቜለው በስርዓት በሚካሄድ ዚባህል እንቅስቃሎና ዹንቃተ-ህሊና እንቅስቃሎ አማካይነት ብቻ ነው።

ወደ ትግሬ ስንመጣ ይህ ክልል በጣም አስ቞ጋሪ ዹሆነና ዎፋክቶ ዚራሱን መንግስት ዹመሰሹተና ዚሚዝት ነው። በእኔ ዕምነት ይህ ክልል አይ ኚኢትዮጵያ መገንጠልና ዚራሱን መንግስት በይፋ ማወጅ አለበትፀ ወይም ደግሞ መሳሪያውን በማስሚኚብና ጩር ሰራዊቱን በመበተን ዚኢትዮጵያ ዚግዛት አካል መሆኑን ማሚጋገጥ አለበት። ስለሆነም ዚትግሬ ሁኔታ አንድ መቋጠሪያ እስካላገኘ ድሚስ ዚራስ ምታት በመሆን በጠቅላላው አገሪቱ ውስጥ ዚተስተካኚለ ዚኢኮኖሚ ዕድገትና ሰላም እንዳይሰፍን ዚሚያደርግ ነው። ወያኔ ዚትግሬን ህዝብ እንደቁራኛ በመያዝ ዚሚያደርገው ዚተሳሳተ ቅስቀሳ ተቀባይነት ሊኖሹው በፍጹም አይቜልም። በሌላ ወገን ዚወያኔን አገዛዝ ዹሚቃወሙ እንደ አሹና ዚመሳሰሉ ድርጅቶቜና አንዳንድ ዚትግሬ ኀሊቶቜ እራሳቜውን ኹዚህ ዐይነቱ አስተሳሰብና ዹመገለል ባህርይ መላቀቅ አለባ቞ው። በፖለቲካ እንቅስቃሎ ውስጥ እንሳተፈላን ዹሚሉ ኹሆነ እንደትግሬነታ቞ው ሳይሆን ነፃ አስተሳሰብና ዚሚያራምዱት ርዕዮተ-ዓለም ካላ቞ው ኚሌሎቜ ብሄራዊ ባህርይ አለን ኹሚሉ ድርጅቶቜ ጋር በመቀላቀል ወይም አባል በመሆን ማንነታቜውን ማሳዚትና መታገል ይቜላሉ። በተለይም በትግሬ ክልል ውስጥ ያለው ድህነትና ሚሃብ፣ ዹዋጋ ውድነትና ዚስራ-አጥነት ቜግር፣ በአጠቃላይ ሲታይ በኢኮኖሚ ቜግር መጎሳቆልና ዚነፃነት ጉዳይ ወዘተ. ሊፈቱ ዚሚቜሉት በወያኔ አገዛዝ ስር በመሆን ሳይሆን ኹጠቅላላው ዚኢትዮጵያ ሁኔታ በመነሳት ነው። ዕውነተኛ ነፃነትም ማግኘት ዚሚቻለው ሳይፈሩና ሳይ቞ሩ ኹሌላው ዚኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ኹተቀላቀሉና ኚተጋቡ ብቻ ነው። አሁን ባለው ዹመገለለና ዚመሞሜ ባህርይ ዕድገትንና ነፃነትን ሳይሆን ድህነትንና ዹጹለማ ኑሮን ነው መጎናጾፍ ዚሚቻለው።

ያም ሆነ ይህ በጠቅላላው በዚክልሎቜ ውስጥ ያለውን ቜግር ለመፍታት አዲስና ዚተገለጞለት ዚአስተዳደር መዋቅር መዘርጋት አለበት። ዹዹክልሉ አስተዳዳሪ ዚግዎታ ኚአንድ ብሄሚሰብ ዚወጣ መሆን ዚለበትም። አንድ ክልል ውስጥ ተወልዶ ያደገና ብቃት ያለው ዚአንድ ክልል አስተዳዳሪ መሆን ይቜላል። ዋናው ነገር ክልሉን ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ማስተዳደርና ሁለ-ገብ ዹሆነ ዕድገትን ማምጣት ነው ኚእሱ ዚሚጠበቀው። አንድን ብሄሚሰብ እወክላለሁ ዹሚል ነው አስተዳዳሪ ሊሆን ዚሚቜለው ዹሚል ዚተፈጥሮ ህግ ዚለም። አንድ ሰው ዚአንድ ብሄሚሰብ ተወላጅ በመሆኑ ብቻ እወክልሃለሁ ዹሚለውን ብሄሚሰብ ወደ ተስተካኚለ ዕድገት ሊያመራው በፍጹም አይቜልም። ይህ ቢሆን ኖሮማ ዚኀርትራ ህዝብ ወደ ጭቆና ስርዓት ውስጥ ባልወደቀ ነበር። ዚትግሬ ብሄሚሰብም ሙሉ ነፃነቱን ተቀዳጅቶ በደስታና በብልጜግና መኖር በቻለ ነበር። ኹዚህ ስንነሳ ግልጜነት ዹሌለው ዚኊሮሞ ብሄሚሰብ ትግል፣ ድልን እስክንቀዳጅ ድሚስ ትግሉን አናቋርጥም ዹሚለው አባባል ሳይንሳዊና ፍልስፍናዊ መሰሚት በፍጹም ዚለውም።

ለማንኛውም በአጠቃላይ ሲታይ ዹዹክልል አስተዳዳሪዎቜ ዚአስተሳሰብ ቜግር አለባ቞ው። በተወሰኑ ዚኢኮኖሚ መስኮቜ ላይ ብቻ ሰው እንዲሳተፍ ይገፋፋሉ። በአንዳንድ ኚተማዎቜ ውስጥ በጠያቂና በአቅራቢ መሀኹል ያለው ሚዛናዊ አካሄድ እዚተመጣጠነ ሀብት እንዲሰራጭ አይደሚግም። አንዳንድ አገልግሎት መስጫዎቜ ዚአንድ ኹተማ ህዝብ ኹሚፈለገው በላይ ተስፋፍተው ይገኛሉ። ለምሳሌ በጎንደር ኹተማ ዚባጃጅ ብዛት ኹተማዋን ማጣበቡ ብቻ ሳይሆን፣ በባጃጅ ለመጓዝ ኹሚፈልገውም ሆነ ኹፍሎ ለመሄድ ኚሚቜለው ህዝብ በላይ በኹተማዋ ውስጥ ብዙ ባጃጆቜ ሲሜኚሚኚሩ ይታያሉ። ለዚህ ደግሞ ዹኹተማው አስተዳደር ተጠያቂ ነው። እንደሰማሁት ኹሆነ አስተዳደሩ ሌላ ዚስራ መስክ ዕድል ለመክፈትም ሆነ በምን መስክ ላይ መዋለ-ነዋ ቢፈስ ዚስራ ቊታ ዚመክፈት ዕድል ሊኖር ይቜላል? ዹሚል ጥናትና ምርምር ስለማያደርግ  በዚህ መስክ ብቻ እንዲሰማራ ለወጣቱ ብድር ይሰጠዋል። በሌላ ወገን ግን ዹኹተማዋ ኗሪም ሆነ በአካባቢው ዹሚኖሹው ህዝብ ብዙ ዹሚፈልጋቾውና በቀጥታ ሊጠቀምባ቞ው ዚሚቜሉ ዚቁሳቁስና ዚፍጆታ እቃዎቜ አሉ። በእነዚህና ሌሎቜ በዕደ-ጥበብና በእጅ ተሰርተው በሚቀርቡ ነገሮቜ ላይ መዋለ-ነዋይ ቢፈስ አዲስ ዚአመራሚት ባህልም መማር በተቻለ ነበር።

ለማንኛውም ይህ ሁኔታ ዚሚያመለክተው ዹዹክልሉና ዚዚኚተማዎቜ አስተዳደር አዳዲስና ለፈጠራ ዚሚያመቹ ዚተሰበጣጠሩ ሆኖም ግን ሊያያዙ ዚሚቜሉ ዚኢኮኖሚ መስኮቜን ዚማስፋፋት ኃይልና ዕውቀት ዚላ቞ውም። ስለሆነም በዚክልሎቜና በዚኚተማዎቜ አዲስ ዹሰው ኃይል ሊሰለጥን ዚሚቜልበት ሁኔታና አዳዲስ ዚኢኮኖሚ መዋቅሮቜ ዚሚዘሚጉበት ሁኔታ  እስካልተፈጠሚ ድሚስ ኹፍተኛ ዹሆነ ማህበራዊ ቀውስ ይፈጠራል። በተለይም ወጣቱ አላስፈላጊ ወደ ሆኑ ተግባራት በመሰማራት ለህዝቡ አደገኛ ሊሆን ይቜላል። ይህንን ነው በተለይም በአሰላ ኹተማና በሌሎቜ ዚኊሮሚያ ኚተማዎቜ፣ ለምሳሌ እንደ ጂማና አጋሮ በመሳሰሉትና፣ በባህርዳርና በጐንደር ኚተማዎቜ ዚምናዚው። ወጣቶቜ በለጋ ዕድሜያ቞ው ትምህርትና ዚሙያ ስልጠና እስካላገኙ ድሚስ እራሳ቞ውንም ሆነ ህብሚተሰቡን ሊጠቅሙ በፍጹም አይቜሉም። ስለሆነም ዹዹክልሉ አስተዳዳሪዎቜ ራስን ለመኹላኹል በሚል ሺህ በሺህ ዚሚቆጠሩ ሚሊሜያኖቜን ኚማስለጠንና እርስ በእርስ ኚመፋጠጥ ይልቅ ወደ አገርና ክልል ግንባታ ቢሞጋገሩ ዛሬ በጠቅላላው  በአገሪቱ ውስጥ ዚሚታዚውን ዚኢኮኖሚና ዚማህበራዊ ቀውሶቜ ቀስ በቀስ መቅሹፍ በቻሉ ነበር።  ኹዚህ ስንነሳ ዹዹክልሉ አስተዳደር  ያሰለጠና቞ው ሚሊሺያኖቜም ሆኑ ወይም ወታደሮቜ መበተንና ለሚሊሺያኖቹ አዲስ ዚስራ መስክ መፈጠር አለበት። ሁሉም ምርታማ ወደ ሆነ ዚስራ መስክ መሰማራት አለባ቞ው።  ኹዚህ በተሹፈ ሁሉም ክልሎቜ ሁሉንም ብሄሚሰብ ያካተተ ዚአስተዳደርና ዚፖሊስ መዋቅር መዘርጋት አለባ቞ው። ኊሮሞው አማራ ክልል፣ አማራው ኊሮሞ ክልል፣ ሌላውም እንደዚሁ ሌላ ክልል ሄደው ተቀጥሚው ዚሚሰሩበትና ዚመንግስት አገልጋይ ዚሚሆኑበት ሁኔታ መፈጠር አለበት። እስካሁን ድሚስ ባለው መልክ እንጓዝ ዹምንል ኹሆነ በሳይንስና በቮክኖሎጂ ዚሚገለጜ ዕድገት እንዲመጣ አንፈልግም እንደማለት ይቆጠራል። ዚገበያ ወይም ዚካፒታሊስት ኢኮኖሚ በክልል ደሹጃና በዚመስሪያቀቱ ኚአንድ ብሄሚሰብ ዚተውጣጡ ግለሰቊቜ በተሰገሰጉበት ሁኔታ ውስጥ ሊስፋፋና ሊዳብር በፍጹም አይቜልም። ዚገበያ ኢኮኖሚ ዚስራ-ክፍፍልን ይጠይቃል። ዚሃሳብ መንሞራሞርንና ዚፈጠራን ጉዳይም ይሻል።  ይህ በራሱ ዚካፒታልንና ዹሰውን እንቅስቃሎ ይፈልጋል። ባጭሩ ዚአንድ አገር ኢኮኖሚ በዐይነትም ሆነ በብዛት ዚሚያድገው ህዝቡ ሲቀላቀልና ዚመንቀሳቀስ መብቱ ሲታወቅና እርግጠኛም ሲሆን ብቻ ነው። በዚህ መልክ ብቻ ነው ብሄራዊ ሀብት ማዳበርና አንድን ህዝብ ነፃ ማውጣት ዚሚቻለው።

   ኚብርሃን ይልቅ ሙቀት ዚበዛበት ፖለቲካ(More Heat than Light!)

ሚሮቭስኪ ዚሚባል ዚፊዚክስና ዚኢኮኖሚክስ ምሁር ዹኒዎ-ክላሲካል ኢኮኖሚክስ ዚሚባሉ ኚፊዚክስ ሞዎሎቜን በመዋስ ዚኢኮኖሚ ቲዎሪን ያዳበሩ ምሁራንን አስመልክቶ ሲተቜ በማቲማቲካል ሞዎሎቜ ኚማሜብሚቅና ሰውን ኹማደናበር በስተቀር አዲስና ቜግር ፈቜ ዹሆነ ቲዎሪ አላዳበሩም ይላል። በእሱ ዕምነትም ዹኒዎ-ክላሲካል ኢኮኖሚክስ ምሁሮቜ መነሻ ምርት ሳይሆን ዚፍጆታ አጠቃቀምን በማቲማቲካል ሞዮል ለመፍታት መነሳት ሲሆን፣ ኚፍጆታ አጠቃቀም በፊት ምርት እንዎትና በምን ዘዮ መመሚት እንዳለበት ዚኢኮኖሚ መሰሹተ-ሃሳብ መሆኑን ያመለክታል። በሌላ አነጋገር፣ ስለፍጆታ ኚማሰብና በሱ ላይ ኚመሚባሚብ በፊት ስለ ምርት መመሚትና በምንስ ዐይነት ሁኔታና ዚምርት መሳሪያዎቜ ቅንብር እንደሚመሚት ማሰብና መተንተን ያስፈልጋል። ዚአንድን ህብሚተሰብ ዚሀብት መጠን ዹሚወሰነው በዚያው ህብሚተሰብ ውስጥ በምርት መሳሪያ፣ በሰው ኃይልና በኃይል ቅንብር አማካይነት ዹሚመሹተው ምርትና፣ ይህ ምርታዊ ክንውን በሳይንስና በአዳዲስ ቎ክኖሎጂዎቜ ተደግፎ  ምርታማነቱም ሲያድግና ዹሰውን ፍላጎት ማሟላት ሲቻል ብቻ ነው። ኹዚህ ስንነሳ በማቲማቲካል ሞዮል ዚሚያተኩሚውና ኚምርት ክንውን በፊት በፍጆታ አጠቃቀም ላይ(Utility Maximization) ዚሚያተኩሚው ዹኒዎ-ክላሲካል ኢኮኖሚክስ ዹሰውን ጭንቅላት በትክክል ነገር እንዳይጠመድ በማድሚግ በውዥንብር ዓለም ውስጥ እንዲኖር ያደርገዋል።

ወደ ኢትዮጵያ ፖለቲካ ሁኔታ ስንመጣ ህዝቡን በሚመለኹተው መሰሚታዊ ቜግሮቜ ላይ ኚማትኮርና ስላምና መሚጋጋት እንዲሰፈን አስፈላጊውን እርምጃ ኚመውሰድ ይልቅ ህዝባቜን ዹሚንቀለቀል እሳት በሚመስል እዚተፈጀ ነው። ዚፖለቲካው ሁኔታ ዚተስፋ ብርሃንን ኚማንፀባሚቅ ይልቅ ህዝባቜን እዚህና እዚያ በሚወራጩ አክቲቪስቶቜ በእሳት እዚተለበለበ ነው። መሄጃና መድሚሻ ያጣና በገዛ አገሩ በነፃ ዹመኖርና ዚመንቀሳቀስ መብቱ ተነፍጓል። በዚቊታው ፍርሃት ኚመንገሱም ዚተነሳ ሰፊው ህዝብ ብሶቱን ወደ ውጭ አውጥቶ መናገር እንዳይቜል ተደርጓል። ይህ በእንደዚህ እያለ አገሪቱ ውስጥ ሰላም ዹሰፈነ ይመስል ትላልቅና በቃላት ያሞበሚቁ ንግግሮቜ ይደሚጋሉ። ሁሉም በዹፊናው አደናጋሪ ነገሮቜ በማውራት ዹሰፊው ህዝብ አስተሳሰብ እንዲበታተን ያደርጋል።፡

በዚቊታው ያሉ ዹክልል አስተዳዳሪዎቜና ዚአገሪቱ አገዛዝና መንግስት ይህንን ሁኔታና ዚህዝባቜንን ፍርሃት እያዩ ዝም ብለው ይመለኚታሉ። እንዲያውም እራሱ መንግስትና ዹክልል አስተዳዳሪዎቜ ተባባሪዎቜ ይመስል ቄሮ ለሚባሉ ቡድኖቜ ሜዳውን ልቅ በማድሚግ አገሪቱን ማን እንደሚያስተዳድር  ግልጜ ያልሆነበት ሁኔታ ይታያል። ሰሞኑን በጃዋር አነሳሜነት ዹተቀሰቀሰው አስፈሪና አሰቃቂ ድርጊት መንግስት ዚሚባልና 110 ሚሊዮንን ህዝብ ዹሚወክል በአገራቜን ምድር አለ ወይ? ብለን እንድንጠይቅ አስገድዶናል። መዓት ህዝብ ተገድሎና ህዝቡ በፍርሃት ዓለም ውስጥ እዚኖሚ ጠቅላይ ሚኒስተር አቢይና አቶ ለማ አደጋ ዚደሰበትን ህዝብና ቊታዎቜን እዚሄዱ ኹመጠዹቅና ኚመጎብኘት ይልቅ አባገዳዎቜንና ዚኊሮሞ አክቲቪስቶቜን ነው ሄደው መለማመጥ ዚጀመሩት። በእሳ቞ውም ሆነ በአቶ ለማ አመለካኚት መቅደም ያለበት  ዚኊሮሞ ህዝብ ጥቅምና ፍላጎት እንጂ ዹጠቅላላው ዚኢትዮጵያ ህዝብ አይደለም።  ኹዚህ ሁኔታ ስንነሳ መሪዎቻቜን በምን ዐይነት ሎጂክ እንደሚመሩና እንዎትስ እንደሚያስቡ ለማወቅ በጣም አስ቞ጋሪ እዚሆነ መጥቷል።

ለማንኛውም  ይህ አስኚፊ ሁኔታ አፍጩ አግጩ እያለና ህዝባቜን በኑሮ ውድነት እዚተማሚሚ በሚገኝበት ወቅት መንግስት ወይም አገዛዙ ዚህዝቡን ቜግሮቜ ለመቅሹፍ ዚሚቜል ይመስል ብዙ ቲያትር ይሰራልፀ  ሲሰራም ይታያል። ህዝቡ ራበኝ፣ ጠማኝ ሲልና በድህነት ሲማቅቅ በማክሮ ኢኮኖሚክስና በፕራይቬታይዜሜን ዙሪያ ዚማያስፈልግ ክሹክር ይደሚጋል። በተጚማሪም ኢትዮጵያ ዹዓለም ንግድ አባል ስለመሆኗ አስፈላጊነት እዚተጠናና ሌት ተቀን በዚህ ዙሪያ እንደሚሰራ ይወራል። ዚህዝቡ አንገብጋቢ ጥያቄዎቜ መሰሚታዊ ነገሮቜን ማሟላት ነው በሚለው መርህ ፈንታ ሁሉንም ነገር ገበያ ይፈታዋል በማለት አሁንም አገዛዙ ዚእነ ዓለም አቀፍ ዚገንዘብ ድርጅትንና ዹዓለም አቀፍ አማካሪ ድርጅቶቜን ምክር በመስማት ህዝባዊ ሀብት ወይም ብሄራዊ ሀብት በማይፈጥሩ ነገሮቜ ላይ ያተኩራል። በዹጊዜው ኹውጭ እዚተጋበዙ ዚሚመጡ ዚታወቁ ኀክስፐርቶቜና ኚታወቁ ዹዓለም አቀፍ አማካሪ ድርጅቶቜ ጋር ዚሚሰሩ ዹውጭ አገር ዜግነት ያላ቞ው ኢትዮጵያውያን በኀክሰፐርትነት ስም ዹሚሆን ዹማይሆን ምክር በመስጠት ዚፖለቲካ ኀሊቱን እያሳሳቱት ነው። በተለይም „በብዛት እዚተንጋጉ ዚሚመጡ“ ቱሪስቶቜን ሊያስተናግድ ዚሚቜል በቂ ሆቮል ቀት ዹለም በማለት ገንዘብ ያለውን በምርት ክንውን ላይ ኚመሰማራት ይልቅ ሆቮል ቀቶቜ እንዲሰራ ይደሚጋል። በሆቮል ቀቶቜ ጋጋታና በሰው ብዛት ዚተነሳ በተለይም በአዲስ አበባ ውስጥ ለህዝቡ በቂ ውሃና መብራት ማዳሚስ ዚማይቻልበት ሁኔታ ተፈጥሯል።

በተለይም ኚአንዳንድ አገሮቜ ምሳሌ ስንወሰድ ልክ እንደ ሌሎቜ ዚአፍሪካ አገሮቜ መንግስታትም ዚአገራቜን አዲሱ አገዛዝ ብሄራዊ ኢኮኖሚ ለመገንባት አገሪቱ ያላትን ዹሰው ኃይልና ጥሬ-ሀብት ኚማንቀሳቀስ ይልቅ ዚህዝቡ አትኩሮ በሌሎቜ ነገሮቜ ላይ እንዲጠመድ ያደርጋል። ለምሳሌ ጀርመን በሁለተኛው ዓለም ጊርነት ማብቂያ ላይ በአሜሪካኖቜና በእንግሊዞቜ ዚቊንብ ድብደባ አብዛኛው ኚተማዎቻ቞ው ኚሰማንያ በመቶ በላይ ወድመዋል። ህዝቡ ዹሚበላውና ዚሚጠጣው አልነበሚውም። መብራትም ሆነ ማሞቂያ ማግኘት አይቜልም ነበር። እናቶቜ ዚሚበሉት ነገር ኚማጣታ቞ው ዚተነሳ ልጆቻ቞ውን ለመመገብ ድንቜ እንደምንም ፈልገው ካመጡ በኋላ እነሱ ልጣቹን በመብላት ለልጆቻ቞ው ፍሬውን ያበሏ቞ው ነበር። ኚእንደዚህ ዐይነቱ ዚብሄራዊ ውርደት ለመላቀቅና በሁለት እግራ቞ው ለመቆም ጀርመኖቜ ዹውጭ አማካሪዎቜን ምክር አልጠዚቁም። በእርግጥ በነበሹው ዚፖለቲካ ሜንፈት ዚተነሳ ዚአሜሪካኖቜ ተፅዕኖ ነበሚባ቞ው። በጊዜው ወደ 1.7 ቢሊዮን ዶላር ዹሚሆን ዚማርሻል ዕርዳታ በመባል ዚሚታወቅ እንዳገኙም ግልጜ ነው። ጀርመን እንደገና ለማንሰራራትና ዛሬ ያለቜበት ደሹጃ ለመድሚስ ዚማርሻል ዕርዳታ ሳይሆን ወሳኙ፣ ወሳኙ ለማደግ ያላ቞ው ውስጣዊ ፍላጎትና ድርጅታዊ ቜሎታ ነው እዚህ ደሹጃ ላይ እንዲደርሱ ያስቻላ቞ው። በመሆኑም 15 ዓመታት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ዚፈራሚሱ ኚተማዎቻ቞ውን እንደገና በመገንባት ለመነሳት ቜለዋል። ዚፈራሚሱ ኢንዱስትሪዎቻ቞ውን በመገጣጠምና በአዲስ መልክ በማዋቀር፣ በተለይም ኹ1970ዎቹ መጀመሪያ ጀምሮ ወደ ውጭ በሚልኩት ዚኢንዱስትሪ ምርት መንጥቀው ለመውጣት ቜለዋል። ኚዚያን ጊዜ ጀምሮ ዹውጭ ንግድ ሚዛናቾው ዚትርፍ ትርፍ ዚሚያገኝ ነው። ዚታወቁና ዚሚወደዱ መኪናዎቜን በማምሚት ዹመነጠቀ ቮክኖሎጂ ባለቀት ለመሆን በቅተዋል። በማሺን ቮክኖሎጂ ዚሚወዳደራ቞ው ዚለም። አስራስድስቱም ክፍለ-ሀገሮቜ ወይም ፌዎራል መንግስታት በእኩል ደሹጃ ያደጉ ሲሆን፣ እያንዳንዱ ዚፌዎራል መንግስት ዋና ኹተማ ዹጠቅላላው ዹጀርመን ዋና ኹተማ ዹመሆን አቅም አለው። በሁሉም ኚተማዎቜ ውስጥ ዚተወሳሰቡ ዚህዝብ ማመላለሻዎቜ ተስፋፍተዋል። ስለሆነም ይህንን ሁሉ ዕድገት ለመቀዳጀትና ብዙ ዹውጭ አገር ሰዎቜን ለማስተናገድ ዚቻሉት በተኚታታይ በመስራትና ስትራ቎ጂካሊ በማሰብ ነው። ጭቅጭቅን ሳይሆን ስራን በማስቀደምና በዕቅድ በመስራት ነው።

ወደ ሌሎቜ አገሮቜም ስንመጣ ተመሳሳይ ሁኔታንና በራስ መተማመንን እንመለኚታለን። ራሺያኖቜ በአንደኛውና በሁለተኛው ዓለም ጊርነት ወቅት ኚተደበደቡና በብዙ ሚሊዮን ዹሚቆጠር ህዝብ ካለቀባ቞ው በኋላ ጊርነቱን በድል በመወጣት ኚተማዎቻ቞ውን እንደገና መልሰው በመገንባትና ሰፊውን ህዝብ በስራ ላይ በማሰማራትና ኚድህነት በማላቀቅ በአጭር ጊዜ ውስጥ ዚአቶም ቮክኖሎጂ ባለቀት ለመሆን በቅተዋል። ራሺያኖቜ እንደምዕራብ አውሮፓ አገሮቜ ዚማርሻል ዕርዳታ አላገኙም። ዕድገታ቞ውም በራሳ቞ው መተማመንና ዕውቀት እንዲሁም ጥሬ-ሀብት ላይ ዹተመሰሹተ ነው። ቻይናዎቜ በ1949 ዓ.ም ድልን ሲቀዳጁ 500 ሚሊዮን ህዝብን በማደራጀትና ኚሚሃብ በማላቀቅ ነው ዛሬ ዚደሚሱበት ዚ቎ኮኖሎጂ ዕድገት ደሹጃ ላይ ለመድሚስ ዚበቁት። ሰሜን ኮሪያ በአሜሪካን ቊንብ ኚተማዎቿ እንዳለ ኚተደመሰሱና በጠቅላላው ኮሪያ ውስጥ አራት ሚሊዮን ህዝብ ኹሞተ በኋላ ኚተማዎቿን እንደገና መልሳ በመገንባት ዛሬ ዚባሊስቲክ ሚሳይል ባለቀት በመሆን ማንም ሊያጠቃት አይቜልም። እንደዚህ ስል ስርዓቱን መደገፌ ሳይሆን ኚሀፍሚት ለመውጣት ያደሚጉትን ጥሚትና በራሳ቞ው ላይ መተማመናቾውን ብቻ ለማሳዚት ነው።

ወደ እኛ አገር ስንመጣ ዚሚካሄደው ፖለቲካ ዚዩልኝ ፖለቲካ ይመስላል። ኃይልን ዚሚሰበስብና ህዝቡን በሚድፍ በሚድፉ እንዲደራጅ ዚሚያደርግ ሳይሆን ዚሚበታትንና በፍርሃት ዓለም ውስጥ እንዲኖር ዚሚያደርገው ነው። በራሱ ላይ እንዳይተማመንና ነፃነት እንዳይሰማው እዚተደሚገ ነው። ዚፖለቲካው ኀሊት በቁም ነገርና በሚያስፈልጉ ነገሮቜ ላይ ኚማትኮር ይልቅ በሚሆን በማይሆን ነገር ላይ ጊዜ ያባክናል። ሁለ-ገብ ፖሊሲ አውጥቶ ዚተትሚፈሚውን ዹሰው ኃይልና ዚጥሬ-ሀብት ኚማንቀሳቀስ ይልቅ በነጥብ በነጥብ በሚካሄዱ ነገሮቜ ላይ ብቻ በደስታ ይሚካል።  ኹዚህ ስንነሳ አጠቃላዩ ፖለቲካ ኚብርሃን ይልቅ ሙቀት ዚበዛበትና ዚሚለበልብ ነው ለማለት እቃጣለህ። ኹዚህ ዐይነቱ ሁኔታና አስተሳሰብ እስካልተላቀቅን ድሚስ ዕውነተኛ ዕድገት ማዚት አንቜልም። ስለሆነም ኚሁለት ነገሮቜ አንዱን መምሚጥ ዹጊዜው አንገብጋቀ ጉዳይ ነው። ወይ በትናንሜ ነገሮቜ ላይ ማትኮርና እዚተተራመሱ መኖር፣ አሊያም ደግሞ ኹውጭ ተፅዕኖ ዚሚያላቅቅ ሁለ-ገብ ዚኢኮኖሚ ፖሊሲ በመኹተል ታሪክ ሰርቶ ማለፍ።

     መደምደሚያ!

በአጠቃላይ ሲታይ ህዝባቜንና አገራቜን ኹፍተኛ ዹሆነ ዚፖለቲካ አጣብቂኝ ውስጥ ገብተዋል። ኚመንግስቱ በሻገር በኢትዮጵያ ስም ዚሚነገዱና ዚሚምሉ፣ በሌላ ወገን ደግሞ ዚአገራቜንን ታሪክ ዚሚክዱ፣ አንድ ዚሚያደርገን ታሪክ ዹለንም በሚሉት መሀክል ዚፖለቲካው አዹር ታምቋል። በዚህ ላይ አገሪቱ ጥራትን ሳይሆን ውዝንብርን በሚያስኚትልና ህዝቡን ግራ በሚያጋቡ ኀክስፐርቶቜ ነን ባዮቜ፣ ዹዚህም ሆነ ዚዚያ ሃይማኖት ዕምነት ተኚታዮቜ ነን ባዮቜ፣ ዹሚሆነውን ዹማይሆነውን እያወሩ በተለይም ወጣቱን በሚያሳስቱ ኃይሎቜ ኹፍተኛ ውዥንብር እዚተነዛ ነው። አገሪቱ ወዎት እንደምትጓዝ በቀጥታ ማወቅ ዚማይቻልበት ወቅት ላይ ወድቀናል። እነዚህ ሁሉ ኃይሎቜ በአንዳቜ ቲዎሪና ፍልስፍና ወይም ሳይንስ ተመርኩዘው ስለማይንቀሳቀሱ በትክክል አቋማቾውን ለማወቅ በጣም አስ቞ጋሪ ሆኗል። ቀለም ዚሌላ቞ው፣ ኚፖለቲካ ወይም ኚርዕዮተ-ዓለም አንፃር ሲመሚመሩ እንደዚህ ዐይነቱን አቋም ነው ዚሚያራምዱት፣ ስልጣንም ላይ በሚወጡበት ጊዜ ይህንን ዚሚመስል ፖሊሲ ነው ተግባራዊ ለማድሚግ ዚሚፈልጉት ብሎ መናገር በፍጹም አይቻልም። ይህ ዐይነቱ ግልጜነት ዹሌለውና በአንዳቜ ዐይነት ፍልስፍና ወይም ሳይንስ ዹማይደገፍ ፖለቲካ ዹሰውን አስተሳሰብ በአዹር ላይ ተንሳፎ እንዲቀር ኚማድሚግ በስተቀር ዚነፃነቱንና ዚዕድገቱን መንገድ ማሳዚት ዚሚቜል አይደለም። ኹዚህ በተጚማሪ በጣም አደገኛ ዹሚሆነው በውጭ ኃይሎቜ በመደገፍና ገንዘብ እንዲፈስላ቞ው በመደሹግ ወጣት ኃይሎቜን በጥላቻ መንፈስ ዚሚቀሰቅሱ ኃይሎቜን መዋጋቱ ነው።

ኹዚህ ሁሉ ሁላቜንንም ዚሚያሳስበው ጉዳይ በተለይም ምሁር ነኝ ዹሚለው ለህዝቡ አቅጣጫ ለመስጠት ዚሚያስቜለው ፍልስፍና ሊያፈልቅና ሊያዳብር አለመቻሉ ነው። አብዛኛው ዹውጭ ኃይሎቜን፣ በተለይም ዚአሜሪካንን ዚበላይነት ዹተቀበለ ይመስላል። ኹዚህ ውጭ ዚኢትዮጵያን ፖለቲካ መወሰን አይቻልም ብሎ ደምድሟል። ይህ ዐይነቱ በራስ ላይ ዕምነት ማጣትና በውጭ ኃይሎቜ ላይ መተማመንን መፍጠር ለነፃነትና ለዕውነተኛ ህብሚተሰብአዊና ዚኢኮኖሚ ዕድገት ዹሚደሹገውን ትግል እጅግ አስ቞ጋሪ ያደርገዋል። እንደምናዚው ዚምዕራቡ ድጋፍ በተለይም ዚአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም በአገራቜን ውስጥ ባለፈው 27 ዓመታት ዘራፊና አምባገነናዊ መንግስት እንዲፈጠርና ህዝባቜንን እንዲጚቆንና ፍዳውን እንዲያሳይ ነው ያደሚገው። አሜሪካ አንድን መንግስት ዹሚደግፈው አገዛዙ ጊርነት እስካካሄደለትና ህብሚተሰብአዊ  ዝብርቅርቅነት እንዲመጣ ካደሚገለት ብቻ ነው። ቢያንስ ቻይናዎቜ ዚተሻለ ስራ ይሰራሉ። ኚምዕራቡ ዚካፒታሊስት ዓለም አሳሳቜና አገር አፍራሜ ፖለቲካ በመማር አንዳንድ ፕሮጀክቶቜን ይሰራሉ። አሜሪካን ዹአፄ ኃይለስላሎ ወዳጅ በነበሚበት ጊዜና፣ ህውሃትን አቅፎ ደግፎ ህዝባቜንን ሹግጩ እንዲገዛ እስካደሚገበት ጊዜ ድሚስ „ይሰጥ ኹነበሹው ድጋፍ“  ኚቻይናው ጋር ሲወዳደር ኚቻይና ዚሚመጣው ድጋፍና ተግባራዊ ዹሚሆነው ፕሮጀክት በብዙ እጅ ዚተሻለ ነው። ይሁንና ግን ይህ ዐይነቱ አካሄድ ዕውነተኛ ነፃነትና ሁለ-ገብ ዹሆነ ዚኢኮኖሚ ዕድገትን ዚማምጣት ኃይል ዚለውም። ያም ሆነ ይህ ዚአሜሪካን ወንጀል በግልጜ እዚታዚና፣ ኚዚያ በሚመጣውም ዚኢኮኖሚ ፖሊሲና ተግባራዊነቱ አገራቜንን ብቻ ሳይሆን ሌሎቜ ዚላቲን አሜሪካ አገሮቜም በሚታመሱበት ጊዜ ሁላቜንም አሜሪካንን እንደ ነፃ አውጭና ዚዲሞክራሲ ብርሃን አፈንጣቂ ኃይል አድርገን ተቀብለናል።

ይህንን ሁሉ ዐይነቱን ዚፖለቲካ ውዥንብርና መወናበድ መቋቋም በፍጹም አይቻልም። በተለይም ሰው በግልጜ ለመወያዚትና ለመኚራኚር በማይፈልግበት ሁኔታ ውስጥ ኃይልን መጚሚስ ብቻ ነው ትርፉ። ዚራስን ህይውት እያበላሹ መታገልና ይህንን ሁሉ ግፊትና ቲዎሪ-አልባ አካሄድ መቋቋም በፍጹም አይቻልም። ዚአንድ ህብሚተሰብ ትግል ውጀታማ ሊሆን ዚሚቜለው ዚአስተሳሰብ አንድነት(Unity of Thought) ሲኖር ብቻ ነው። ዚአስተሳሰብ አንድነት ሲኖርና፣ በተለይም በአሁኑ ዚውዥንብር ዓለም ዚአስተሳሰብ ጥራት ብቻ ሳይሆን ተኚታታይነት ያለው ዚጠራ አስተሳሰብ ሲሰራ ለህብሚተሰብአዊ ለውጥ ዹሚደሹገው ትግል መልክ ሊይዝ ይቜላል። ለተኚታታና ጥራት ለሚኖሹው ስራ ደግሞ  ዚማ቎ሪያል ሁኔታዎቜ መዘጋጀት አለባ቞ው። ሳይንሳዊና ተግባራዊ ሊሆኑ ዚሚቜሉ ጜሁፎቜን በተኚታታይነትና ጥራትነት ባለው አቀራሚብ በዹጊዜው ለንባብ ማቅሚብ ያስፈልጋል። ጋዜጣ ወይም መጜሄት ወይም ለዚህ ዐይነቱ አስተሳሰብ ማስተጋቢያ ዹሚሆን ልዩ ዐይነት ድህሚ-ገጜ ለማዘጋጀት ዹሰው ኃይልና ዚማ቎ሪያል ሁኔታ በበቂው መዘጋጀት አለባ቞ው። ይህ ሁሉ ነገር በአንድና በሁለት ሰዎቜ ትኚሻ ላይ ዚሚወድቅ ሳይሆን ዚብዙ ሰዎቜን ቆራጥና ተኚታታይነት ያለው ተሳትፎ ዹሚጠይቅ ነው። ይህ ጉዳይ ደግሞ ዞሮ ዞሮ መደራጀትንና ለአንድ ዓላማ መቆምን ይጠይቃል። አንድ አገር በአክቲቪስቶቜና እዚህና እዚያ በሚደሹግ ንግግር አይደለም ነፃ ዚምትወጣው። ጥራትና ተኚታታይነት ባለው ስራ እንጂ!! መልካም ግንዛቀ !!

                                                                  fekadubekele21@gmx.de